Saturday, January 11, 2014

“ፓርቲ ለመምራት ብዙ የሚቀረኝ ቦታ እንዳለ ተረድቻለሁ” – አቶ ግርማ ሰይፉ


አንድነት ጠቅላላ ጉባኤውን በማድረግ እና ፓርቲውን እስከቀጣይ ጉባኤ የሚመራውን አዲስ የፓርቲ ሊቀመንበር መርጧል፡፡ ፓርቲው ለሁለት ቀናት አባላቱን በመሰብሰብ ጠቅላላ ጉባኤውን ካከናወነ በኋላ፣ ታህሳስ 20/2006 ዓ.ም ምሽት ላይ አባላቱ የሰጡትን የድምፅ ውጤት ይፋ በማድረግ አዲሱን ተመራጭ አሳውቋል፡፡ በዕለቱም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ጋዜጠኞች በቦታው ተገኝተው የነበር ሲሆን፤ የድምፅ ውጤቱ ይፋ ከመደረጉ አስቀድሞ ፓርቲውን ላለፉት 3 ዓመታት ለመሩት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ሽልማት መበርከቱ አይዘነጋም፡፡ ከዝግጅቱ ውስጥ ትኩረት የሰጠው ከትግራይ ክልል የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ቅርንጫፍ ቢሮ የተበረከተላቸው ሽልማት ነው፡፡
Girma Siefu
ሽልማቱ ታሽጎ ነበረ በመሆኑ፤ ምን ሊሆን ይችላል? የሚለው የበርካታዎችን ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ ሽልማቱ ከታሸገበት ሲከፈት፣ በእንጨት ቅርፅ የተፈለፈለ ብርማ ቀለም ያለው የአክሱም ኃውልት ሆኗል፡፡ ይህን የአክሱም ኃውልት ሽልማት ስጦታ ያበረከቱት ተወካይ ሲገልጹ፣ በአንድ ወቅት የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት መለስ ዜናዊ የአክሱምን ኃውልት አስመልክተው ሲናገሩ፣ “የአክሱም ኃውልት ለወላይታ ህዝብ ምኑ ነው? ብለው ነበር፡፡ ሌላው አቦይ ስብሃት ነጋም የአክሱም ኃውልት ለአዳማና (ትግራይ ክልል ውስጥ የሚገኝ ቦታ) ለአጋሜ ምኑ ነው? በማለት ገልጸዋል፡፡ ታዲየ የአክሱም ኃውልት ለኢትዮጵያውያን ሁሉ ነገሩ ነው፡፡” በማለት ሽልማቱን አበርክተዋል፡፡
ከትግራይ የመጡት ተወካይ አያይዘውም ሲገልጹ፣ ብዙውን ጊዜ በህወሀት ላይ ያለውን ጥላቻ ለመግለፅ “ወያኔ” ይባላል፤ ወያኔ ማለት ቃሉ ራያና ተምቤ እንደርታ የነበሩ ገበሬዎች ግፍ ሲፈፀምባቸው አንቀበልም በማለት ኢፍትሃዊ አገዛዝን ለመቃወም ያደረጉት እንቅስቃሴ መጠሪያ ነው፡፡ እናም ህወሀትን ወያኔ ስንል ጀግና እያልን ጠራነው ማለት ነው፡፡ ወያኔ የሚለው ቃል ከዚህ በኋላ ሕወኃትን አይወክለውም፡፡ ህወሀትን የሚወክለው ገንጣይ አስገንጣይ የሚለው ቃል ነው” ሲሉ ገልፀው ነበር፡፡
