Monday, December 16, 2013

አይ አበሻ! አበሻና ልመና፦ አንድ (ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም )

በዓለም ሕዝቦች መሀከል ውድድር ቢደረግ ያለጥርጥር አበሻ አንደኛ ከሚወጣባቸው ነገሮች አንዱ ልመና ሳይሆን አይቀርም፤ ለአበሻ፣ ልመና የኑሮ ዘዴ ነው፤ እንዲያውም ከልመና ውጭ የሆነ ኢትዮጵያዊ ኑሮ የለም ለማለት የሚቻል ይመስለኛል፤ ስለዚህም ልመና ባህላዊ ጥበብ ሆኖአል፤ አንዳንድ አላዋቂዎች፣ አንዳንድ አዋቂዎችም አንዳንዴ እየተሳሳቱ ልመናን እንደነውር ይገልጹታል፤ ልመና ነውር አይደለም፤ ለጨዋ ልጆችማ አንዳንድ አጥንትን የሚያበላሽ ሥራ ከመሥራት ለምኖ መብላት ክብር ነው፤ ይህ ባህላዊ ጥበብ ያልገባቸው የድሬ ዳዋ ለማኞች ብቻ ናቸው፤ እጃቸውን እየዘረጉ ‹‹እስቲ አሥር ብር ስጠኝ!›› ይላሉ! በጫት ሞቅ ሲላቸው መቶ ብር ይጠይቃሉ፤ የድሬ ዳዋ ልመና መሆኑ ነው!
Prof. Mesfin Woldemariam
Prof. Mesfin Woldemariam
የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ቄሶቹ ምንም ይስበኩ በተግባር እንደሚታየው ጽድቅ የሚገኘው በልመና ነው እንጂ በሥራ አይደለም፤ ሥራኮ ለአበሻ ከእርግማን የመጣ ነው፤ አበሻ አልተረገመ፤ ታዲያ ለምን ብሎ ይሥራ! አሁን እንደሚሰማውና እንደሚመስለኝ አገዛዙም እንደተቀበለው የቻይና ሰዎችም እንደመሰከሩለት ከሥራ ጋር ጠብ አለው፤ ደግሞስ ለምን ይሥራ! ለአንድ እንጀራ? ለተራበ አብልተው ለመጽደቅ የሚፈልጉ ስንትና ስንት ሰዎች አሉ፤ ስለዚህም ደግ ሰዎች መጽውተው እንዲጸድቁ በግድ ለማኞች ያስፈልጋሉ፤ ለመጽደቅም መለመን ያስፈልጋል፤ ጸሎት ልመና መሆኑን አትርሱ፤ ስለዚህም ዋናውና ከፍተኛው ልመና ወደእግዚአብሔር ነው፤ ብልጦቹ እግዚአብሔርን የሚለምኑት ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት ነው፤ አንድ ቀን ተነሥተው እግዚአብሔር ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት እንደሰጣቸው ያውጃሉ፤ አውጀውም በሕዝብ ራስ ላይ ይወጣሉ፤ በራሱ ላይ ወጥተውም ይጨፍራሉ፤ ሰውን ከመሬቱ፣ መሬቱን ከሰው መለየት ይሳናቸዋል፤ ሰውን ከመሬቱ፣ መሬቱን ከሰው ያጣላሉ፤ እግዚአብሔር ለእናንተ ብቻ እንዴት ሰጣችሁ? እግዚአብሔር እኛን ለምን ነፈገን? ብሎ የሚጠይቃቸውን እየደበደቡና እያቃጠሉ፣ እየገረፉና እያራቆቱ በዝምታ እንዲገዛ ያደርጉታል፤ አልበቃው ካለም አካሉን ለውሻ ሰጥተው ነፍሱን ወደእግዚአብሔር ይወረውራሉ፤ እግዚአብሔር እየቆጠረ የማይመዘግብ ይመስላቸዋል፤ የጠጠረ ጉልበታቸው ዓይኖቻቸውን አውሮ፣ ኅሊናቸውን አፍኖ እግዚአብሔር በዕዳ እንደሚይዛቸውና በጥጋባቸው ያደሉትን መከራና ስቃይ፣ የወረደውን እንባና ደም ከነወለዱ እንደሚያስከፍላቸው መገንዘብ ያቅታቸዋል።
