Saturday, September 14, 2013

ዘመናዊያንን የተገዳደረች የእምነት ፍልስፍና

ዘመናዊያንን የተገዳደረች የእምነት ፍልስፍና
(ከእግዚአብሔር የሆነች ጥበብ)

የዘመናት ባለቤት ልዑል እግዚአብሔር እንኳን ከዘመን ወደ ዘመን አሸጋገራችሁ! ፍልስፍና ከመሠረቱ ጥልቅ ነገሮችን ማስተዋል የምታስችል ልዩ ጥበብ እንጂ በዘመናችን እንደሚታየው
የተደነባበሩ ሐሳቦችን በመጠቀም የሰዎችን ደካማ አእምሮዎች ሸብቦ በመያዝ በደካሞች ላይ የሰለጠነች አልነበረችም፡፡ ከመጀመሪያው ፍልስፍና ከልዑል አምላክ የምትሰጥ ልዩ የማስተዋል ጥበብ ብትሆንም ኋላ ግን ጠላት የራሱን ጥበብ በሰዎች በማሳደር ተንኮለኝነትንና ማሳሳቻዎችን እንደ ፍልስፍና ማስፋፋት ጀመረ፡፡ እየቆየም ፍልስፍና የምትለው ቃል ራሷ በልዑል እግዚአብሔር በሚያምኑ ሰዎች እንደሌለችናየአለማውያን ብቻ ጥበብ ተደርጋ ተተረጎመች፡፡ ዛሬ ያለንውም ከጥቂቶች በስተቀር ፍልስፍና ከአለማዊ ጥበብ ጋር እንጂ ከእግዚአብሔር መንፈሳዊ ጥበብ ጋር የተያያዘች ፍልስፍና እንዳለች አናስተውልም፡፡

እርግጥ ነው ከእግዚአብሔር የሆነችውን የእምነት ፍልስፍና ለመረዳት በራሱ ልዩ ጥበብና የእምነት ኃይል የሚጠይቅ ነው፡፡ ሲጀምር አእምሮአችንን በእኛ በምናውቀው እውቀት ብቻ ገድበን ለጥበብ ነጻነት ሳንሰጥፍልስፍናን ማሰብ ሕልም ነው፡፡ ፍልስፍና ራስን ጨምሮ እግዚአበሔር ከፈጠራቸው ሌሎች እልቆ መሳፍርት የጥልቅ ማስተዋልና አድናቆት ልምምዶች መንገዷ ሊዘረጋ ይችላልና፡፡ ሆኖም ግን አይተን ማስተዋላችን በአጭሩ ተቀጭቶ ይሄ የሆነው በዚህ ምክነያት ነው ብለን ድምዳሜ ስንጀምር የፍልስፍናችን ጉዞ ይቋረጥና አንድ የተዛባ መልዕክትን በማስተላለፍ ሌላውን በመበከልና ብዙ ሊኬድባቸው የሚችሉፍልስፍናዎችንም በእኛው ልክ እናቀጭጫቸዋለን ወይም የተሳሳት አቅጣጫ በማስያዝ ከነጭርሱ የዳሕራዊ እውነትን (Ultimate reality) ተቃራኒ ጉዞ እንጓዛለን፡፡