ስለፓርቲው ሊቀመንበሮች ምርጫ ውጤት የምርጫ ሂደቱን ሲያስተባብሩ የነበሩ ወገኖች ወደ መድረክ በመውጣት ስለምርጫው ይዘት ተናግረዋል፡፡ እንዳሉትም ከሆነ አዲሱን የአንድነትን ሊቀመንበር ለመምረጥ 290 ሰዎች ተካፋይ ሆነዋል፡፡ ይሁንና ከዚህ ውስጥ 34 ወረቀቶች አልተካተቱም፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ለምርጫ በተሰጠው ወረቀት ላይ በሶስቱም ቦታዎች ላይ ወይም ተመራጮች ስም ላይ የራይት ምልክት በመደረጉ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የማያገለግል ሆኖ በመገኘቱ ከውድድር ውጭ ሆኗል፡፡ በዚህ ምክንያት የ256 ድምፆች ውጤት ነው የተካተተው፡፡ በዚህ መሰረት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው 227 ድምፅ በማግኘት አንደኛ ሲሆኑ አቶ ግርማ ሰይፉ ደግሞ 29 ድምፅ በማግኘት በሁለተኝነት ተቀምጠዋል፡፡ ሶስተኛው ዕጩ ራሳችውን አግልለዋል፡፡ በቀጣይነትኢንጅነር ግዛቸው ሽፈራው ፓርቲውን በሊቀመንበርነት እንዲመሩ ተመርጠዋል፡፡ ከዚህ ውጤት በኋላ በምርጫው ማሸነፍ ያልቻሉት አቶ ግርማ ሰይፉ ወደ መድረክ በመውጣት የተሰማቸው ስሜት ምን እንደሆነ እንዲገልፁ ተጠይቀው፡-
“የቅስቀሳው ጊዜ አጭር ነበር፤ ውጤቱን ከቅስቀሳ በኋላ መገመት ቀላል ነው፡፡ ባሸንፍ ላደርግ የነበረውን ንግግር አላመጣሁትም፡፡ ስለዚህ የምጠብቀው ነው የሆነው፡፡ ውጤቱ ልክ ነው ልክ አይደለም የምርጫ ኮሚቴዎቹ የገለፁት ነው፡፡ ስለዚህ አሁን የተሰጠው የምርጫ ውጤት ከጠቅላላው መራጭ ህዝብ 10 ፐርሰንት ነው፡፡ በዚህ ውጤት ፓርቲ ለመምራት ብዙ የሚቀረኝ ቦታ እንዳለ ተረድቻለሁ፡፡ ትልቁ ክፍተት ምንድነው ብላችሁ ብትጠይቁኝ ይህንን ለማድረግ ከመረጠ ህዝብ ጋር ምን መደረግ ነበረበት? ምን ማድረግ ነበረብኝ? የሚለው ነው፡፡ ምንም አላደረኩም፤ አውቃለሁ፤ ስለዚህ ፊት ለፊት ነበረ ጨዋታው፡፡ ፊት ለፊት የተገኘውን ውጤት እቀበለዋለሁ፡፡ ለተመራጩ ፕሬዚዳንት መልካም የስራ እና የስኬት ዘመን እንዲሆንላቸው እመኛለሁ፡፡ 10 ፐርሰንት በወረዳ ጠንክሮ ለመሰረት ጠቃሚ ነው ብዬ አስባለሁ” ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ከዛ በኋላ አዲሱ ፕ/ት ኢ/ር ግዛቸውና ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በመድረክ ላይ በመውጣት የስልጣን ርክክብ ሰላምታ በመለዋወጥ በቦታው ለነበሩ ታዳሚዎች አሳይተዋል፡፡ ከአንድነት ወገኖች በወቅቱ የሎሚ መፅሔት ዘጋቢዎች መረጃ ሲያሰባስቡ የበርካቶች ግምት አቶ ግርማ ሰይፉ ይመራሉ የሚል ነበር፡፡ እንደታሚወቀው አዲሱ የአንድነት ሊቀመንበር ኢንጅነር ግዛቸው ሺፈራው ከዚህ ቀደም ፓርቲውን በምክትልነት የመሩ ሲሆን በ1997 ዓ.ም ምርጫ በወረዳ 17 ተወዳድረው አሸናፊ ነበሩ፡፡ ከዛም የቅንጅት አመራሮች ሲታሰሩ አብረው ታስረው የነበሩ ናቸው፡፡ የ“ሎሚ” መጽሔት አዘጋጅ ቶማስ አያሌው ከተከበሩ አቶ ግርማ ሠይፉ ጋ ያደረገው ቆይታ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

አቶ ግርማ፡– ተመልካቾቹ እናንተ ናችሁ፤ እኔ ተወዳዳሪ ነበርኩ፡፡
ጥያቄ፡– የምርጫ ውጤቱን እንዴት አዩት?
