Thursday, December 19, 2013

የቀበጠ ቀን፤ የአቅል ማጥ – ዳጥ፤ – በስንጥቅ። (ከሥርጉተ ሥላሴ )


ከሥርጉተ ሥላሴ 19.12.2013
ገርሞኝ! … ሲያንስ …. መገረም …. ም …. እም! ህም!
ጠ/ር ኃይለማርያም ደስአለኝ ያላግጠሉ …
 
sreate1ወይ መዳህኒተ – ዓለም አባቴ … እንዴትና እንዴት ነው ነገሩ? የዓለም ህዝብ በደቡብ አፍሪካ ህዝባዊ አደባባይ የማህሪ ተምሳሌት የሆኑትን የሰላም ልዑቁን ኔልሰን ማንዴላን አክብሮታዊ ዝክረ በተምስጦ ጉባዔ ከወነ። 60000 ነፍስ በአካል ስቴዲዮም ላይ፤  በቴሌቪዥንና በራዲዮ ደግሞ ቪሊዮኖች ታደሙ። ከ100 ሀገሮች በላይ መሪዎቻቸውን ሆነ ውክል አካላቸውን ልከው ሀገሮች ማዕደኛ ሆኑ። በዕለቱ ዬይበቃኛሉን ልዑል የኔልሰንን በተግባር የተባውን፤ በድርጊት የፈለቀውን የህይወት ዘመናት በምልሰት በመቃኘት ሰላም ወዳድ ቤተሰብ ሁሉ ዕንባውን ሲራጭ፤ ልብ በሚናካ ስሜት ውስጡን ሲጋራ፤ የኢትዮጵያ ቴሊቪዥን ኢቲቪ ግን በሁለት ደቂቃ የውክልና ተራ ሪፖርት አጠናቆ የወጣቶች፤ ህብረ – ትርዒት እያለ ሲደልቅ ኢትዮጵያ የዓለም፤ የአፍሪካ አካልነቷ እስኪያጠራጥር ድረስ የቀበጠ ቀን የአቅል ስንጥቅ በዳጥ ሲተራመስ አዬን፤ ሰማን። ትዝብት ነው። ኢቲቪ ከሰረ …

… ውሎ አድሮ  ግን የለበጣ ጨዋታ ተጀማመረ፤ የሃዘን ቀናት ተባለ፤ አለፍ ተብሎም አፍር ለማልበስ በ15.12.2013 ጠ/ሚር ኃይለማርያም ዓይናቸውን በጥሬጬው አሽተው ኩኑ ላይ ተገኙ። በትርጉም ማቃናት ስለማይቻል ገጠመኙን በሰባራ ገሉ፤ ልብጥ የሄሮድስ መለስ ሌጋሲ ተብሎ ቢወራረድ ይሻል ይመስለኛል – ሸንጣራ። ከዚህም በተጨማሪ የወያኔ ደጋፊዎችም ዓለም ለታላቁ የነፃነት አባት የሰጠውን ልዩ አክብሮታዊ ዕውቅና ሲያጣጥሉና ሲያወራጫቸው ነበር የሰነባበተው …. የተበደሉ። …. በቅናት አረሩ – ደበኑ – ትክን ብለውም ተኮመታተሩ ….. የእነሱ መለመላ እንዴት እንደተሰናበቱ ያውቁታልና ….

እንደሚታወቀው በቀደምቶቹ ደጋጎች፤ በተግባር አዛውንታት መሪዎቻችን ኢትዮጵያ በፓን አፍረካኒስትነት እንቅስቃሴ፤ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት በዛሬው ህብረት ምስረታ፤ በተባበሩት ዓለምዐቀፍ ድርጅት፤ በስፖርት አህጉራዊና ዓለምዓቀፍ ፌድሬሽኖች፤ በዓለም ዐቀፍ የውርስ ቅርስ ቤተኝነትም ሳይቀር በሁሉም ትርጉም ያለው ተግባርን የከወነች አንቱ ሆና፤ አስተውሉ አንቱ ሆና፤ በዘመነ ዱድማ ወያኔ ግን ጭራ መሆኗ ሲገርመኝ ውሎ አደረ ….. ያን ቀን ዓለምን የአስከፋ የዕንባ ቀን ሆኖ ህብረት ትርዒቱ በአፍሪካ መዲና አዲስ አባባ ላይ ቅልጥ ቅብጥ ሲል ማዬት ለትውልደ ኢትዮጵውያን ሃሞት ነበር። እነዚህ ጉዶች እኮ ሁለመናችን ነው ፍቅፍቅ እያደረጉት ነው ያሉት ….