 በሂደቱ ሊነቃ የሚችል ሌላ ልዩ ፈላስፋ እስከሚመጣ ድረስ ለዘመናት ይሄንንው የስህተት ጉዞ ልንነጉድበት እንችላለን፡፡ ሁሌም የሚገርመው ደግሞ በተሳሳተው አቅጣጫ የሚመሩ ፍልስፍናዎች በብዙዎች ዘንድ የሚኖራቸው ተአማኒነት ከፍተኛ ነው፡፡ ምክነያቱም ቀላልና ለተራው ሁሉ አእምሮ ሳይቀር በሚገቡ ሁኔታ ስላሉ ይመስላል፡፡ ወደ ዳህራዊ እውነታ የሚያመሩት ፍልስፍናዎች ግን አጅግ የጠለቀ ማስተዋልን የሚሸከም አእመሮን ስለሚጠይቁ ለብዙዎች ግልጽ አይደሉም፡፡ ፍልስፍና (በአጠቃላይ አእመሮ) ሰዎች እንደምናስበው በራሳችን ኃይል የሚመራ ሳይሆን በሌላ ኃይል የሚመራ ነው፡፡ ወይ በእግዚአበሔር ወይም በሰይጣን፡፡ ከእግዚአበሔር የሆነችው ወደ ዳህራዊ እውነታ የምታመራው እግዚአብሔርን ለሚያምኑትና በሚያውቁት ሰዎች የምትሰጥ ፍልስፍና ስትሆን ከሰይጣን የምትሆነው ግን ሰይጣንን አወቁትም አላወቁትም እግዚአበሔርን ለማያውቁ ለማወቅም በማይፈልጉ ሰዎች የምትመጣ የማይረባ አእምሮ ውጤት ነች፡፡ የመካን አእምሮ ፍልስፍናዎች በዘመናችን ሙሉ በሙሉ በሚያሰኝ ሁኔታ ፍልስፍናውን የተቆጣጠሩት ከመሆኑ የተነሳ በጣም እጅግ ጥቂት በሚባሉ የዳህራዊ እውነት ጉዞ ፍልስፍናዎች ተቀባይነትን ሊያገኙ አልቻሉም፡፡
 
በመጽሐፍ የሚነበቡት የጥንታዊያኖቹ የነብያት ኋላም የሐዋሪያትና ሰማዕታት የዳህራዊ እውነት እምነት ፍልስፍና ዛሬ ላለነው ዘመናውያን ተረት ተረቶች ናቸው፡፡ የእነዚህ እግዚአበሔርን ለማወቅ የመሻት ፍልስፍና የቱንም ያህል በሕይወታችን ተገልጾ በዓይናችን ብናይም እኛ ለማስተዋል አእመሮአችን በተቃራኒው ኃይል ስለተጋረደ አቅም አጥተናል፡፡ በተቃራኒው የሆኑ ሌሎች ፍልስፍናዎችን (ከተራ ጥንቆላ እስከ ሳይንሳዊ ምናቦች) ግን በቀላሉ እንቀበላለን፡፡ ለምሳሌ በየጋዜጣውና መጽሔቱ የሚወጡ የእድል ጥንቆላ ሥራዎች፤የመዳፍ መስመረ ንባብ፣ የኦሾና ራምፓ የክህደት ፍልሰፍናዎቸ እስከ የዳርዊን የዘገምተኛ ለውጥ ፍልስፍናዎች የቱንም የህል ተጨባጭ ማረጋገጫ እንደሌላቸው ቢታወቅም ተቀባይነታቸው እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በአንጻሩ በአይን የሚታዩት የእግዚአብሔር እምነት ያላቸው ፍልስፍናዎችን ለመቀበል አእምሮአችን እጅግ ይቸገራል፡፡
በዘመናችንና በአገራችን በተግባር የእግዚአበሔርን ኃይልና የክፉ መናፍስትን የተደበቀ ሴራ ያወጣውን የፈላስፋውን (ይህ ለእኔ ልዩ ፍልስፍና ነው) የመምህር (በልአከ መንክራት) ግርማ ወንድሙን አስተምሮትና ፈውስ እንደ አንድ ማሳያ ለአንባብያን ማስተዋልን የሚሰጥ ስለመሰለኝ ላነሳው ፈለግሁ፡፡
 