አቶግርማ፡– የምርጫ ውጤቱ እንደጠበኩት አልነበረም፡፡
ጥያቄ፡– በምርጫው ቅስቀሳ ወቅት ድክመቴ ምን ነበር ብለው ያስባሉ?
አቶ ግርማ፡– ድክመት ነበረብኝ ብዬ አላስብም፡፡ እኔ በቀጥታ ሳሳይ የነበረው መጫወት የምፈልገውን ነው፡፡ በሌላ መንገድ የተደረገ ቅስቀሳ ስለሆነ፣ ያለኝ ዕድል መቀበል ብቻ ነው፡፡
ጥያቄ፡– አዲሱ የአንድነት ተመራጭን እንዴት ይመለከቷቸዋል?
አቶ ግርማ፡– በአሁን ሰአት በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት መስጠት ተገቢ አይደለም፡፡
ሎሚ፡- የዘንድሮው የፓርላማ እቅንስቃሴ ምን ይመስላል?
ግርማ፡- የተለመደው ነው፤ እየለመድነው ስለመጣን ምንም አዲስ ነገር የለውም፡፡ ሪፖርቶችን መስማት አልተጀመረም፡፡ ምናልባት በፓርላማው ሞቅ ያለ ነገር ካለ፣ ይሄኛው የመጨረሻው ጊዜ ይመስለኛል፡፡
ሎሚ፡- የፓርላማው እንቅስቃሴ አቶ መለስ ከነበሩበት ጊዜ ይልቅ፣ በአቶ ኃ/ማርያም የሥልጣን ዘመን ለውጥ ታይቶበታል ይባላል፡፡ በርግጥ የተለወጠ ነገር ተመልክተዋል?
ግርማ፡- በተወሰኑ ጉዳዮች ዙሪያ ለውጦች ይታያሉ፡፡ የለውጡ ምንጮች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስለሞቱ ነው ወይስ ፓርቲው ችግር የለውም ተብሎ ስለተንቀሳቀስ የሚለውም መታየት ይኖርበታል፡፡ የኢህአዴግ አባላት አቅማችን እየተገነባ ስለመጣ የአቅማችን መገለጫ ነው ሊሉ ይችላሉ፡፡ በእኔ እምነት ግን ፓርላማው እንደተቋም መስራት አስፈላጊ የሆነበት ደረጃ ላይ የደረሰበት ጊዜ ይመስለኛል፡፡ ጠ/ሚ መለስ በነበሩበት ወቅት ፓርላማው እንደተቋም የሚጠበቅበትን ለማድረግ፣ ጠ/ሚሩ ጠቃሚ ነው ብለው የሚያምኑ አይመስለኝም፡፡ ፓርላማው ሊያደርግ የሚችለውን ነገር እርሳቸው በስልክ ያደርጉ ስለነበር ማለት ነው፡፡ የአሁኑ ጠ/ሚ ደግሞ የፓርላማውን ጠቃሚነቱን ተረድተው ሊጠቀሙበት ይችላሉ፡፡ የጠየቅከኝ፣ እዚያ ደረጃ ላይ ደርሰዋል ወይ? ከሆነ አልደረሱም ነው፡- ምላሼ፡፡
ሎሚ፡- “የሚሊዮኖች ድምፅ” ዘመቻችሁን ካደረጋችሁ በኋላ ፓርቲያችሁ ፀጥታን መርጧል እየተባለ መሆኑን ሰምተዋል?
ግርማ፡- ፀጥ አላለም፡፡ በፕሮግራም ስንንቀሳቀስ ቆይተናል፡፡ “የሚሊዮን ድምፅ ለነፃነት” ዘመቻን ስናካሂድ፣ ዓላማችን ህዝቡን ከፍርሃት ቆፈን አውጥቶ መብቱን የሚያራምድበት ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ ይሄ ከሞላ ጎደል የተሳካ ነበር፡፡ በአብዛኛው በተዘዋወርንባቸው ቦታዎች ለማሳካት ችለናል፡፡ ያንን መሠረት አድርገን የመንግስት አስተዳደሮችንና መዋቅሮችን እንዴት ባለ አቅም እንደሚሰሩ ፈትሸናቸዋል፡፡ አቅም የሌላቸው ሌላ ቦታ ስልክ እየደወሉ የሚሠሩ መሆናቸውን አረጋግጠናል፡፡
ሎሚ፡- አንድ ሠሞን እናንተን ጨምሮ ሰላማዊ ሠልፍ በዘመቻ ስታደርጉ ቆይታችኋል፡፡ ሰላማዊ ትግል በሰላማዊ ሠልፍ ብቻ ነው የሚገለፀው?