ህም! … ኢትዮጵያ ሀገራችን የነፃነት ትርጉም ያገባት ቀደምት አብነታዊት ሀገር በመሆኗ፤ ለመላ አፍሪካ የነፃነት ትግል የደም ጋን ልብ ነበረች። ኢትዮጵያ ለአህጉራችን ለአፍሪካ አርነታዊ እንቅስቃሴ መሪና ረኛም ነበረች። ኢትዮጵያ ነፃነትን የታረቡ ነፍሳትን በእቅፏ ውስጥ በማድረግ ከእቅሟ በላይ የመስዋዕትነቱን ቀንበር የተሸከመች ብቸኛዋ አፍሪካዊት ነፃ ሀገር ነበረች። ኢትዮጵያ ያን ፈታኝ ኃላፊነት ወዳና ፈቅዳ በመውሰድ ከቅኝ ገዢዎች ዴፕሎማሲያዊ ግንኙነቷ ሳይቆስል ወይንም ሳንክ ሳይፈጠር፤ ግን በጥበብና በብልህነት መስጥራ አህጉሯን ከቅኝ ግዛትና ከአፓርታይድ ሰላባ የታደገች ልዩ ቅዱስ መንፈስ ነበረች። ውለታው ማገርነት፤ ምሰሶነት ለጥቁር አርማነት፤ ዓዕምድነቷ ለሰብዕዊ መብት መከበር ቀደምትነት – ለህጉራችን ለአፍሪካ ብቻ ሳይሆን ለዛሬዎቹ ዓለምዓቀፉ ሰብዕዊ መብት አስከባሪ ድርጅቶች ሁለመና ብሩህ ተስፋን የዛራና ያዘመረ ነበር። በዛ ደግ ዘመን ኢትዮጵያ ሥራቸውን አቃለለችላቸው፤ ሸክማቸውን አራገፈችላቸው ለአምንስቲ በሉት ለቀይ መስቀል። ህማማቸውን ቀድማ ፈወሰችላቸው። ትናንት ። መዳህኒታችን እዬሱስ ክርስቶስ ለእኛ ፍቅር እራሱን ሰጠ። ኢትዮጵያ ለአፍሪካዊነት ክብር እራሷን የሰጠች የነፃነት መዳህኒት ሀገር ነበረች …. ዛሬን ተውት … እሷም ህማማት ላይ ናትና ….

ይህን ለሚያውቅ ዘርና ግንድ፤ የዛሬው ታሪክን በሁሉም መስክ ትቢያ ለማልበስ ወያኔ ለሚያደረገውን የታቀደ ደባ ለሚመዝን ህሊና፤ የሽፍታውን እስተዳደር የቋሳ ዓላማ ሆድ እቃ መፈተሽ፤ ሌላ ማገናዘቢያ ሳይስፈልገው ብዙም ሳይደክም ጠንቅቆ ማወቅ ይችላል። ለአደባባዩ የሃዘን ቀን ሀገራችን በባይታውርነት ብቻውን ተንጠልጥላ ተነጥላ ቀረች። ይሁን ተብሎ … ያው እንድትሰረዝ፤ ክብሯም እንዲቀበር፤ ተፈሪነቷም ማቅ እንዲለብስ ተፈርዶባታልና ብጣቂ አትኩሮት ሳይሰጥ የዓለም ሀገሮች ሁሉ በቂ ሽፋን በመስጠት የጥቁር ዕንቁ የስንብት ሳምንታትን በተደሞና በአርምሞ በአኃቲ ድምጽ ከወነ። የአፍሪካ የነፃነት ዓርማዋ ውክል አካል ደግሞ ክብሯን ለመሸጥና ለመለወጥ ሱዳን ላይ አታሞ ሲደልቁ ነበር። ዳር ድንበሯን በስጦታ ለመለገስ ሱዳን ላይ ጠብ እርግፍ ይሉ ነበር ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደስአለኝ። ከእሳቸው የተጠጋ ቅብዐ የማረት ጉድ – ሥጦ። አቅምና ችሎታው የኢትዮጵያዊነት ሚስጢር ለመተርጎም በፍጹም ሁኔታ አለመጠኑን ከዚህ በላይ ማስረጃ ማቅረብ የሚቻል አይመስለኝም። የሰሞናቱ ሂደት ማንነታችን እንድናመሳጥር ግድ ይለን ስለነበር በትዝብት ሁኔታውን ስንከታታል ደግሞ አይታፈር …. ቀብር ላይ እገኛለሁ ብለው ዱቅ! …. የቀበጠ ቀን አቅሉ ሲሰነጠቅ፤ …. ማጥ ዳጥ  … በወያኔ ሽቦ ቱቦ፤