እኝህ ኢትዩጵያዊ የኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት አባት በዚህ አይነት ጥበብ በቤተክርስቲያኒቱ ብቸኛና የመጀመሪያ ባይሆኑም ለብዙዎቻችን የተደበቀውን ልዩ የእምነት ፍልስፍና ገሃድ በማውጣት እንደ ተረት ከተቀበልንው (ለማመን ከተቸገርንበት) ሌሎች እንደነ ጻድቁ አቡነ ተክለሐይማኖት ታሪክ በኋላ በእኛ ዘመን ሁለተኛው ሰው ሲሆኑ ለዓለም ሳይቀረ በማሳየት ግን የመጀመሪያው ናቸው፡፡ ከመምህር ግርማ በፊት በቤተክርስቲያኒቱ በገሀድ የእግዚአበሔርን ኃይል በማሳየትና የክፉ መናፍስትን ሴራ በማምከን ይታወቁ የነበሩት በብዙዎች የወሊሶው አባ ወልደተንሳይ በመባል የሚታወቁት ኋላም የምዕራብ ሸዋ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት አቡነ ዲዩስቆሮስ ናቸው፡፡ አቡነ ዲዮስቆሮስ ከአንድ ሚሊዮን በላይ በክፉ መናፍስት የተጠቁ ድውያንን (አይነስውሯን የኩዌት ንጉስ ልጅን ጨምሮ) እንደፈወሱ ቢነገርም በወቅቱ የነበረው ክስተቶችን በፎቶና በቪዲዮ የማስቀረት ሥራ እምብዛም ባለመሆኑ መረጃዎችን ለማዳረስ እንደ አሁኑምቹ ባለመሆናቸው ፍልስፍናቸውንም (አስተምህሮታቸውን) የተግባር ሥራዎቻቸውንም እንደልብ ለማየት እድሉ አልገጠመንም፡፡ ከላይ እንደጠቆምኩት እኛ ሰዎች ብናይም እንደነዚህ ያሉ ፍልስፍናዎችንና ተግባሮችን ለመመስከር አቅም ያለን አይደለንም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን እድሜ ለቴክኖሎጂ ሰው ዝም ቢል እንኳን በቪዲዮ የተቀረጹ ፊልሞች ያሳብቁብናል፡፡ የመምህር ግርማም ፍልስፍናና ተግባር በዚህ ቁሳዊ ምስክር እንጂ እንደሰው ቢሆን ገና ሰፈር ውስጥ ብልጭ እንዳለ እዛው ባለበት ሊቀጭ ይችል እንደነበር ለመገመት መምህሩን በዚህ ሥራቸው የገጠሟቸው አስቸጋር ፈተናዎች አብነት ናቸው፡፡

ብዙዎች እግዚአብሔርን በአካል ቢያዩት ሊያምኑት እንደሚችሉ ይገምቱ ይሆናል፡፡ ብናየውም ጭራሽ ኋላ ለመጠየቅ እዳ ይሆንብናል እንጂ ብዙዎቻችን አናምነውም፡፡ እግዚአብሔርን በእግዚአብሔርነቱ (በሙሉ ግርማውና ክብሩ) ለማየት ሲጀምር ለእኛ ሊቻለን የሚችል ጉዳይ አይደለም፡፡ ብዙ ነብያትና ጻድቃን አዩት ቢባልም ለእነሱ በሚቻላቸው ሁኔታ እንጂ እግዚአብሔርን ከቶም ለማየት አይቻልም፡፡ እሱ በወደደው መልክ ሲታየንም ለማየት አእምሮአችን ብቃት ላይኖረው ይችላል፡፡ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው ለዘመናት እንዲጠብቁት አስቀድሞ ተነግሯቸው ሰው ሆኖ ቢመጣ ሥራውን ሁሉ በአይናቸው እያዩ ሊያዩት ያልቻሉት ካህናትና የካህናት አለቆችን ጨምሮ ብዙ ክርስቶስን የተቃወሙት ናቸው፡፡ ዳህራዊ እውነት እግዚአብሔር ነው፡፡ ወደዚህ የምትወስድ ፍልስፍና ደግሞ እጅግ የረቀቀ ማስተዋልንና መሻትን የምትጠይቅ ናት፡፡ በአይን ማየት ለእንደዚህ ያለችቱ ፍልስፍና ለመቀበል ማረጋገጫ ሊሆን አይችልም፡፡