ግርማ፡- እኛ በዘመቻ መልክ አልተንቀሳቀስንም፡፡ በዕቅድ ነው የተንቀሳቀስነው፡፡ ሌሎች ይሕንኑ እያደረጉ ከነበረ የግጥጥሞሽ ጉዳይ ነው የሚሆነው፡፡ “የሰላማዊ ትግል መገለጫ፣ ሰላማዊ ሠልፍ ነው” የሚል ካለ ተሳስቷል ብዬ ነው የማምነው፡፡ እኛ እርሱ ብቻ ነው ብለን አናምንም፡፡ ሰላማዊ ትግል ማካሄድ የሚፈልግ ሰው ነፃነት ሊሰማው ይገባል፡፡ ስለዚህ መፈክራችንም “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ነበር የሚለው፡፡ ሚሊዮኖች ለነፃነታቸው ድምፃቸውን ማሰማት አለባቸው፡፡ ድምፃቸውን ሲያሰሙ ደግሞ የግድ በጩኸት ብቻ መሆን የለበትም፡፡ የተወሠኑ ሰዎች ሰላማዊ ሠልፍ በመውጣት፣ እስረኛ በመጠየቅና ፓርቲውን በተግባር በመርዳት ሊሆን ይችላል፡፡ እንደዚህ አይነት ነገሮችን በማድረግ ሚሊዮኖች ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ነው ያነቃቃነው፡፡ ይሄም የነፃነት እንቅስቃሴ ነው፡፡
ሰላማዊ ሠልፍ ብቸኛው የትግል ስልት ነው አላልንም፡፡ የእኛ የሰላማዊ ትግል የሚንፀባረቀው ነፃነት ባለው ህዝብ ላይ ነው፡፡ ቀዳሚው ነገር ማንኛውም አይነት የሰላማዊ ትግል ስልት ለመጠቀም፣ ነፃ የሆነ ሰው ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ነፃነቱን የሚያውጅ ሰው ይዘን ነው መንቀሳቀስ የምንችለው፡፡ ዘር ጭንጫ መሬት ላይ ቢዘራ እንደማይበቅለው ሁሉ፣ ሰላማዊ ትግልንም ነፃነት በሌለው ሰው ላይ መዝራት አይቻልም፡፡ አለዚያ ረብሻ መፍጠር ነው የሚሆነው፡፡ የሰላማዊ ትግል ዋናው መሬት ነፃ ህዝብ ነው፡፡ ያንን ከማድረጋችን በፊት፣ “በሉ ከነገ ጀምሮ ለሰላማዊ ትግል እንዲህ እናደርጋለን” ብንል ሕዝቡ ነፃ አይሆንምና ሊተገብረው አይችልም፡፡ ስለዚህ እኛም ይሄንን ነው እያደረግን ያለነው፡፡
ሎሚ፡- የመድረክ እንቅስቃሴ እየተቀዛቀዘ መሆኑን የሚገልጹ ወገኖች አሉ፡፡ መድረኩ አሁን ምን እየሠራ ይገኛል?
ግርማ፡- እኔ የመድረክ ሥራ አመራር አይደለሁም፤ ስለ መድረክ ሪፖርት የማድረግ ኃላፊነት የለብኝም፡፡ ስለዚህ ይሄንን መግለጽ ያለባቸው ኃላፊዎቹ ናቸው፡፡
ሎሚ፡- አንድነትና መድረክ ልዩነት የፈጠሩበት ዋናው ምክንያት ምንድነው?
