Saturday, April 26, 2014

“አማራ ከኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ ከአፍሪካም እጅግ ድሃ ሕዝብ ነው”

“አማራ ከኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ ከአፍሪካም እጅግ ድሃ ሕዝብ ነው”

ከድንበሩ ስዩም
መቀመጫውን ኳታር ያደረገው አልጀዚራ እየተባለ የሚጠራው ቴሌቪዥን ጣቢያ በኢትዮጵያ ላይ ከሰሞኑ አንድ ዶክመንተሪ ፊልም አቅርቦ ነበር። ፊልሙ የሚያተኩረው በሰሜን ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኘው በአማራ ክልል እና በውስጡ ያሉት ነዋሪዎች በዓይን ሕመም ምክንያት ለዓይነ-ስውርነት እንዴት እንደሚጋለጡ እና ከዚሁ ጋር ተያይዞ ደግሞ በዘመቻ መልክ ወደ ክልሉ ተጉዘው በነፃ የዓይን ሕክምና ስለሚሰጡት ዶክተሮችም የበጎ ተግባር ሥራ ነው። ዶክተሮቹ የበርካታ ሰዎችን ብርሃን መልሰው ሲያመጡትም ፊልሙ ያሳያል። ይህ የዓይነ-ስውርነት በሽታ በክልሉ ውስጥ እጅግ ከመስፋፋቱም በላይ በአጭሩ መፍትሄ ሳይሰጠው ለረጅም ዓመታት ተንሰራፍቶ መቆየቱም በፊልሙ ውስጥ ይተረካል። የዚሁ ክልል ነዋሪዎች የሆኑትም ‘የአማራ’ ህዝቦች ጓዳ እና የኑሮ ደረጃቸውንም የአልጀዚራ ካሜራዎች ለዓለም እያሳዩት ነበር። ከድህነት ጠርዝ በታች የሚኖሩ ሰዎችን ገመና ካሜራዎቹ አልሸሸጉትም ድህነትን ባይተርኩትም እያሳዩን ነበር። ነገር ግን ተረኩት። ተራኪዋም እንዲህ አለች፡- “አማራ ከኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ ከአፍሪካም እጅግ ድሃ ሕዝብ ነው” በማለት ተናገረች። ነገሩን እንደ ኢትዮጵያዊነት ስንወስደው ልብ ይነካል። ያደማል። ያሳፍራል። ያበሽቃል። ግን ደግሞ በጥሞና ስናስበው ጉዳዩ ያልተጋነነ እውነት ሆኖ እናገኘዋለን። ምክንያቱም አበው ማየት ማመን ነው ስለሚሉ፣ የአልጀዚራ ካሜራዎች እውነቱን እያሳዩን ነበር።
ግን የአማራ ሕዝብ የአፍሪካ ድሃ ነው? የዚህ ሕዝብ ድሕነት እንዴትስ እዚህ ደረጃ ላይ ደረሰ? ቀድሞ እንዴት ነበር? አሁን ምን ሆነ? ወደፊትስ ምን ይሆናል? ብዙ ጥያቄዎችን እያነሳሳን መጫወት እንችላለን። ፊልሙ የለኮሰው የሃሳብ ክብሪት በቀላሉ የሚታለፍ አይደለም።
የአልጄዚራ ዶክመንተሪ በዓይን ሞራ ግርዶሽ እና ተያያዥነት ባላቸው የዓይን ሕመሞች ዙሪያ በጐ ፈቃደኛ ሐኪሞች የሚሰጡትን የዘመቻ ሕክምና እና የሕዝቡንም ኑሮ እያሳየ ነበር። የዓይን የሞራ ግርዶሻቸውን ለማስገፈፍ ከወጣት እስከ አዛውንትነት የእድሜ ክልል ውስጥ ያሉት ነዋሪዎች ከ20 ኪሎ ሜትር በላይ በእግራቸው ተጉዘው ሐኪሞቹ ያሉበት ቦታ ሲደርሱና ሕክምናውን ሲያገኙም ይታያል። ለረጅም