የአእምሮ መከፈት ከሌለ፡፡ ችግሩ ደግሞ እናውቃለን በሚሉ ሰዎች ይበዛል፡፡ እራሳቸውን በእግዚአብሔር ደረጃ ይኮፍሳሉና፡፡ እግዚአብሔር አለም-አለማትን (The entire universe) እንደፈጠረ አነበብንው እንጂ አላስተዋልንውም፡፡ ሳይንስ አለም ከተፈጠረ ጀምሮ ቢሊየን (ቁጥሩ ሳይንስ የሚለው እንጂ ትክክለኛው አይደለም) ዓመታት እንደተቆጠሩ ያምናል፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ብርሃናቸው በሰኮንድ 300000 ኪሎ ሜትር በደቂቃ 18 ሚሊዮን ኪሎሜትር፣ በሰዓት 1.08 ቢሊዮን ኪሎ ሜትር፣ በቀን 64.8 ቢሊዮን ኪ.ሜ. እያለ በዓመት 23,652 ቢሊዮን ኪሎሜትር (ከፀሐይ እስከ መሬት 8 ደቂቃ ብቻ ነው) እየነጎደ እስከዛሬም መሬት ያልደረሰ ብርሃን ያላቸው ከዋክብት ወይም ሌሎች ብርሃናዊ አካላት እንዳሉም ያምናል፡፡ እንግዲህ እግዚአበሔር የእነዚህ ሁሉ ርቀትና አለማት ፈጣሪ ነው! ለዛም ሳይሆን አይቀርም በእሱ ጥበብ የተመሰጡት ፈላስፋዎች የእግዚአብሔርን አኗኗር ለማውቅ የሚችል ምን አእምሮ፣ ምን ፍልስፍና፣ ምን ሐሳብ ነው የሚሉት!!! እግዚአብሔርን ይቅርና በእነዚህ ሁሉ ርቀትና አለማት እንኳን ምን እንዳለ ሳይንስ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ የምድሩን እንኳን የሚያውቀው በጣም ኢምንት በሚባል ደረጃ ነው፡፡

እግዚአብሔር ግን በሥራውና እሱ በፈቀደው የአካል መጠን ቢገለጥም ብዙ ጊዜ ለመቀበል አንችልም፡፡
 
በዚህ ምክንያት እንኳን ለሰማንው እራሳችን በአይናችን ላየንው ነገር ለመመስከር አይቻለንም፡፡ የዘመኑ ሚዲያዎችም አይደፍሩትም፡፡ በተቃራኒው ያለው ፍልስፍና ግን ወሬ ከተሰማ በቂ ነው፡፡ የአለም ዜና ማሰራጫዎች ሳይቀሩ ላልታየው በወሬ ብቻ ለተሰማው እንዲህ ያለው ፍልስፍና ቀዳሚ ዘጋቢ ለመሆን ከፍተኛ እሽቅድምድም ያደርጋሉ፡፡ በተመሳሳይ እኚህ በዘመናችን የተነሱት የእምነት ፈላስፋ መምህር ግርማ የቱንም ያህል የሚናገሩት ሰዎች እናምነዋለን የሚሉትን የክርስትና እምነት ፍልስፍና ቢሆንምና እሳቸው የሚናገሩት ነገር አንዳችም ስህተት እንደሌለበት ቢያውቁም ብዙዎች በተለይም ደግሞ የኦረቶዶክስ እምነት አስተምሮ እናውቃለን በሚሉ ሰዎች ከፍተኛ ፈተና እየገጠማቸው ላለፉት 20 ዓመታት በላይ ትግል ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ ግን ፍልሰፍናቸውን ፊት ለፊት ለማስተባበል የቻለ አንድም የቤተክርስቲያኗም ይሁን ከሌላ እምነት የሆነ ሰውሊቀርብ አልቻለም፡፡ ይልቁንም የኖረ ወግንና ባህልን ከእምነት የቀላቀሉ ስርአቶችን እንደ መቃወሚያ
ስልት በመፍጠር በአሉባልታና በሰፈር ሀሜቶች በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት እንዳያገኙ መምህሩን
የሚፈታተኗቸው እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡ ብዙ ጊዜም ጭራሽ ባልተፈጠሩ ባልተሰሙ የፈጠራ የውሸት
ወሬዎችና ክሶች፡፡ እንደነዚህ ወሬዎች መምህሩ ብዙ ጊዜ ታስረዋል፣ ታግደዋል፣ ብዙም ጊዜም ተከሰው ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ ግን በመምህሩ አንዴም አልተፈጸሙም፡፡ አሁን በቅርቡ በግል ጥቅም ፍላጎት ሳቢያ በተፈጠረ መሰሪ ሴራ ያገለግሉበት ከነበረ አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ከሚገኘው የቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን በጉልበተኞች፣ በዘመኑ የቤተክርስቲያኒቱ ባለስልጣኖችና አባሮቻቸው መታገዳቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ በይፋ ከመጻፉ ውጭ በሁሉም ደብሮች አገልግሎት ሲጅምሩም ተጋብዘው ነው ሲተውትም በራሳቸው ፍቃድ በአንዳንድ የደብር አስተዳዳሪዎች ደስተኛ ባለመሆናቸው ነው፡፡