አሁን በሞቴ ወያኔ መራሹ አስተዳደር በምን ሞራሉ ነው በነፃነት አባት ቀብር ላይ ተገኝቶ ስለ ነፃነት የሚሰብከው። ማላገጥ ነው። የዛሬው ማንዴላ እኮ በአሸባሪነት የክስ መዝገብ የሚታወቁት የትግል መስመር እኮ ነው የኛዎቹ እነ በቀለ፤ እነ እስክንድር፤ እነ ውብሸት፤ እነ አንዷዓለም እነ በላይነሽ እነ ርዕዮት ቁጥር የለሽና ስምዬለሽ ሺዎች በካቴና የሚታመስቡት …። አሁን እነሱን በእግር ብረት የቆለፈ አንደበት በምን ሞራል? በምን አቅም? በምን ስሌት? በምን ሜትር? በምን አንደበት? በምን ህሊና? ነው በሰላም – በፍቅር – በነፃነት ወዳድ ህዝብ መሃከል መናገር የሚችለው? …. ይችላል? የቀበጠ ቀን አቅሉ ሲሰነጠቅ በዳጥ ሲያምጥ!

በወ/ሮ /ት ባርባራ የተመራው የአውሮፓ ኮሚሽን እስረኞችን ለማዬት እንኳን ሳይፈቀደለት ተስፋውን ምች አስመትቶ የሸኘ ደኛ አስተዳደር እንዴት ብሎ ነው አፉን ሞልቶ  „ …. አፍሪካ ከማንዴላ ብዙ አግኝታለች። የማንዴላ ህይወት በትግል ውጣ ውረድ የተሞላ ቢሆንም አርያነታቸው የነፃነት የፍትህ የእኩልነትና ነው። የማንዴላን የፍትህና የነፃነት ትግል ከምንም በላይ ደግሞ የሰብዕዊ ክብርን በመጎናጸፍ በክፋት ላይ ያሸናፊነት ተስፋን መፈንጠቅ እንደምንችል ተረድተናል። በዚህ ታሪካዊ አጋጣሚ ከዚህ ታላቅ ሰው ሥራዎችን ለመማር በማቻላችን እራሳችንን እድለኛ አድርገን ልንቆጠር ይገባናል።“  በ15.12.2013 ከሰላም እናት ኩኑ ላይ ጠ/ሚር ኃይለማርያም ደስአለኝ ያደረጉት የለበጣ፤ የማስመሰል፤ የማላገጥ ግልብ፤ እራስን የመዋስና የመበደር ገላጭ ዲስኩር – ተግባር የመከነበት። ማንነታቸው የሾለከባቸው፤ ውስጣቸው እሳቸውን ትቶ ረግረግ የሰመጠባቸው …. ። እራፊ አልባ ሩጫ … መጋጋጫ ….
ለመሆኑ ሰውዬው ከነፍሳቸው ወይንስ ደመ ነፍሳቸውን የትኛው ይሆን ዕጣ ክፍላቸው?! በሺህ የሚቆጠሩ የነፃነት ወገኖችን ያፈነ – ያሳደደ – የገፋ – ያሰረ – የገደለ፤ ህፃናትን፤ ቤተ አምልኮዎችን እስከ መሪዎቻቸው፤ አውደ ምህረቶችን እስከ ቅርሶቻቸው በማንአለብኝነት ያጠቃ። ምህረት ያልሰጠ ውርዴ  በምን ዓይነት  ወኔ ነው ለዛውም እንደ ድህነቷ ጎለጎታ የሰላም ምህረት ወላድ በሆነቸው ኩኑ መንደር አንደበቱን ከፍቶ አንድ ቃል መተንፈ የሚቻለው?  ቃር!