ዓመታት ብርሃናቸውን አጥተው በጨለማ ሕይወት ውስጥ ሲዳክሩ የነበሩ ሰዎች የብርሃን ፀዳል ሲያዩ የሚፈጠረው ስሜት ልብን ይነካል። አንዳንዱን ደግሞ ሕክምና ቦታም ቢደርስ ዓይኑ በቀላሉ ወደማየት ደረጃ እንደማይደርስና ዓይነ-ስውርነቱ እንደሚቀጥል ሲነገረው ማየትም ልብን ይነካል። ጉዳዩ እጅግ ስሜታዊ ነው። ታዲያ ከዚህ ስሜታዊ ጉዳይ ውስጥ ተፈልቅቆ የሚወጣው ማጠንጠኛ ደግሞ ድህነት ነው።
የዓይነ-ስውርነት ሕመም በስፋት ከተንሰራፋባቸው ክልሎች ዋነኛው የአማራ ክልል ነው። በተለይ ደግሞ ጐጃም ውስጥ ጉዳዩ አሳሳቢ ነው። እኔ ራሴ የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ በአንድ ወቅት ጐጃም ውስጥ የሚገኙ ታላላቅ አድባራትና ገዳማትን ዶክመንተሪ ፊልም ለመስራት በምዘዋወርበት ወቅት በርካታ ሕፃናት፣ ወጣቶችና አዛውንቶች ዓይነ-ስውር ሆነው በማየቴ በእጅጉ ደንግጬ ነበር። ለምሳሌ ዲማ ጊዮርጊስ ተብሎ በሚታወቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስትያን የቅኔ እና የሃይማኖት ማስተማሪያ ገዳም ውስጥ ያየሁት ጉዳይ ለዘላለሙ ከህሊናዬ አይጠፋም። በዚያ ገዳም ውስጥ በርካታ ወጣት ተማሪዎች አሉ። ከእነዚህ ተማሪዎች ውስጥ ሲሶው ዓይነ-ስውራን ናቸው። ይሄ ብቻም አይደለም። የእነዚህ ተማሪዎች መምህርት የሆኑት መነኩሴም ዓይነ-ስውር ናቸው። መምህርታቸውም ሆኑ ተማሪዎቹ ዓይነ-ስውራን ነበሩ። ከዚህ በላይ ልብ የሚነካ ነገር የለም። አልጀዚራ ይህን ጉዳይ ግን አልሰራውም።
በወቅቱ የዚህን የዲማ ጊዮርጊስን ጉዳይ በተመለከተ የደብሩን ኃላፊ ጠይቄያቸው ነበር። “ለምንድን ነው ተማሪዎቹም መምህርታቸውም ዓይነ-ስውራን የሆኑት?” አልኳቸው። የደብሩ ኃላፊም ሲመልሱ፤ “ለአብነት (ለቆሎ) ተማሪዎች እንደ ድሮ ምግብ የሚሰጣቸው የለም። ዞረው ለምነው የሚበሉትን አግኝተው መማር አልቻሉም። ስለዚህ ዓይን ያላቸው (ማየት የሚችሉት) ወደ አዲስ አበባ እየሄዱ ሎተሪ ይሸጣሉ። ማየት የማይችሉት እነዚህ ደግሞ የት ይሒዱ? እዚሁ ሆነው ከነችግራቸው እንደምንም ይማራሉ። ዓይነ-ስውራኑ በከፍተኛ ችግር ውስጥ ናቸው” እያሉኝ የደብሩ ኃላፊ አጫወቱኝ።
ጐጃም ውስጥ ለምንድን ነው ዓይነ-ስውርነት የተስፋፋው? ሕፃናት ሳይቀሩ ዓይነ-ስውራን ናቸው። ይህ ጉዳይ ሊመረመር እና መንስኤው ሊታወቅ ግድ ይላል።