 በእስጢፋኖስም ከቀድሞው አስተዳዳሪ ጋር ጥሩ መግባባት ስለነበራቸው ጥሩ የአገልግሎት ሥርዓት
(ከሕዝብ የሚሰበሰብን ገንዘብ በአግባቡ ለደብሩ በማስገባት ጨምሮ) ስለተመሠረተና ለሕዝብም ማዕከል ከመሆኑ ጋር ምቹ ቦታ ስለነበር እንጂ በኋላ በመጣው አስተዳደር ደስተኛ አልነበሩም፡፡ በሕዝብ ግፊት እዛ ቆዩ እንጂ ብዙ ጊዜ ከዛ ቦታ ወደሌላ ሰላማዊ ደብር መሄድ እንዳለባቸው በጉባዔ ሳይቀር አስቀድመው ሲናገሩት የነበረ ጉዳይ ነበር፡፡ ሆኖም ሕዝብና ብዙዎቹ የደብሩ ካህናት (ለደብሩ የእሳቸው ጉባዔ ወሳኝ ነበር) ሁኔታዎችን እንደሚያስተካክሉ ቃል ስለተገባላቸው ነበር እዛ የቆዩት፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ በጥቅም ያኮረፉት የደብሩ አስተዳዳሪና አባሮቻቸው አግደናል ብለው ጻፉ ለመምህሩም ጥሩ አጋጣሚ ሆነ ምንም እንኳን የደብሩ ካሕናትና (ደሞዝ ሳይቀር የሚከፈለው ከመምህሩ ጉባዔ ከሚገኝ ገቢ ነው) ሕዝብ (ማዕከል ነው) ቢጎዱም፡፡ ይህንን አጋጣሚ ግን ሌሎች ደብራት ጊዜ አልሰጡትም የመምህሩ ምርጫ ቀድሞም በየወሩ ሲያገልግሉበት የነበረው ምንም ሕዝብ የሌለው ልዩ ታሪክ እንዳለው የሚነገርለት የየርር ጽረሐአርያም ስላሴ ቢሆንም፡፡