ግርማ፡- እኛ በመጀመሪያ ደረጃ በመድረክና በአንድነት መካከል ልዩነት አለ ብለን አናምንም፡፡ የሃሳብ ልዩነት በመድረክና በአንድነት ብቻ ሳይሆን፤ በአንድነትም ውስጥ ይኖራል፡፡ የእኛ የሃሳብ ልዩነቶች ሰላማዊ ናቸው፡፡ የሃሳብ ልዩነቶች የጤነኛነት ምልክቶች ናቸው ብለን ነው የምናስበው፡፡ አንተ ጠዋት ስለምትተኛና ማታ ስለምትነሳ፣ ለምን ትነሳለህ? ብለን አንልም፡፡ መተኛትም መነሳትም የጤነኛነት ምልክት ናቸው፡፡ በፓርቲዎች ውስጥም በማንኛውም ግንኙነት መሃል ልዩነቶች ይኖራሉ፡፡ በቤትህም ውስጥ የሃሳብ ልዩነት ሊፈጠር ይችላል፡፡ በመድረክና በአንድነት መካከል የሃሳብ ልዩነት አለ ወይ ከተባለ፣ አዎ አለ፡፡ እነዚህ ልዩነቶች ምንድናቸው? ለሚመለከታቸው አካላት እየተነገሩና እየተገለጹ ናቸው፡፡ ለምን ልዩነት ተፈጠረ ብሎ የሚያስብ ካለ፣ የተሳሳተው እርሱ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ አንድነት ከመድረክ ጋር እየሠራ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ይወጣል፤ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡
ሎሚ፡- ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ውህደት ልታከናውኑ እንደሆነ ሲነገር ነበር፡፡ ከማን ጋር ለመዋሃድ ጠየቃችሁ? እንቅስቃሴውስ ምን ደረጃ ላይ ይገኛል?
ግርማ፡- በጣት ከሚቆጠሩት በቀር፣ ተመዝግቦ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ለመሳተፍ ፈቃድ ያገኘ ከሆነ፣ ማንኛውም ፓርቲ ከአንድነት ጋር ያለን የፕሮግራም አካሄድ ይስማማኛል ካለ ውህደት እንጠይቃለን፡፡ በስትራቴጂክ ፕላናችን መሰረት ይህንን ውህደት የጠየቅነው በ2002 ዓ.ም ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የፓርቲ ቁጥር የምንቀንሰው እንደዚህ አይነት ውህደት በማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን ጥሪ ተቀብሎ ከመጣው ከማንኛውም ጋር ውይይት እንጀምራለን፡፡ ውይይቱ ሲደርስ ውጤቱ የሚገለጽ ይሆናል፡፡
ሎሚ፡- ኢትዮጵያውያን ከሳዑዲ እየወጡ ነው፡፡ የወጡትም በአስከፊ ሁኔታ መሆኑን እየገለጹ ነው፡፡ በተመሳሳይ ከእስራኤልም ኢትዮጵያዊያን እንዲወጡ ተወስኗል፡፡ በዚህ ዙሪያ መንግስት ምን ማድረግ ነበረበት?
ግርማ፡- መንግስት ኢትዮጵያ ውስጥ ለኢኮኖሚ ዕድገት መሠረት ሊሆን የሚችል የፖለቲካ ስርዓት መፍቀድ አለበት፡፡ ኢትዮጵያውያን ሥራ የመፍጠር ዕድል እንዲያገኙና የውጭ ሃገር ዜጎች ጭምር ኢትዮጵያ ውስጥ ገብተው ሥራ ሊፈጥሩ የሚችሉበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነው ያለበት፡፡ መንግስት ይህን ካደረገ ዜጎች ሃገራቸውን ጥለው አይሠደዱም፡፡ ይሄ ባልሆነበት ሁኔታ አሁን ከሳዑዲ ቢባረሩ፣ ተመልሰው ሳዑዲ ኤምባሲ በር ላይ ቆመው ታገኛቸዋለህ፡፡ ከእስራኤልም ቢባረሩ እስራኤል ኤምባሲ በር ላይ ቆመው ታገኛቸዋለህ፡፡ ስለዚህ ከስር ነው መስተካከል ያለበት፡፡