አልጀዚራ ዓይነ-ስውርነትን መሠረት አድርጐ “አማራ ከኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ ከአፍሪካም እጅግ ድሃ ሕዝብ ነው” ብሎ ተናገረ። ይህን አባባል ከሰማ ብዙ ነገር አሰብኩ። እኔ የአማራ ክልል ተወላጅ አይደለሁም። ግን ደግሞ አማራ ኢትዮጵያዊ ነው። ያውም ብዙ ታሪክ ያለው። ብዙ ሀብት ያለው። ባሕል ያለው። ማንነት ያለው። ለሀገሩ ቤዛ የሆነ። ብዙ ነገር መጠቃቀስ ይቻላል። ታዲያ ይህ ህዝብ የአፍሪካ ድሃ ህዝብ ነው ሲባል እንደ ኢትዮጵያዊነት ሁላችንንም ጉዳዩ የሚቆረቁረን ይመስለኛል። ከዚህ ከአልጀዚራ አባባል የሚደሰት ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለኝም። ምክንያቱም ጉዳዩ የአማራ ሕዝብ ብቻ አይደለም። የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጉዳይ ነው።
የአማራ ክልል የአፍሪካ የቋንቋ ማዕከል ነው። በዚህ ክልል ውስጥ ተወልዶ እና አድጐ የመላው ኢትዮጵያ ቋንቋ የሆነው አማርኛ ከአፍሪካ ውስጥ የራሱ ፊደል ያለው ብቸኛ ቋንቋ ነው። በ1950ዎቹ ውስጥ በተሰራ ጥናት የአፍሪካ ኅብረት ቋንቋ መሆን አለበት እየተባለ ሁሉ የሃሳብ ክርክር ቀርቦ ተቀባይነት አግኝቶ ነበር። ቋንቋው ከመግባቢያነት አልፎ እጅግ የዳበረ የሥነ-ፅሁፍ ቋንቋ ነው። የትልልቅ ፍልስፍናዎችና አመለካከቶች መገለጫም ነው። እናም ይሄ የአፍሪካ ድሃ ሕዝብ፣ ለአፍሪካ ቋንቋንና ሥነ-ጽሁፍን ያበረከተ ነው።
የአማራ ክልል በአፍሪካ ውስጥ ቁጥር አንድ የሆነ የታሪክና የቅርስ ማዕከል ነው። ለምሳሌ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባሕል ድርጅት /ዩኔስኮ/ የዓለም ድንቅዬ ቅርሶችን እያለ የሚያቆለጳጵሳቸው አያሌ ጉዳዮች መቀመጫቸው እዚሁ አማራ ክልል ውስጥ ነው።
በሰው ልጅ የኪነ-ሕንፃ ምርምር እና ጥናት ውስጥ እስከ አሁን ድረስ የአሰራራቸው ምስጢር ምን እንደሆነ የማይታወቁት የቅዱስ ላሊበላ ፍልፍል አብያተ-ክርስትያናት የአፍሪካ ቁጥር አንድ ቅርሶች ናቸው።
የ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የዓለም የሥልጣኔ ማዕከል ናት እየተባለች በታሪክ ተመራማሪዎች ዘንድ ዘወትር የምትጠቀሰው የጐንደር ከተማ እና በውስጧ ሰብስባ የያዘችው አብያተ-መንግሥታትና አብያተ-ክርስትያናት የኪነ-ሕንፃ አሰራር የዓለም ድንቅዬ ቅርሶች ናቸው ብሎ የመዘገበው ይሄው የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት ነው። ጐንደር በ17ኛውና በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በጥበብና በስልጣኔ ገናና ሆና በምትጠራበት ወቅት መላው አፍሪካ በባርነት ቀንበር ውስጥ ይዳክር ነበር። በወቅቱ ጥቁር ሕዝቦች ሁሉ በቅኝ ግዛት ተስፋፊዎች መዳፍ ስር ገብተዋል። በጭቆና ውስጥ ለወደቁ ለጥቁር ሕዝቦች በመሉ የነፃነት አርአያ ሆኖ የኖረው ይህ ሕዝብ እና ክልል ዛሬ የአፍሪካ ድሃ ሕዝብ ነው ሲባል ይቆረቁራል። ያማል። ያሳስባል። …. አሜሪካ በእንግሊዞች የቅኝ አገዛዝ ስር ስትማቅቅ ጐንደርን የኢትዮጵያ መዲና አድርጐ ይኖር የበረው አስተዳደር የነፃነት ተምሳሌት ነበር። ዛሬ የአፍሪካ ድሃ ሕዝብ እየተባለ ነው።