የመምህሩን ድንቅ የእምነት ፍልሰፍናና በተግባር የእግዚአበሔርን ኃይል የማሳየትና የእርኩሳን መናፍስትን ሴራ የማክሸፍ ሥራ ለሕዝብ ለማድረስ ብቸኛና ደፋር ሆኖ የተገኘው የብዙሃን ማሰራጫ አሜሪካን አገር የሚገኘው ንብረትነቱ አቶ አያልቅበት ተሾመ የሚባል ሰው የሆነው የአቢሲኒያ ሬድዩ ብቻ ነበር አሁንምነው፡፡ የመምህሩን በልዩ ሴራ ከእስጢፋኖስ ቤተክርስቲያን መታገድ ለመዘገብ እንደ ታላቅ ምስራች የዛመቱት ሚዲያዎች ግን አጅግ ብዙ ነበሩ፡፡ ይባስ አሳፋሪነቱ ደግሞ አብዛኞቹ የቤተክርስቲያን ነን የሚሉ ሚዲያዎች መሆናቸውና ባልታረሙና ለሕዝብ በማይመጥኑ በወረዱ ቃላቶች መዘገባቸው ነው፡፡ ይህ አጋጣሚ የብዙዎችን ማንናት ያጋለጠ በመሆኑ ለሕዝብም ጠቅሟል፡፡ ሚዲያዎቹ ግን ራሳቸውን እንዴት እንደታዘቡ ቢነግሩን ጥሩ ነበር፡፡ ከሕዝብ የደረሳቸው ትችት ቢጠቀሙበት ጥሩ አስተማሪያቸው ነው፡፡

አጋጣሚው የቤተክርስቲያኒቱ ሲኖዶስ ሳይቀር እንዲፈተነበት የሆነ ነበር፡፡ ብዙዎቹም የሲኖዶሱ አባላት የመምህሩን ድንቅ ጥበብ በስብሰባቸው ሊመሰክሩ የተገደዱበት፡፡ አሁን የሚያገለግሉበት ደብር አስተዳዳሪ በስብሰባው ተካፍለው እጅግ የተደመሙበትና የተደሰቱበት፡፡ ጳጳሳቶቹ መምህሩን የሚመለከቷቸው እንደ ቤተክርስቲያኒቱ ብርቅዬ ልጅ እንጂ ሌሎች እንደሚያነሾካሹኩት ሀሜት እንዳልሆነ በግልጽ በስብሰባው ስለተነገራቸው፡፡ ምክነያቱም ከአንዳንድ ሰዎች ለምን ፈቀድህ የሚል የስልክ ጥሪ ይደርሳቸው ነበርና፡፡

ከላይ እንደጠቆምኩት እንደነዚህ ያሉ ፍልስፍናዎች በመገናኛ ብዙሀን አይደፈሬ ከመሆናቸው አንጻር
የአቢሲኒያ ሬድዮ በተቀዳሚነት ያሳየው መነሳሳትና ድፍረት አጅግ የሚያስደንቀው ነው፡፡ ሊያውም ሙሉ ወጭውን ራሱ ሬዲዎው ሸፍኖ የአየር ሰዓት ውድ በሆነበት አገር፡፡ ይህ ሬድዮ የመምህሩን ፍልስፍና (የሀይማኖት ትምህርት) ለአለም በማሰራጨቱ በየአህጉራቱ ያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የአማርኛ ቋንቋ አደማጮች (በየትኛውም እምነት ያሉ) የመምህሩን ትምህርት በመከታተል ከፍተኛ ጥቅም እዲያገኙአድርጓል፡፡ በሬዲዮ የሰሙትንም በአካል ለማየትና ከአገልግሎቱም ተጠቃሚ ለመሆን ከየአህጉራቱ ወደ ኢትዮጵያ ብዙ ሕዝብ እየመጣ ይገኛል፡፡ በቅርቡ ደግሞ የኢቢኤስ ቴልቪዥን ሁለተኛው በመሆን የመምህሩን ትምህርት ጅምሯል፡፡ ምንአልባትም በፊልም የተደገፉ ሌሎች ሥራዎች ሊያቀርብ ይችላል፡፡

እነዚህ ሁለት ሚዲያዎች በዚህ ረገድ የታደሉ የሚያሰኛቸው ተግባር ለማከናወን ፊትአወራሪ ሆኑ ማለት ነው፡፡ ምን አልባት ከዚህ በኋላ ብዙ ሚዲያዎች መምህሩን ለማግኘት በር የሚያንኳኩ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

