Wednesday, December 25, 2013

ሰላም ለአቶ አበራ የማነዓብ

ታደለ መኩሪያ
Ethiopian political prisoner Abera Yemaneab
አበራ የማነአብ
አቶ አበራ የማነዓብን ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት በበጋው እ ኤ አ በ1990 ዓ ም ካናዳ ቶሮንቶ ከተማ ነበር። ስለ ኢትዮጵያ ዲሞክራሲ ኃይሎች ቅንጅት (ኢዲኃ ቅ)  ዓለማውን አስመልክቶ ለቶሮንቶ ኗሪ ኢትዮጵያውያን ማሕበረሰብ  ማብራሪያ እንዲሰጥ ተጋብዞ  በመጣበት ወቅት ነበር። ከጉዞው ወደ ሰብሰባው አዳራሽ በቀጥታ የመጣ ይመስላል፤ ፀጉሩ አልተበጠረም፤ በትከሻው ላይ ያላወረደው ሸክም እንዳለ ያመለክታል፤ ከጉልጓሎ ወይም ከአጨዳ የመጣ ታታሪ ገበሬ አስመስሎታል፤  በግርድፉ እንደምንገምተው በከፍተኛ የትምህርት እውቀት ተገርቶ የወጣ አይመስልም፤ ወይም የከፍተኛ የቢሮክራሲው ማሕበረሰብ ክፍል አይመስልም። ከስብሰባው አካባቢ ከሀገር የወጣው በሱማሌያ በኩል ነው የሚል ጭምጭምታ ሰለሰማሁ እኔም በዚያ አቅጣጫ የወጣሁ ስለነበር ሰለዚያ አካባቢ ሁኔታ ራሴ በግል ያሳተምኳትን  መጽሐፌን አበረከትኩለት፤ ከዚያ በኋላግን አላየሁትም።
በኢትዮጵያውያን አቆጣጠር 1986 ዓ ም ለዲሞክራሲ አማራጭ ኃይሎች ሰብሰባ ከዋሽንግተን ዲሲ ወደ አዲስ አበባ ሄዶ ቦሌ አይሮፕላን ማረፊያ ተይዞ ወህኒ መውረዱን ሰማሁ። በ1997 ዓ ም ለጥቂት ቀናት ተለቆ ተመልሶ መታሰሩንም  በድሕረ ገጾች አነበብኩ። የተፈታበትን ቀን ዕርግጠኛ  ባለውቅም ሕዳር መጨረሻ 2006 ዓ ም በኢትዮጵያ ሳታላት ትቪ (ኢሳት) ሲሳይ አጌና ቃለ መጠይቅ ሲያደርግለት ሳይ በጣም ተደሰትኩ። ቶሮንቶ ባየሁት ወቅት እንደኔው ጊዜው የፈጠረው የፖለቲካ አቀንቃኝ መስሎኝ ነበር። ለሁለት ጊዜ በተከታተልኩት ቃለ መጠየቆች አቶ አበራ የማነዓብ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ አገፋው ሰው መሆኑን ተረዳሁኝ። በሕይወት መኖሩ የሚያስደስት ነው፤ ከርሱ ልምዶች ብዙ የምንማረው ነገር እንደለ እገምታለሁ። አቶ አበራ የማነዓብ ለመጠይቆቹ መልስ ሲሰጥ ከተጣደ የቡና ጀበና እንፋሎት የመሰለ ሐቅ ገንፍሎ ሲወጣ ፤ የኢሳቱ ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና እባክህ ንገረን የሚል የጉጉት ስሜት በፊቱ ላይ ይነበብ ነበር።
ከአቶ አበራ የማነዓብ ለማወቅ የምፈልጋቸው በዙ ነገሮች አሉ። ይህን ሰል ሌሎቻችሁን  አይመለከትም  ማለቴ አይደለም። ሁላችንም በጋራ ያጣነውና በስደትም በሀገር ውስጥም እንዲመጣ የምንታገልለትን ‘ፍትህ’ የሚለውን ቃል በመልሱ ውስጥ ጠቅሶታል። ከሃያ ዓመት እስራት በኋላ ከ1956 ዓ ም የጀመረውን የፍትህ ፍለጋ ዛሬም በ2006 ዓ ም  አላገኘውም። በዚህ ሳምንት ያረፍት የፍትህ ታጋዩ ታላቁ ሰው ኔልሰን ማንዴላ ኢትዮጵያ ውስጥ ለረጅሙ ትግላቸው ዝግጅት ያደረጉበት ዘመን መሆኑ ነው፤ አበራ የማነዓብም የፍትህ ጥያቄውን የጀመረው። የሚገርመው የኝህን የታላቅ ሰው ሞት ከውጭ ሰምቼ ኢሳትን ከፍቼ ሰበር ዜናውን አዳምጬ  ወደአለፉት ቀናት ፕሮግራሞች አለፍኩኝ። ሲሳይ አጌና  አቶ አበራ የማነዓብን መጠየቅ ሲያደርግለት ከሚያሳየው ላይ አነጣጠርኩኝ።ይህንን ጽሑፍ እንዳቀርብ ያነሣሣኝ ያ ገጠመኝ ነው።
