Saturday, December 28, 2013

የትግል ስም


(አፈንዲ ሙተቂ)
Nom de Guerre
ለመግቢያ ያህል
ሰሞኑን የበርካታ ሰዎችን የብዕር ስም አካፍዬአችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለትግል ስም በጥቂቱ አወጋችኋለሁ፡፡ አንዳንድ ሰዎቻችን የሚጠሩባቸውን የትግል ስሞችም አካፍላችኋለሁ፡፡
*****
“የትግል ስም” ቃሉ እንደሚያመለክተው በትግል ዓለም ውስጥ ላለ ሰው ነው የሚያገለግለው፡፡ ታጋዩ በትግል ዓለም ውስጥ እያለ የሚጠቀምበት መጠሪያው ነው፡፡ ታጋዮች የትግል ስምን የሚጠቀሙት በልዩ ልዩ ምክንያቶች ነው፡፡ ዋነኛው ምክንያት ግን ታጋዩ በትግል ዓለም ውስጥ ሳለ አደጋ እንዳይደርስበት ለመከላከል በሚል ነው፡፡
የትግል ስም እንደ ብዕር ስም በሚስጢራዊነት አይያዝም፤ ሰውዬው ድሮ የሚታወቅበትን ስም ተክቶ በስራ ላይ ይውላል እንጂ፡፡ ታጋዩ ወደ ትግል ዓለም ከገባ በኋላ የሚያገኛቸው የትግል ጓዶች በትግል ስሙ ነው የሚጠሩት፡፡ በመታወቂያም ሆነ በሌሎች ሰነዶች ጥቅም ላይ የሚውለውም የትግል ስም ነው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ ትግሉን በድል ካጠናቀቀ በኋላም በአብዛኛው በትግል ስሙ መገልገሉን ሲቀጥልበት ይታያል፡፡
የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅም ላይ ያለው ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ ሆኖም የሩሲያ ኮሚኒስቶች በትግል ስም በብዛት በመጠቀም ቀዳሚዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ እንደ ቭላድሚር ሌኒን፣ ጆሴፍ ስታሊን፣ ሊኦን ትሮትስኪ፣ ሉሊ ማርቶቭ ያሉ ስሞች በሙሉ የትግል ስሞች ናቸው፡፡ በሌሎች ሀገሮች የነበሩ ኮሚኒስቶችም በትግል ስም በብዛት ይጠቀሙ ነበር፡፡ ሆ ቺ ሚን፣ ኪም ኢል ሱን፣ ቼ ጉቬራ የመሳሰሉ መጠሪያዎች የትግል ስሞች ናቸው (የቼ ጉቬራ ትክክለኛ ስም “ኧርነስቶ ጉቬራ” ነው፤ የኪም ኢል ሱንግ ትክክለኛ ስም “ኪም ሱንግ ቹ” ነው)፡፡