ይህ እስካልሆነ ድረስ ምንም ለውጥ ሊመጣ አይችልም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ሰው ሃገር ሄዶ “እንደዚህ አድርጉ፣ ይሄ ይደረግ” የሚልበት አቅም የለውም፡፡ ሃገራት በሃገራቸው ውስጥ የሚኖሩ ዜጎችን ህጋዊ ካልሆኑ አልፈልጋችሁም “ውጡ” አሉ ብሎ ቡራ ከረዩ ሊባል አይቻልም፡፡ እነዛ ሃገሮች ላይም ዜጎች ከሃገራቸው እንዴት ብለው እንደሚወጡ ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ለሰው ልጅ የሚገባውን ክብርና ሰብዓዊ መብት መስጠት ይገባቸዋል፡፡ ይህንን ማድረግ ያለባቸው የኢትዮጵያን መንግስት ፈርተው ሳይሆን፤ የሚኖራቸውን ልዕልና በማሰብ ነው፤ አለያማ የኢትዮጵያ መንግስት ሊያስፈራራበት የሚችል አቅም ኖሮት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን በውጪ ሃገራት የሚንገላቱትና ክብራቸው የሚደፈረው በሃገራቸው ሥራ የማግኘት፣ የመኖር፣ የነፃነት መብታቸው የተደፈጠጠ ስለሆነ ነው፡፡ ቤቱን ጥሎ ሄዶ ለመዋረድ ፍላጎት ያለው የሰው ልጅ ይኖራል ብዬም አላስብም፡፡
ሎሚ፡- ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የከፉ የተባሉ የሙስና መረጃዎች እየወጡ ነው፡፡ አሁን ከሚታሰሩት አንፃር ገዢው ፓርቲ ሙስናን በተገቢው መንገድ እየተጋፈጠ ነው?
ግርማ፡- መንግስት ለምን ትንንሾቹን ሙሰኞች ነካ ማለት አይቻልም፡፡ ሆኖም ሙሰኞችን በማሰር ብቻ ሙስናን ማቆም አይቻልም፡፡ ድሃ ሚኒስትር እስከሾምክ ጊዜ ድረስ ድህነቱን ለመቅረፍ አንዳንድ ነገሮችን ማድረጉ የማይቀር ነው፡፡ አንድ ሹም በአራትና በአምስት ሺህ ብር ደመወዝ እንዴት ነው የ15 ሺህ ብር የሞባይል ቀፎ የሚገዛው? ለራሳቸው ብቻ አይደለም፤ ለልጆቻቸውም ጭምር ነው የሚገዙት፡፡ ይህ ማለት የሆነ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ለምን ያደርጋሉ አይደለም፤ ማድረግ ካለባቸው በስርዓት ነው መደረግ ያለበት፡፡ ኢህአዴግ አባላቱን የሚመለምለው፣ አባላቱ ጥቅም ስለሚፈልጉ ነው፡፡ ወደ እኛ ፓርቲ አንድነት ስብሰባ ላይ ለመሰብሰብ የሚመጡት ጊዜያቸውን እና ገንዘባቸውን ለመስጠት እንጂ፣ የሚያገኙት ነገር ኖሮ አይደለም፡፡ የኢህአዴግ አባል የሚሆኑት ደግሞ ሥልጣን ለማግኘት ወይም የሆነ ነገር ለማድረግ ነው፡፡ ይሄ እስካልተቀረፈ ድረስ ችግር ይቀጥላል፡፡ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የኢህአዴግ አባል የሚሆኑት ምሕርት ጨርሰው ሲወጡ ሥራ ለመቀጠር ነው፡፡ ይሄ እኮ ሙስና ነው፡፡ ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሊቆጣጠራቸው የሚገቡ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ የሞራል ልዕልና የሌላቸውን ሰዎች መቅጣት የመሳሰለውን ማድረግ ሊሆን ይችላል፡፡
ሎሚ፡- ውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ማሕበራዊ ድረ ገጾችን መጠቀማቸው፣ መድረክ ላይ ወጥተው መዝፈናቸው… ከኢሕአዴግ ባለሥልጣናት አካሄድ ለየት ያለ አልመሰለም?