አቶ አበራ የማነዓብ በ1969 ዓ ም እርሱና የቀሩት የመላው ኢትዮጵያ ሶሻሊስት ንቅናቄ በአራት አቅጣጫ ወደ ሕዕቡ መግባታቸውን ገልጾልናል። ወደ ምስራቅ ኢትዮጵያ የሄዱትን በአካልም በዝና የማውቃቸው ነበሩ፤ እነርሱም፤ መገርሳ በሪ በባሌ ያደገ የ ክፍለሃገር ምክትል አስተዳዳሪ የነበረው፣ ዶክተር ባሩ ቱምሳ፣ አቦማ ምትኩ፣ዲማ ነገዎ፣ኡላና የሐረር አካዳሚ ምሩቅ፣ ገላሳ ዲቦና ሌንጮ ለታ የማስታውሳቸው ናቸው። በምዕራብ ኢትዮጵያ በሲዳሞ ክፍለሃገር በኩል መግባታቸውን በ1970 ዓም በሱማሊያ ሬዲዮ ጣቢያ በአማርኛው ፕሮግራም የእሸቱ አራርሶ መጠየቅ ከሰማሁ በኋላ ነበር።እሸቱ አራርሶ በ1969 ዓ ም በሲዳሞ ክፍለሃገር  የሕዝብ ድርጅት አላፊ ነበር። እንግዲህ በደቡብ፣ በደቡብ ምዕራብና ምስራቅ ያሉ ወጣቶች ወደሱማሌያ መሰደድ የጀመሩት  ከ1967 ዓ ም  ስልሳዎቹ ጅንራሎችና ሚኒስትሮች በደርግ  ከተረሸኑ በኋላ ነበር።
ወደ ዋናው ርዕሴ  ልመለስና አቶ አበራ የማነዓብ የሲዳማ አውራጃ አስተዳዳሪ ሳለ፤ መገርሳ በሪ  ደግሞ የባሌ ክፍለ ሃገር ምክትል አስተዳዳሪ ነበር። ኃይለማሪያ ሌንጮ ተቀዳሚ አስተዳዳሪ ነበር። በ1969 ዓ ም መሆኑ ነው ሻለቃ ተፈራ ወልደተሳይ ተቀይሮ ባሌ ሲመጣ፤  ከአቶ አበራ የማነዓብ  እንደሆነው ከመገርሳም ጋር አልተስማሙ ለቆ አዲስ አበባ ገባ። ይህ እንግዲህ 1969 ዓ ም መጀመሪያው ላይ መሆኑ ነው፤ መኢሶን ሕዕቡ የገባው ነሐሴ 1969 ላይ ነበር። ይህንን 1969 ዓ ም ደጋግሜ የምጠቅሰው ሻለቃ ኃይለማሪያም ሌንጮና ሻለቃ ተፈራ ወልደ ተንሳይ የሲዳሞና የባሌውን ክፍለሃገር ሕዝብ በተለይ ወጣቱን አስበርግገው ከሱማሌያ ጉያ  እንደከተቱት ለማሳየት ነው። ምንጊዜም የሃገራችንን ሕዝብ ከሃገሩ እንዲኩበልል የሚያደርጉት መሪ ነን ባዮቹ መሣሪያ የታጠቁት ክፍሎች መሆናቸውን መረዳት አለብን። ባሌ ከደሎ መና ዋቆ ጉቶም  ቀደም ብለው  ሀገር ለቀው ወደሱማሌያ ተሰደዋል፤ እርሳቸውን ይዘው እንግዲህ  የሱማሊያ መንግሥት የሱማሌ አቦ የሚለው ድርጅት አቋቋሞ እርስ በርስ ሊያጫርሰን የተሰማራው። አንዳንድ በቦታው ያልነበሩ በሕዝቡ ውስጥ ምን ይካሄድ እንደነበር የማያውቁ በሰሚ ሰሚ ዋቆ ጉቶን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር መሪ አድርገው ያቀርቧቸዋል።ስለዋቆ ጉቶ ጊዜው ሲፈቅድ ከ1956 ዓ ም እስክ 1970 ዓ ም ያለውን እንዲት ማንኛው ኢትዮጵያዊ አሁን ድረስ የሚጠይቀውን ‘የፍትህ’ ጥያቄ በተለይ ለደሎ ሕዝብ ይጠይቁ እንደነበር በሌላ ጽሑፌ እመለስበታለሁ።  