በሥነ-ጽሑፍ ዓለም ውስጥም ከአፍሪካ አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃም ቢሆን 12 ጥንታዊ መፃህፍትን የዓለም ድንቅዬ ቅርሶች ሆነው የተመዘገቡት በዚሁ ክልል የተፃፉና የተገኙ ናቸው።
በሐይማኖት፣ በባሕልና በታሪካዊ እሴቶችም ቢሆን ክልሉ ያበረከተው አስተዋፅኦ ቀላል አይባልም። እንደውም አፍሪካዊ ለዛና ማንነት ያላቸው ጉዳዮችን በስፋት የምናገኝበት ክልል ነው። እጅግ በርካታ ገዳማትና አድባራት እንዲሁም ደግሞ በውስጣቸውም የጥቁር ሕዝቦች ሁሉ መኩሪያ የሆኑ ቅርሶችን የያዙ ናቸው። ከፍም ሲል ደግሞ የሰው ልጅ ሁሉ መመኪያ የሆኑ ሃይማኖታዊ ቅርሶችን በውስጡ ጠብቆ የኖረ ክልል ነው።
በቅርቡ ዩኔስኮ ከሃይማኖታዊ ክብረ-በአሎች አንዱ የሆነውን የመስቀል አውደዓመትን የዓለም ቅርስ አድርጐ መዝግቦታል። ታዲያ የመስቀል በዓልን እጅግ ብርቅ ካደረጉት ጉዳዮች አንዱ እየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ግማደ መስቀል እዚሁ ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይም በአማራ ክልል ግሸን ደብረ-ከርቤ ውስጥ መኖሩ ነው። ከዚህም አልፎ በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተደጋግሞ የሚጠቀሰው ግዮን /የአባይ ወንዝ/ በወርድና በቁመት ተገማሽሮ የሚገኝበት ቦታ ነው። አባይ የጣና ሐይቅ ማህፀን ውስጥ ገብቶ የሚወጣውም ከዚህ ክልል ነው። ጣና ሐይቅ ላይም 37 ደሴቶች ኖረው ሁሉም ማለት ይቻላል እጅግ ድንቅዬ አብያተ-ክርስትያናት ያሏቸው ናቸው። ያውም ከበርካታ ልዩ ልዩ ቅርሶች ጋር። ታዲያ ይህ ክልል አሁን የአፍሪካ እጅግ ድሃ ህዝቦች መኖሪያ ነው ሲባል ያሳፍራል።
የአማራ ህዝብ ከሌሎቹ የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በመሆን ሀገሩ ኢትዮጵያን ከባዕዳን ወረራ ጠብቆ የኖረ ሀገሪቱ በቅኝ ገዢዎች መዳፍ እንዳትወድቅ መስዋዕትነትን የከፈለ ህዝብ ነው። “የነፃነት – መስዋዕት” በመሆን ሀገሩን አስከብሮ የኖረ የታሪክ ባለቤት ነው። ግን የአፍሪካ ቁጥር አንድ ድሃ እየተባለ ነው።
አማራ ክልል በርካታ የሀገሪቱን ምሁራን ያፈራም ክልል ነው። በሳይንስ፣ በፍልስፍና፣ በታሪክ፣ በቋንቋ እና በሌሎችም የትምህርት መስኮች ውስጥ አንቱ የተባሉ ሰዎችን ያፈራና እያፈራም የሚገኝ ነው። ግን ድሃ ህዝብ ነው። ኧረ ሌሎችንም ጉዳዮች እያነሳሳን መጫወት እንችላለን። ቢሆንም እዚህ ላይ ቆም እናድርገውና ድህነት ምንድን ነው? ለምንስ የአፍሪካ ድሃ ሕዝብ ሆነ የሚለውን ሁላችንም መልስ ለመስጠት መሞከር አለብን።