ግርማ፡- እኔ በበጎ ነው የምመለከተው፡፡ (ረጅም ሳቅ!) ዶ/ር ቴዎድሮስ ልጆቹን ይዞ ስታዲየም ይገባል፡፡ ልጆቹ መደበኛ የሆነ ህይወት ሲኖሩ ታያቸዋለህ፡፡ ፌስቡክና ትዊተር ገጽ ላይ ከህዝቡ ጋር ይገናኛል፡፡ በመደበኛ ሕይወቱም ቀላል የሆኑትን የህይወት እንቅስቃሴዎችን ያደርጋል፡፡ ይሄ መደነቅ አለበት፡፡ ምናልባትም ውጪ ስለተማረ፣ እንደ ኢህአዴግ ሹሞች ተጠርንፎ ስላልኖረ ሊሆን ይችላል፡፡ ሁሉም ባለስልጣናት ከዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም መማር አለባቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ እኔ በበኩሌ ሁለት ድርብ መስመር ይሰመርልኝና በበጎ ነው የምመለከተው፡፡
ሎሚ፡- አንዳንድ የዜና ምንጮች ዶ/ር ቴዎዱሮስ ይሕንን በማድረጋቸው በፓርቲው አለቆች መገምገማቸውን ሰምተዋል?
ግርማ፡- ይሕን ተከልክሎ ከሆነ ትዊተሩ ሲዘጋ አምናለሁ፡፡ አቶ ኃ/ማርያም እንደዚህ ያደርጋሉ ብዬ አላስብም፡፡ ለምን ትዉተር ተጠቀምክ ማለት የሰው ልጅን መብት መንካት ነው፡፡ ግፋ ቢል የመንግስት አቋምን በትዊተር ገጽህ ላይ አትግለጽ ካላሉ በቀር፣ እንዳትጠቀም ማለት ከባድ ነው፡፡ እንዲህ ተብሎ ከሆነ ዶ/ር ቴዎድሮስ ስልጣኑን ቢለቅ ነው የሚሻለው፡፡
ሎሚ፡- በቅርቡ ሕወሐት የተፈጠረበትን ልዩነት በዕርቅ መፍታቱ ተገልጿል፡፡ ሕወሐት በአጠቃላይ ኢህአዴግ በአንድ መስመር ተሰልፏል ማለት ይቻላል?
ግርማ፡- ሕወሐት መሃል ፀብ አለ፡፡ መታረቃቸውንም በማህበራዊ ድረ-ገፆች ላይ ተከታትያለሁ፡፡ በግልጽ የማውቀው ነገር የለም፡፡ እርግጠኛ ሆኜ ግን የምናገረው ሕወሐት መለስ በነበረበት ደረጃ ላይ እንደማይገኝ ነው፡፡
ሎሚ፡- ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተገቢው መንገድ ሥራቸውን እያከናወኑ ነው ማለት ይቻላል?
ግርማ፡- የሚገባቸውን ያሕል እያከናወኑ ነው ላይባል ይችላል፡፡ የአቅማቸውን ግን እያደረጉ ነው፡፡ ይህንን አላደረጉም የሚሉ ሰዎች፣ የጎደለው ይሄ ነው ብለው መግለጽ አለባቸው፡፡ ብዙ ሠዎች ውጪ ሆነው ሊተቹ ይችላሉ፡፡
ሎሚ፡- ፓርቲያችሁ በወጣት ፖለቲከኞች ያምናል?
ግርማ፡- ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በዕምነት ብቻ ሳይሆን፣ እርግጠኛ ሆኜ የምናገርበት ነው፡፡
ሎሚ፡- በወጣቶች የምታምኑ ከሆነ ባለፈው ሳምንት ለፓርቲው አመራር ከታጩት ውስጥ አንድ ወጣት እንኳ እንዴት አላካተታችሁም?
ግርማ፡- አንድነት ቤት መሪነት በፍላጎት የሚሠጥህ አይደለም፡፡ ፓርቲውን ለመምራት የሚወዳዳር ሰው ቢያንስ የመጀመሪያ ዲግሪ ያለው ሊሆን ይገባል፡፡ በዚህ ምክንያት ካልሆነ በቀር ወጣት፣ ጎልማሳ የሚባል ክፍፍል የለም፡፡ ስለዚህ ተወዳዳሪው ባለው አመለካከት ነው የሚመረጠው፡፡ ሥልጣን የምታገኘው በውድድር እንጂ በቅሚያ አይደለም፡፡

zehabesha

No comments:

Post a Comment