ልክ ዛሬ ብዙ ደብሮች እንደሚፈልጓቸው፡፡ ደብራቶቹ መምህሩን በአብዛኛው የሚፈልጓቸው
የሚያስገኙላቸውን የገንዘብ ገቢ ታሳቢ አድርገው እንጂ እውንም የመምህሩን ልዩ ሀይማኖታዊ
ፍልስፍና(ትምህርት)ና በተሰጣቸው ጸጋ ለሕዝብ የሚሰጡትን የፈውስ አገልግሎት አስበው አይመስልም፡፡ በመሆኑም መምህሩ ጥቂት በቅንነት ለጋበዟቸውና እግረመንገዱንም ችግር ላለባቸው ደብራት የበረከት ገንዘብ ለማሰባሰብ ካልሆነ ለብዙ ግብዣዎች ፍላጎት ያላቸው አይመስልም፡፡ በዚህ አጋጣሚ አሁን የሚያገለግሉበት የየረር ስላሴ ቅንነት የተሞላበት አገልግሎታቸውን የሚያግዝ አሰራር ቢኖርም ከሚገባው ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ ገቢ ጋር በተያያዘ እየቆየ ችግር እንዳይፈጠር ቢታሰብበትና ሰዎች በገንዘብ እንዳይታለሉ ጥንቃቄ ቢደረግ ጥሩ ይመስለኛል፡፡ ይህ ደብር በፊት ምንም ያልነበረው ሲሆን አሁን በየሳምንቱ የሚገባው የአገሪቱ ብር በተጨማሪ በርካታ የዶላር፣ ዩሮ እንዲሁም የተለያዩ አገራት ገነዘብ የሚገባበት ሆኗል፡፡ ምንአልባትም እስጥፋኖስ ይገባ ከነበረው በላይ፡፡ ከአንድ ግለሰብ እስከ አስር ሺ መስጠት የተለመደ ነው፡፡ ሰው እዛ የሚያገኘውን የፈውስና የተለያዩ የኑሮ አክሎች መላቀቅን በገንዘብ ቢገመት ብዙ እንደሆነ በአብዛኛውም በየትኛውም የገንዘብ ኃይል የማያገኘው ድህነት ስለሆነ ለመስጠት ወደኋላ አይልም፡፡ አንዳንዱም ምንም የማያውቀው ሰው እንኳን ድኖ ስላየ በደስታ የሚሰጠው ነው፡፡

ወደ ተነሳሁበት ፅሑፍ መደምደሚያ ልምጣና አሁን ላይ ሆኜ ሳስብ (ድሮ እንዲህ ለማሰብ እቸገር ነበርና) የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው የሚለው ምክር ዘልማዳዊ አድርገንው በየግድግዳው፣ መኪናው ወይም በሚታይ ቦታ መለጠፉ ሳይሆን እውነትም ጥበብ እግዚአበሔርን ከማወቅ የምትመጣዋ ወደ መጨረሻ እውነት እንደምትወስድ አምኛለሁ፡፡ ግን እንዲህ ያለችውን ፍልስፍና ለማግኘት እጅግ የረቀቀ ማስተዋልን የሚጠየቅና ተራውን የአለም ፍልስፍና መናቅ የሚያስችል አቅም መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ለብዙዎች የእውነት መዳረሻዋ ፍልስፍና ሞኝነት ነችና፡፡ አስቀድሞ ለኖሕ፣ ከዚያም አብርሃም፣ ሙሴ፣ በልዓም (የሰባሰገሎቹ አባት)፣ ለኤልያስ፣ ዳንኤልና ሰለስቱ ደቂቅ፣ ሌሎች ነብያት፣ እያለ ከእንስቶች ለእናቱ ለድንግል ማርያምና ሌሎች፣ ለመቶ አለቃው (ቃል ተናገር ያለው)፣ ለዮሐንስ መጥምቅና ዮሐንስ የጌታ ወዳጅ (ወንጌላዊው)፣ ጳውሎስ፣ ጴጥሮስና ሌሎች ሐዋሪያት፣ እያለ እስከዚ ዘመን ለደረሰቸው እግዚአብሔርን ለፈለጉት እየተሰጠች የምትገኝ ፍልስፍና ዛሬም አለች፡፡

