Friday, September 27, 2013

እምቧይ

እምቧይ ለዛፍ ንጉስነት የተመረጠበት ጉባዔ!
አንድ ጊዜ ዛፎች ከአደባባይ ወጥተው፣
ንጉስ ለመሰየም ሁሉም ተሰብስበው፣
ወይራን ንገስልን ብለው ቢጠይቁት፣
እግዚአበሔርና ሰው በእሱ የሚከብሩበት፣
ውድ ዘይት ሳለኝ ክብሬን የሚጠብቅ፣
ለዛፎች እንድነግስ ከቶ እንዴ ልጠየቅ፣
ብሎ እምቢ አላቸው ዛፎችን በመናቅ፡፡
ይሄ የወይራ መልስ ተስፋ አስቆርጧቸው፣
በለስንም ቢሉት እንዲነግስላቸው፣
በንዴት ቃል ጮሆ እንዲህ አሳፈራቸው፡፡
አጅግ ጣፋጭና መልካም ፍሬ ሳለኝ፣
በዚህ ተወድጄ ሰው ሁሉ ሲያከብረኝ፣
በዛፍ ላይ መንገሴ ይህን ክብሬን ትቼ፣
አንዴት ቢታሰብ ነው ከቶ ምን አጥቼ፡፡
ዳግም በበለስ መልስ ቅስማቸው ተሰብሮ፣
ወይንን ቢጠይቁት ሁሉ እሱን አክብሮ፣
እንዲህ ሲል መለሰ ፊቱን አኮሳትሮ፡፡
እግዚአብሔርና ሰው ደስ የሚሰኙበት
መልካም ጣፋጭ ፍሬ ከእኔ ሲበረከት፣
በዛፎች ላይ መንገስ ክብር እንዳነሰው፣
በእውነት ይህ ለእኔ የውርደት ውርደት ነው፡፡
ወይራና በለሱ እንዳሳፈሯቸው፣
ተስፋ ያደረጉት ወይንም ደገማቸው፡፡
ምንአልባት አሉና ቢጠይቁት ዝግባን፣
እንዲ ሲል መለሰ አገንፍሎ ደሙን፡፡
የእግዚአብሔር የሰው ቤት የሚገነቡበት፣
ውብ እንጨት እያለኝ የምከበርበት፣
ለዛፍ የምነግሰው ከቶ ምን ሲደረግ፣
ክብሬን አዋርጄ ከዚህ ሁሉ ማዕረግ፡፡
እንዲህ እንዲህ እያለ ሁሉም ስላለቀ፣
የማታ የማታ እምቧይ ተጠየቀ፡፡
ጉባዔው በጉጉት መልሱን ሲጠባበቅ፣
እንኳንስ እምቢ ሊል በክብር ሲጠየቅ፣
ደስታ ፈንቅሎት ጀመረ መፈንደቅ፡፡
ያ ሁሉ የዛፍ ዘር የናቀው ንግስና፣
እምቧይ ተቀበለው ሲጠይቁት ገና፡፡
ወዲያው ተነሳና ወጥቶ ከዙፋኑ፣
ንግግር ቀጠለ ንጉስ በመሆኑ፡፡
በዚህ ድንቅ ምርጫ እኔን ማንገሳችሁ፣
ፍትሐዊነትን አረጋገጣችሁ፡፡
ከአሁኗ ሰዓት ከዛሬ ጀምሮ ፣
ረዥም ሆንሽ አጭር ግዙፍ ሆንሽ ጭራሮ፣
ሁልሽም ዝቅ ብለሽ ታች ከጥላዬ ሥር፣
ለጥ ሰጥ ብለሽ ትዕዛዜን በማክበር፣
መገዛት አለብሽ ያለማንገራገር፡፡
የሰማም ጉድ አለ ግራ ገባው የሚያይ፣
በዛፎች ጉባዔ በዚህ አደባባይ፣
ሁሉን ቁልቁል አይቶ ሊጫናቸው ከላይ፣
የዛፍ ንጉስ ሆኖ ተመረጠ እምቧይ፡፡
ተጻፈ በታላቋ ቀን ልጅ
(የታላቋ ቀን ልጅ ታላቅ ነገርን ያስባል እስካሁን ግን እሱ ታላቅ አይደለም)
የታላቋ ቀን ልጅ ንጉስ (መሪ) ለመሆን ንጉሳዊ (ክብር ያለው) መሠረት ያስፈልጋል፤ ባሪያን (ወራዳን)
ብትሾመው ከእሱ በታች ያዋርድሃል እሱ ወደ አንተ ደረጃ (አስተሳሰብ) ከፍ ማለት አይችልምና ብሎ
ያምናል፡፡

No comments:

Post a Comment