የባሌና የሲዳሞ  ክፍለሃገር ወጣቶች በሱማሊያ አቦ ሰም ታጥቀው በገጠር መሸጉ። በሲዳሞ በኩል ባላውቅም በባሌ በኩል ወደ መደብ ትግል አንለውጠዋለን ብለው የተቀላቀሏቸወን  የኢሕአፓ አባላት በሰላይ ስም  ፈርጀው ገለዋቸዋል።  በሐረርም እንደዚያው በታወቁት የክፍለሃገሩ ኗሪ ሼክ ኢብራሂም ቢሊሳ በሐርጌሳ በኩል በሱማሌ አቦና በኢሰላሚያ ኦሮሚያ  ስም ታጥቀው በምስራቁ ክፍል መሽገው ነበር።የመኢ ሶ ን መሪዎች በሲዳሞ ሕዕቡ ሲገቡ ኦሮሞኛ ተናገሪው ሕዝብ በሱማሌ  አቦ ቁጥጥር ሥር ነበር፤ ሱማሌ አቦ ነን የሚሉትም አብዛኞቹ ኦሮሞ ተናጋሪዎች ሲሆኑ መሪዎቹ ኦሮሞኛ ጉራኛና ሱማሌኛ  የሚናገሩ ግን ሱማሌያ ውስጥ ለብዙ ዓመታት የኖሩ ቆለኞቹ ነበሩ። በኦሮሞና በአማራ መካከል ልዩነት አያደርጉም። የደርግ መንግሥት አባሪ አድርገው ይመለከቷቸዋል። ስለዚህ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር አልነበረም። በሐረር በኩል የገቡት የመኢሶን አባላት የኦሮሞ ተወላጆች ቢሆኑ  ኢስላሚያ ኦሮሚያና ሱማሌያ አቦ በአንደነት የሚቀሳቀሱበት ስለነበር በኦሮሞ ነፃነት ግንባር ስም መሣሪያ ይዘው አንዲት ጥይት  የተኮሰ አልነበረም፤ በመኢሶን፣ በኢሕአፓ እንደዚያው። ሰለዚህ አቶ አበራ የማነዓብ   በወቅቱ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር በሐረር በባሌ በሲደሞ መኖር ያለመኖሩን በዙ ተጨባጭ ሐቆችን ሊያስጨብጠን ይችላል። ስለ እነ መገርሳ በሪ አማሟትም በሕይወት የሚኖሩት አንዲት ነገር ትንፍሽ ሲሉ አይሰማም። በመሬት ላይ የሌሉ ነገሮች እንደነበሩ ተደርገው እየተነገሩ ሕዝቡ ወደ ትልቁ ጠላቱ  ሀገር ከፋፋዩ ወያኔ  እንዳያተኩርና ለፍትህ የሚደረገውን ትግል እንዳይገፋ መሰናክል ሆኖበታል። የሱማሌያ አቦ ታጣቂዎች ወያኔ ሀገሪቱን ተቆጣጥሮ የሽግግር መንግሥት ሲመሰርት ራሰቸው ቀይረው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ነን ሲሉ የኦሮሞ መሑራን ከወያኔ ሽግግር መንግሥት የተካፈሉት  ደግሞ ጦራችን ነው ብለው እርፍ አሉት። ይህን  ሁኔታ በሌላው ጸሑፌ እመለስበታለሁ።
ለዛሬው እኔና  አቶ አበራ የማነዓብ የምንጋራቸው ጉዳዮች ላይ አተኩራለሁ።አቶ አበራ የማነዓብ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች መማክርት ዋና ጸሐፊ በነበረበት 1956 ዓ ም የስደስተኛ ክፍል ተማሪ ነበርኩ።ስለዚህ ስለእርሱ ስገልጽ የእርሱ ወደርተኛ ሆኜ ለመቅረብ እንዳልሆነ አንባቢዎቼ እንዲረዱልኝ እሻለሁ።  እርሱ የሚከተለው የፖለቲካ ድርጅት አባል አይደለሁም። ይልቁንም ‘እርሱ ካልተፈታ አልፈታም’ ካለቺው፤ እርሱም ‘የእኔ እህት ካላት’ ክፍል ነኝ። የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) አባል የሆነችውን ገነትን ነበር ‘የእኔ እህት’ ያላት። በመኢሶንና በኢሕአፓ ስም ጎራ ለይተን ቂምና ጥላቻን በተግባርም በቃልም ስንገልጸው ለኖርነው ያ አቀራረብ የጥላቻን  ግባ ከመሬቱን ያከናወነ ይመስለኛል።