እግዚአብሔር ፍርዱን እስቲሰጥ ድረስ ሥልጣን፣ ሀብትና ጉልበት ተረክበናል የሚሉት የተለያዩ ስሞችን እየለጠፉ በተዋረድ የለማኞችን ሠራዊት ያደራጃሉ፤ ሕዝብ ሁሉ ከነዚህ የለማኞች ሠራዊት በአንዱ ውስጥ ለመግባት በፉክክር ይተላለቃል፤ ሠራዊቱ ውስጥ በመግባት የሚገኘው ጉርሻ ልጆቻቸውን እንኳን ከረሀብ የማያድን መሆኑን ሳይገነዘቡ መብታቸውን እያስረገጡ የሌሎችን መብት ለመርገጥ መሣሪያ ይሆናሉ፤ እነዚህ እንግዲህ ልመናን በማኅበረሰቡ ውስጥ ተክለው እየኮተኮቱ የሚያስፋፉት ናቸው፤ ልመናን ባህል የሚያደርጉት እነዚህ ናቸው፤ ልመናን ታሪካችን ያደረጉት እነዚህና ከነሱ የቀደሙት ገዢዎቻችን ናቸው።
በእኛ ባህል የራበውን በማብላት ጽድቅ ይገኛል፤ ስለዚህም ለምኖ መብላት ይቻላል፤ ስለዚህም ሰዎች መጽውተው እንዲጸድቁ በግድ ለማኞች ያስፈልጋሉ፤ እንግዲህ ለምነው እየበሉ መኖር ከተቻለና እግዚአብሔርን በመለመን ጽድቅ ከተገኘ፣ የመሬቱንና የሰማዩን ጣጣ በልመና መገላገል ከተቻለ ታዲያ ሥራ ለምን ያስፈልጋል! ለነገሩስ ሥራ በእርግማን የመጣ ነው፤ ስለዚህ የተረገሙት ሲሠሩ ያልተረገሙ የሚመስላቸው ይለምኑ፤ ለሌላው ዓለም ልመና የችግር ምልክት ነው፤ ለአበሻ ግን ልመና የጽድቅ ምልክት ነው፤ የጨዋ ልጅ፣ ማለት በልመና በሰዎች ላይ ሥልጣንን ከአግዚአብሔር አግኝቻለሁ ብሎ የሚያምን፣ አይሠራም፤ ቀን ቢጥለውም የጨዋ ልጅ በእጁ ሠርቶ ከሚበላ ለምኖ ቢበላ ይሻለዋል፤ ሆድ የተፈጥሮ ነው፤ ረሀብም የዕለት ከዕለት የተፈጥሮ ግዳጅ ነው፤ ስለዚህም ለአበሻ የተፈጥሮን ሆድና የተፈጥሮን ረሀብ በልመና መወጣት የተፈጥሮን ሥርዓት መከተል መስሎ ይታየዋል።
ሌላ ቀርቶ ተማሪ ለምኖ ካልበላ ትምህርት አይገባውም፤ ለተማሪ ሲሆን ልመና አይባልም፤ ቀፈፋ ነው፤ አበሻ በልመና ምን ይህል እንደተራቀቀ የሚያመለክተው ለተለያዩ ልመናዎች የተለያዩ ስሞች ማውጣቱ ነው፤ እንደተባለው ተማሪ ሲለምን ቀፈፋ ነው፤ በዘመናዊ ቋንቋ የትምህርት ታክስ ነው፤ ምግብ የሚቀርብበትን ሰዓት እየጠበቀ ከተፍ የሚለው ቀላዋጭ ነው፤ አብዛኛውን ጊዜ ለቀላዋጭ ቀላል ሰበብ የሚሆነው ቀላውጦ የሚያገኘው ወሬ ነው፤ ሌላም የልመና ዓይነት አለ፤ እርጥባን ይባላል፤ — ደርቄአለሁና አርጥቡኝ ማለት ነው! ‹ላሊበላዎች› የሚባሉት ለምነን ካልበላን እንቆመጣለን በማለት ልመናን የኑሮ መሠረት አድርገውታል፤ ሌላም የልመና ዘር አለ፤ ደጅ መጥናት ይባላል፤ ደጅ መጥናት ማለት ብርዱን ችሎና እንቅልፉን አቋርጦ በሌሊት እየተነሡ በመኳንንቱና በመሳፍንቱ፣ በንጉሡ፣ በንጉሠ ነገሥቱ ደጃፍ ላይ አጥር ወይም ዛፍ እየተደገፉ የተፈለገውም ሰው ብቅ ሲል በመሬት ላይ በመነጠፍ እጅ በመንሣት ፊት ለማስወጋት ለመታወቅና ለሹመት ለመታጨት የሚጠቅም የልመና ዘዴ ነው፡፡ በአበሻ አገር ሁሉም ነገር በልመና ነው፤ ምግብ በልመና፣ ትምህርት በልመና፣ መሬት በልመና፣ … በልመና፣ ግብር የሚከፈለው በልመና ነው፤ ሥልጣን የሚገኘው በልመና ነው፤ ንጉሥነትም የሚገኘው በልመና ነው፤ ባጭሩ ኑሮ ማለት ልመና ነው፤ ልመና ማለት ኑሮ

No comments:

Post a Comment