የትግል ስም በኢትዮጵያ

የትግል ስምን ለመጀመሪያ ጊዜ በስራ ላይ ያዋለው ኢትዮጵያዊ ማን እንደሆነ በትክክል አይታወቅም፡፡ ሆኖም ከተማሪዎች ንቅናቄ የፈለቁት ወጣቶች የፋኖነት ህይወት በጀመሩበት ዘመን በብዛት ስራ ላይ እንደዋሉት ይታወቃል፡፡ ታዲያ እነዚያ ፋኖዎች የትግል ስምን የሚጠቀሙበት ምክንያትና ስሙን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዘይቤ አንድ ወጥ አልነበረም፡፡ የትግል ስም አጠቃቀም ልማድም እንደ ፓርቲው ይለያያል፡፡ ከዚህ በማስከተልም በቀደምት ፓርቲዎች ውስጥ ይሰራበት የነበረውን ልማድ በአጭሩ እናወሳለን፡፡
1. ጀብሃ እና ሻዕቢያ
ጀብሃ እና ሻዕቢያ የትግል ስምን የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ አልተመዘገበም (ወይም አላነበብኩም)፡፡ ሆኖም ሁለቱም ፓርቲዎች የሚስጢር ስም የመጠቀም ባህል የነበራቸው መሆኑ በስፋት ይታወቃል፡፡ በተለይም ታጋዮቹ ለየት ያለ ተልዕኮ በሚፈጽሙበት ወቅት በሚስጢር ስም እንዲጠቀሙ ይደረጋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጀብሃና ሻዕቢያ ዘንድ ታጋዩን በቅጽል ስም መጥራት በጣም የተለመደ ነው፡፡ ለምሳሌ የጀብሃው “መሐመድ ቺክኒ”፣ የሻዕቢያዎቹ “ወልደ ዲንክል”፣ “ተክላይ አደን”፣ “ሀይሌ ጀብሀ” ይጠቀሳሉ፡፡ “የማነ ጃማይካ” የሚባለው የህወሐት ታጋይም ከሻዕቢያ ይዞት በመጣው ቅጽል ነው የሚታወቀው፡፡
2. ህወሐት
ህወሐት በትግል ስም የመጠቀም ሰፊ ልማድ አለው፡፡ በትጥቅ ትግሉ ዘመን ፓርቲው እያንዳንዱ ታጋይ በትግል ስም እንዲጠቀም ያደርግ ነበር፡፡ እነዚያ ታጋዮች ከትጥቅ ትግሉ ፍጻሜ በኋላም በትግል ስማቸው መጠራታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በዚህ ረገድ ከፓርቲው የተገለሉትም በፓርቲው ውስጥ ያሉት ተመሳሳይ መንገድ እየተከተሉ ነው፡፡
ህወሐቶች የትግል ስም የሚመርጡት ስማቸውን ሙሉ በሙሉ በመቀየር አይደለም፡፡ የታጋዩ የልደት ስም ብቻ ነው የሚለወጠው እንጂ የአባቱ ስም አይቀየርም፡፡ ከታዋቂ የህወሐት ሰዎች መካከል የሚከተሉትን ከትግል ስማቸው ጋር መጥቀስ ይቻላል፡፡
1. እምባዬ መስፍን= ስዩም
2. ዘርዑ ገሠሠ= አግዓዚ
3. መሐሪ ተክሌ= ሙሴ
4. አታክልቲ ጸሐየ= አባይ
5. ዮሐንስ ገ/መድህን= ዋልታ
6. ስዕለ አብርሃ= ስዬ
7. ወልደስላሤ ነጋ= ስብሐት
8. ለገሰ ዜናዊ= መለስ
9. ራስወርቅ ቀጸላ= አታክልቲ
10. አየለ ገሰሰ= ስሁል
11. መሐመድ ዩኑስ= ሳሞራ
12. ዮሐንስ እቁባይ= አርከበ
ህወሐቶችም እንደ ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን በቅጽል ስም የመጥራት ልማድም አላቸው፡፡ ለምሳሌ ከህወሐት ታጋዮች የሚበዙት ሙሉጌታ ገ/ህይወትን “ጫልቱ”፣ ሰለሞን ተስፋዬን “ጢሞ”፣ ጄኔራል አበበ ተክለ ሀይማኖትን “ጀቤ”፣ ጄኔራል አብርሃ ወልደማሪያምን “ኳርተር”፣ ካሳ ገብረመድህንን “ሸሪፎ”፣ አብረሃ ታደሰን “መጅሙእ”፣ ጸጋይ በርሄን “ሀለቃ”፣ ጄኔራል ታደሰ በርሄን “ጋውና” እያሉ ነው የሚጠሩት፡፡ ግንቦት 20/1983 ከአዲስ አበባ ሬድዮ ጣቢያ “የዘመናት የህዝብ ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሰራዊት…” በማለት