እኔም በኢሕአፓ አባልነት ከአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ ተይዤ ከታሰርኩበት እስር ቤት   1971 ዓ ም የካቲት አምልጬ የተወለድኩበት ክፍለሃገር ባሌ ደሎ መና የዋቆ ጉቱ ሀገር ገባሁ። የሱማሌያ አቦ ታጣቂዎች ከተቆጣጠሩት አካባቢ ከርሜ በ1972 ዓ ም  ዶሎ የሱማሌ ክፍል ዳዋ ወንዝ ላይ ሰፈርን፤ ከአምስት መቶ በላይ ወጣቶች ነበሩ። በምዕራብ በኩል ከሲዳማ ክፍለሃገር የመጡ አቶ አበራ የማነዓብ የጠቀሳቸው አቶ ወልደማኑኤልና ልጆቻቸው እሸቱ አራርሱ እኔ የማውቃቸው  አቶ ይልማ ና አቶ ቁምጣ የሚባል ከክብረመንግሥት አካባቢ ኦሮመኛ ተናጋሪ ነበሩ፤ በመሐል የምንገኘው ደግሞ ከባሌ የመጣናው ስንሆን መሪያችን የዋቆ ጉቶ ምክትል የሆነው አልይ ዑመር ነበር። ዛሬ በስደት ለነደን ይገኛል። በምስራቅ በኩል ከኦጋዴን የመጡ የሠፈሩበት ነበር። አቶ አበራ የማነዓብ ወደቆሮሌ የተወሰደው ከቤተሰብ ጋር ስለነበር ይመስለኛል። አቶ አበራ የማነዓብ ብዙ ግንዛቤ ይኖረዋል ብዬ የማስበው በሲዳማ ነፃ አውጪ ስም ሆነ በ ሱማሌ አቦና በሱማሌ ገልቤድ ወይም ምዕራብ ሱማሌያ ብለው ይቀሳቀሱ የነበሩት ተዋጊዎች ደርግ በፈጠረው የጅምላ  ግድያ ምክንያት የውጪ ጠላቶች የፈጠሯቸው እንጂ  ሀገርን ለማስገንጠል ወይም ለመገንጠል የሚቀሳቀሱ አልነበሩም። ወጣቱም ወደእነዚህ ንቅናቄዎች ሲቀላቀል የወጪዎችን ደባ ለማክሸፍ ነበር። ጥላሁን ግዛው 1961 ዓ ም የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲት ተማሪዎች መማክርት ፕሬዘዳንት ወቅት እሸቱ አራርሶ ዋና ጸሐፊ ነበር። ዶክተር እሸቱ ጮሌ በ1956 ዓ ም የቀደማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቪርሲቲ ፕሬዘዳንት  ሲሆን  አበራ የማነዓብ  ዋና ጸሐፊ ነበር። ስለዚህ  ሕዝቡ ውስጥ የገቡት ሀገራቸውን ለማስገንጠል ነው ብሎ የሚያስብ የለም። በሲዳሞ መስመር እነ ሻለቃ ሰርኔሣ ‘እኔ ኮሩ ኢትዮጵያዊ ኦሮሞ እንጂ ሱማሌ አቦ አይደለሁም በማለቱ በሱማሊያ እስር ቤት ተገሏል፤ እሸቱ አራርሱ  የኢሕአፓ አባል መሆኔን እያወቀ  ከሱማሌው ሴንተራሌ እስር ቤት ለማስፈታት   መጣሩ ከሥር ከተፈታሁ በኋላ ሰምቻለሁ። ሱማሌያ ለቅቄ ከወጣሁ በኋላ በሱማሌያ እስር ቤት አንደ ሻለቃ ሰርኔሣ መገደሉን ተነግሮኛል። ስለዚህ በምስራቅ በኩል ወደሕዝቡ የገቡት የመኢሶን ሆኑ የኢሕአፓ አባላት ሀገር ለመገነጠል ወይም ለማስገንጠል ያለመሆኑን   ከኔ በላይ አቶ አበራ የማነዓብ ሊያውቅ ስለሚችል ከቃለ መጠይቅ ያለፈ በመጽሐፍ መልክ ሊያስተላልፈው የሚችለው ብዙ የማናውቀው ሐቅ ይኖረዋል ብዬ አምናለሁ። በዚህ አጋጣሚ ቤተሰቡ ከርሱ ጋር በሀገርም በባዕድ ሀገርም የደረሰባቸውን እንግልት በቆራጥነት መውጣታቸውን ሣላደንቅ አላልፍም።

 https://ecadforum.com/Amharic/archives/10490/

No comments:

Post a Comment