ይህ ሕዝብ በአንዳንድ መስመር በሳቱ ግለሰቦችና ተቋማት አማካይነት ‘አድሃሪ’፣ ‘ትምክተኛ’፣ ‘ነፍጠኛ’ ወዘተ እየተባለ የራሱ ወገኖች በሆኑ ኢትዮጵያዊያንም ሲንጓጠጥ እና ሲዘለፍ የኖረም ነው። ይሄ ደግሞ ማኅበራዊ መሸማቀቅን ፈጥሮበታል። በእነዚህ ቅስም ሰባሪ ቃላት እንደልባቸው ሲዘልፉት የነበሩት ሰዎች አንድም ቀን ሲጠየቁ እና የሚናገሩትም ነገር ስህተት እንደሆነ በአደባባይ ተነግሯቸው አያውቅም። ይሄ ሲዘለፍ የኖረው ህዝብ አሁን ደግሞ የአፍሪካ ቁጥር አንድ ድሃ ሆኗል። ኦነግን የመሳሰሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የማሸማቀቁን ሚና በሰፊው ተጫውተውታል።
ሌላውና አንገብጋቢው ነገር ደግሞ የአማራ ህዝብ ራሱን መጠየቅ አለበት። የዚህ ሁሉ ባህል፣ ታሪክ፣ ቅርስ፣ ማንነት ባለቤት ሆኜ ለምን ድሃ ሆንኩ ብሎ መጠየቅ ያለበትም ወቅት ነው። በርግጥ ይህን ጥያቄ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሊጠይቀው የሚገባ ነው። ለምን ድሃ ሆንን?
አልጀዚራ የአማራን ህዝብ የአፍሪካ ቁጥር አንድ ድሃ ነው ቢለው ያበሽቃል እንጂ ሀሰት አይደለም። የአማራ ህዝብ በተለያዩ ከተሞች ውስጥ በልመና የሚተዳደር ነው። በሰው ቤት ሰራተኝነት የሚያገለግሉት የአማራ ተወላጆች ናቸው። ከቦታ ቦታ የሚሰደዱትም የሚፈናቀሉትም እነርሱ ናቸው። ግን እንደ አንድ ህዝብ የተሻለ ህዝብ እንዲሆን ከማን ምን ይጠበቃል የሚለው ጥያቄም መመለስ አለበት።
በባሕል፣ በታሪክ፣ በቅርስ ወዘተ መበልፀግ እንዴት ከድህነት ሊያወጣን አልቻለም ብሎ ማሰብም ተገቢ ነው። በአጠቃላይ ሲታይ ኢትዮጵያ ከድህነት ወለል በታች ናት እየተባለ በሚነገርበት ሁኔታ ውስጥ የአማራ ህዝብ ደግሞ የድህነት ጣሪያው የጐላ መሆኑን አልጀዚራ ተናግሯል፤ ስለዚህ ቆም ብለን ረጅሙን ጉዞ ከአሁኑ አሻግረን እያየን መጪውን ጊዜ የተሻለ ለማድረግ ብዙ መጣር አለብን።
Ze-Habesha Website may contain advice, opinions, and statements of various information and content providers. The Website neither represents nor endorses the accuracy of information or endorses the contents provided by external sources. All blog posts and comments are the opinion of the authors.

No comments:

Post a Comment