ያወጀውን ታጋይ በእውነተኛ ስሙ የሚያውቁት ጥቂቶች ናቸው፡፡ የታጋዩ ቅጽል ስም “ላውንቸር” ስለመሆኑ ግን ብዙዎቻችን እናውቃለን፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ህወሐትና ሻዕቢያ ታጋዮቻቸውን “ወዲ እገሌ” (የእገሌ ልጅ) እያሉ በሰሜናዊው ባህል መጥራትን ያዘወትራሉ፡፡ በኦፊሴላዊ ደብዳቤ እንኳ “ወዲ እገሌ” የሚለውን ልማድ ሲጠቀሙ ይስተዋላል (በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ይፋ የሆኑትን የአቶ ኢሳያስና የአቶ መለስን ደብዳቤዎች አስታውሷቸው)፡፡
3. መኢሶን
የመኢሶን ሰዎች በትግል ላይ በነበሩበት ወቅት በልደት ስማቸው ነው የሚጠቀሙት፡፡ ሆኖም ከዋነኛ ስማቸው በተጨማሪ በሚስጢር ስምም ይገለገሉ እንደነበር ከልዩ ልዩ ሰነዶች የተገኘው መረጃ ያረጋግጣል፡፡ በዚህ መሰረት የመኢሶን መስራቾች ከሚታወቁበት የሚስጢር ስሞች የሚከተሉት ይጠቀሳሉ፡፡
a. ሀይሌ ፊዳ= መላኩ
b. ነገደ ጎበዜ= ነጋልኝ
c. አብዱላሂ ዩሱፍ= አደም
d. አንዳርጋቸው አሰግድ= ወልዴ
e. ፍቅሬ መርዕድ= ሳሙኤል
f. ከበደ መንገሻ= ነጋ
g. ሲሳይ ታከለ= አሸናፊ
h. ንግስት አዳነ= አይዳ
i. ተረፈ ወልደጻዲቅ= ሚካኤል
ታዲያ እነዚህ ስሞች ሚስጢራዊ ደብዳቤ በሚጻፍበት ወቅት ወይም ሚስጢራዊ ስብሰባ በሚካሄድበት ጊዜ ብቻ ነው የሚያገለግሉት፡፡ መኢሶኖች በመታወቂያም ሆነ በፓስፖርት የሚገለገሉት በዋነኛ ስማቸው ነው እንጂ በሚስጢር ስም አይደለም፡፡
4. ኢህአፓ
ኢህአፓዎችም በትግል ላይ ሳሉ ዋነኛ ስማቸውን በመተው በፓርቲው በሚሰጣቸው ስም ይገለገሉ ነበር፡፡ ፓርቲውን ወክለው በሚገኙበት መድረክ ሁሉ በዚያው ስም ነበር የሚጠቀሙት፡፡ ለተጋዮቹ የትግል ስም የሚሰጥበት ዘይቤ አንድ ወጥ አይደለም፡፡ አንዳንድ ታጋዮች የልደት ስማቸውን ብቻ ይለውጡና ሌላ ቅጥያ ሳያስከትሉበት በዚያው ይጠራሉ (ለምሳሌ “ጋይም” እና አያልነሽን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ አንዳንዶች ግን የአባታቸውን ስም ጭምር ይለውጣሉ፡፡ ከዚህ ሌላም ብዙዎቹ የኢህአፓ ታጋዮች ከትግሉ ዓለም ከተገለሉ በኋላ ወደ ቀድሞ ስማቸው ሲመለሱ ይታያል፡፡ ከኢህአፓ አባላት የትግል ስሞች የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
a. ክፍሉ ታደሰ= ታዬ አስራት
b. መላኩ ተገኝ= ያፌት
c. ገብረ እግዚአብሄር ወልደሚካኤል= ጋይም
d. የዓለም ገዥ ከበደ= አያልነሽ
e. መርሻ ዮሴፍ= በላይነህ ንጋቱ
በነገራችን ላይ ድሮ የኢህአፓ ታጋዮች የነበሩት የአሁኖቹ የኢህዴን/ብአዴን ዋነኛ ባለስልጣናት በትግል ስማቸው ነው የሚጠሩት፡፡ እንደምሳሌም መብራቱ ገ/ህይወት (በረከት ስምኦን)እና ፍቅሩ ዮሴፍን (ህላዌ ዮሴፍ) መጥቀስ ይቻላል፡፡ ጌታቸው ጀቤሳ በበኩሉ ለረጅም ጊዜ በትግል ስሙ ሲጠቀም ከቆየ በኋላ ከኢህዴን ሲወጣ “ያሬድ ጥበቡ” የተሰኘውን እውነተኛ ስሙን መጠቀምን መርጧል፡፡
5. ኦነግ
ከላይ የጠቀስኳቸው ድርጅቶች የትግል ስምን በስራ ላይ የሚያውሉበት ዋነኛ ምክንያት የታጋዮቻቸውን ደህንነት ለማስጠበቅ በሚል ነው፡፡ በተለይም ታጋዩ በተወለደበት አካባቢ ለውጊያም ሆነ ለሌላ ተልዕኮ የሚሰማራ ከሆነ በዋነኛ ስሙ ቢጠቀም ህይወቱ አደጋ ላይ ይወድቃል ተብሎ ስለሚታመን ነው በትግል ስም እንዲጠቀም ሲደረግ የነበረው፡፡ በተጨማሪም ታጋዩ በትግል ስም ቢጠቀም በወላጆቹና በሌሎች ዘመዶቹ ላይ አደጋ እንዳይደርስባቸው ለመከላከል ይረዳል የሚል ምክንያት ከድርጅቶቹ ይቀርብ ነበር፡፡