ይህች ፍልስፍና በአለማውያን ዘንድ ሞኝነት ተደርጋ በታሰበችበት ልክ የዓለምን ጥበብ ሁሉ ሞኝነትና መካን ለማድረግ የማይታጠፍ ክንድ አላት፡፡ ሁሉን ትመረምራለች ግን አሷ በማንም አትመረመርመ! ለዚያም ነው ያወቁ የመሰላቸው ግን ያላወቁ ሞኞች ሞኝነት የመሰለቻቸው፡፡ እሷ የዳህራዊ እውነትን (የእግዚአብሔርን ሥም) አርማዋ አድርጋለችና፡፡ የዳህራዊ እውነት ፍልስፍና በታሪክ ብዙም ስለማትገለጽ ለዘመናትና ለብዙ ትውልድ ሳትገለጥ በአለም የሞኝ ፍልስፍና እድል አግኝታ ለዘመናት ትውልድን ሞኝ አድርጋለች፡፡ ዛሬ እኛ እድለኞች ሆነን የዳህራዊ እውነት ፍልስፍና በእኚች ፈላስፋ ተገልጣ ብዙ ሞኝነቶቻችንን (ለእኛ ጥበብ የነበሩ) አጋልጣብናለች ወይም አጋልጣልናለች፡፡ አለም በደረሰበት ጥበብ እልባት ያላገኙ ደዌያት በቃል ብቻ በልዑል እግዚአብሔርና በቅዱሳኑ ስም ልቀቅ እየተባሉ ሰዎች ሲፈወሱ፣ ውስብስብ የኑሮ ችግሮች አቁም እየተባሉ ወደ ተደላደለና የደስታ ሕይወት መመለስ፣ ብዙ ትክክል ነን ሲሉ የነበሩ ፍልስፍናዎችና እምነቶች እራሳቸው ሐሰተኞች ነን እንዲሉ የተገደዱበት፣ ችግሮቻችንና በአብዛኛው ጥበቦቻችንም በድብቅ የክፉ መናፍስት ሴራዎች ሰለባ እንደሆኑ በገሀድ አየን፡፡

አሁንም ማስተዋሉን ከሰጠን ብዙ ጥያቄዎች አእምሮአችን ይጠይቃል፡፡ ማወቃችን ሁሉ አለማወቅ፣
ጥበባችን ሁሉ ሞኝነት፣ አለን የምንለው ሁሉ መና ሊሆን አንደሚችል ታዘብን፡፡ ሳይንስም ይሁን ሌላ
ጥበብ ጥያቄ ውስጥ ገባ፡፡ የዕውቀታችን ውሱንነት ተጋለጠ፡፡ በተለይ የስነ ሕይወቱ ሳይንስ አቅጣጫ ሁሉ እንደሳት ታዘብን፡፡ በአንዱ በመምህር ግርማ ወደ ብዙ የፈላስፎች የደረሰች እውቀት ጥያቄ ጫረች፡፡

ጥበባችንና እውቀታችንን ሁሉ ናደች፡፡ በአጠቃላይ አለማዊ ፍልስፍናዎችን ተገዳደረች፡፡
አምላክ ሆይ አንተ ሁሉን ፈጠርህ፣ አለም-አለማትን በውስጣቸው ያሉትን ሁሉ! እኛን ደግሞ ማስተዋልንና ጥበብን ሊለብሱ ከሚችሉ ከከበሩ ፍጥረታቶችህ ወገን አደረግከን! እኛ ግን የአንተን የከበረ አባታችንን ስጦታ ትተን ውርደትን መረጥን (የአሳማ ምግብ ተመኘን)! ብዙ በድለናልና አቤቱ ይቅር በለን! ዳግምም ወደ ሰጠህን የክብር ጥበብ (ፍልስፍና) መልሰን! ሁሉን መመርመር የምታስችለንን ፍልስፍና እንከተላት
         ዘንድ አቤቱ አእምሮአችንን ክፈት!! ዘመናችንንም ባርክ! አሜን!



No comments:

Post a Comment