…. ድፍረት ነው! የምር ድፍረት … „በክፋት ላይ የአሸናፊነት ተስፋን መፈንጠቅ“ ይሉናል ጠ/ሚሩ ምን? ወያኔ እኮ ፍጥረቱ ክፋትና በቀልን የሰነቀ። የጎጥ ድርጅት – መርዝ። „ለመማር በመቻላችን“ ድንቄም … … ኪኪኪ … መሳቂያ   ምንድን ነው እነሱ ከተከበሩት የምህረት አባት የተማሩት … ማፈን? ማሳደድ? ማራድ? ማፍለስ? መግለል? መግደል? መብትን መፍለጥ?ልነትን በግፍ መተርተር?  እኮ! ምንድን ነው? እኮ!  ቀለም ፆታ፤ ዕድሜ፤ ወሰን ሳይለዬው ከሰማይ እስከ ምድር በሶስት ተፈጥሯዊ ጅረቶች ዕንባ ከዘነበላቸው ደግና ማህሪ የሰላም አባት ምንድን ነው የቀሰሙት? ለገዳያቸው ምህረትን በገፍ የቸሩ … የመሆን ለጋስ – የወንጌል አርበኛ እኮ ናቸው ማዲባ!   ይህ ሮ ወያኔ የሚሉት ሙጃ ስለምን? ትንሽ የሚመዝንበት ተፈጥሮ አባቴ መዳህኒተ ዓለም እንደ ነፈገው ግራ ያጋባል …. ለመሆኑ አቶ ኃይለማርያም ቃሉን „ነፃነት፤ ፍትህ፤ እኩልነት“ ያውቁታልን? የመንፈሳቸው እድገት ለእኔ ለሥርጉተ ከእንግዲህ ልጅ ላይ ያለ ይመስለኛል … ለነገሩ እሳቸው በፈቃዳቸው ነፃነታቸውን በጠራራ ፀሐይ የሸጡ – የጥገኝነት ሹመኛ፤ ዬት የሚያውቁትን …. በሶስት ምርኩዝ የሚተክዙ ብን …. ምስል።

መቼም የአረብ ሥነ – ጹሑፍ ምርጥ ሆኖ ለዛው ግን ያለ ነው – የውበት ፍልሰት የሚዋኝበት። ስለምን? ይሉኝታ ስለነጠፈበት። የወያኔው መራሹ ጠ/ሚር ቃናቸው የተላመጠ አገዳ ነው የሆነው፤ ይሉኝታው የተጣበቀ። ሰብዕዊ መብት በኢትዮጵያ ቀራኒዮ ላይ ሆኖ እሳቸው ግን በቅዠት ይዋዥቃሉ፤ ለመሆኑ ሰውዬው እያሉኑ ወይንስ …. እዬለሉ …. እንዲህ የጠቆረ ኪኖ በዬጊዜው ጎብኙ እያሉ ልባቸነን የሚያፈሱት …. የቋሳ ዳንኪረኛ!

ልሰብስበው … ጥምልምሉና ጥውልውሉ ንግግር ገመናን በአደባባይ ማወጁ አንገት የሚያስደፋ በመሆኑ እፍረትን ለሸመቱት ጠቅላይ ሚ/ር ወጣ ገቡ ብቃት አዳለጠው – ኩኑ ላይ። አይሆኑ ሆኖም እንኩትኩት ብሎ ኩኑ ላይ ደቀቀ። ከራባቱም ብላሽ ገበርዲኑም ከንቱነት ዘፈነበት።

ጌጦቼ … ቆይታችን ህመምን የነካካ ቢሆንም ፈቅዳችሁ መንፈሳችሁን ለሸለማችሁኝ አንባቢዎቼ ሁሉ ለጥ ብዬ በትህትና ምስጋና አቀረብኩ። መልካም ሰንበት።

አረም የጨፈረበት መንፈስ ሲቀበር ተባይ የለማበት ውስጥ ይጋለጣል።


አግዚአብሄር ይስጥልኝ።




Ze-Habesha Website may contain advice, opinions, and statements of various information and content providers. The Website neither represents nor endorses the accuracy of information or endorses the contents provided by external sources. All blog posts and comments are the opinion of the authors.

No comments:

Post a Comment