የኦነግ ባህል ግን ከዚህ ይለያል፡፡ በዚህ ድርጅት ውስጥ ያለ ታጋይ የትግል ስም እንዲጠቀም የሚደረገው በዋነኛነት ለታጋዩ ደህንነት ተብሎ አይደለም፡፡ ከታጋዩ ደህንነት በላይ ለድርጅቱ አንድነት ጠቃሚ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ የኦነግ ሰዎች ታጋዮቻቸው በትግል ስማቸው ቢጠቀሙ ሀይማኖትና ክፍለሀገርን አስታክኮ የሚመጣ መከፋፈልን ለመከላከል ይረዳል በማለት ያምናሉ፡፡ አንድን ታጋይ በስሙ ብቻ ተለይቶ ጥቃት እንዳይደርስበት ለመታደግም ጠቃሚ ነው በማለት ያስረዳሉ፡፡
በዚህም መሰረት የኦሮሞ ስም የሌለው ታጋይ (አሕመድ፣ አብደላ፣ አበበ፣ ከበደ ወዘተ… በመሳሰሉት የሚጠራ) ወደ ድርጅቱ ሲመጣ ቀዳሚ ስሙን ይተውና በኦሮሞ ስም እንዲጠራ ይደረጋል፡፡ የታጋዩ የአባት ስም ኦሮምኛ ካልሆነ እርሱንም ይቀይራል፡፡ ታዲያ ታጋዩ የአባቱን ስም የሚመርጠው በዘፈቀደ አይደለም፡፡ የዘረግ ሀረጉን ወደላይ ሲቆጥር መጀመሪያ የሚመጣበትን የኦሮሞ ስም (የኦሮሞ ስም ያለው ቅመ-አያት የሚጠራበትን) ነው እንደ አባቱ ስም የሚገለገልበት፡፡ የአባቱ ስም ኦሮምኛ ከሆነ (ለምሳሌ እንደ ዮሐንስ ለታ) የራሱን ስም ብቻ ነው የሚቀይረው፡፡ ታጋዩ ይዞት የመጣው ሰው ሙሉ በሙሉ ኦሮምኛ ከሆነ ግን በስሙ ላይ የሚደረግ ለውጥ የለም (እንደ ምሳሌም ባሮ ቱምሳ፣ ኢብሳ ጉተማ፣ አባቢያ አባጆብር የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ ሆኖም ጥቂት የኦነግ ሰዎች ይህንን ልማድ አልተከተሉም፡፡ ከዚህ አሰራር ጋር በማይጣጣም መንገድ ነው የትግል ስማቸውን የመረጡት፡፡ እንደ ምሳሌም በተከታታይ የኦነግ ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡትን በሪሶ ዋቤ፣ ገላሳ ዲልቦ እና ዳውድ ኢብሳን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ድርጅቱን ከውጪ ሀገር የተቀላቀሉትም እንደ አዲስ የትግል ስም ሲሰጣቸው አይታይም (ለምሳሌ ጣሃ አብዲ፣ በያን አሶባ ወዘተ.. ይጠቀሳሉ)፡፡ ከታዋቂ የኦነግ ሰዎች መካከል የጥቂቶቹ የትግል ስም እንደሚከተለው ነው፡፡
a. አብዱልከሪም ኢብራሂም= ጃራ አባገዳ (ከኦነግ በልዩነት ወጥቶ “የኦሮሞ እስላማዊ ነጻነት ግንባር” የተሰኘውን ድርጅት ቢመሰርትም ከኦነግ መስራቾችም አንዱ ነበር)
b. መገርሳ በሪ= በሪሶ ዋቤ
c. ዮሐንስ በንቲ= ገላሳ ዲልቦ
d. ፍሬው ኢብሳ= ዳውድ ኢብሳ
e. ቃሲም ሑሴን= ነዲ ገመዳ
f. ዮሐንስ ለታ= ሌንጮ ለታ
g. አብረሃም ለታ= አባ ጫላ ለታ
h. ዮሐንስ ኖጎ= ዲማ ኖጎ
i. አብዱልፈታህ ሙሳ= ቡልቱም ቢዮ
j. ጀማል ሮበሌ= ጉተማ ሀዋስ
————-
ስለትግል ስም ይህንን ጽፌአለሁ፡፡ የተረሳ ነገር ካለ እናንተ ልትጨምሩበት ትችላላችሁ፡፡ የተሳሳተውንም ማስተካከል መብታችሁ ነው፡፡
*****
ታህሳስ 11/2006
አፈንዲ ሙተቂ

 https://www.goolgule.com/nom-de-guerre/

No comments:

Post a Comment