Friday, September 6, 2013

የሥላሴዎች እርግማን (አምስት) የመንፈስ ደሀነት – ከፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም

ከፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም

ነሐሴ 2005
ዱሮ በአጼ ዘመን አንድ ወዳጅ መጣና አንድ ቤት ላሳይህ እንዳያመልጥህ ብሎ ይዞኝ ሄደ፤ ቤቱ ከጀርመን ኤምባሲ ፊት ለፊት ያለ ሰፊ ግቢ ያለው ቪላ ነበር፤ ባለቤቲቱ አንዲት ቆንጆ ወጣት የልጆች እናት ነበረች፤ ባልዋ በአደጋ ሞቶባት የባንኩ ዕዳ በየወሩ እያደገ ልትከፍለው የማትችለው ስለሆነባት በጨረታ ከመሸጡ በፊት ሌላ ዘዴ ሰዎች መክረዋት ነበር፤ እኔ የቀረብሁት ለዚህ ነበር፤ እስዋ ለሠራተኞች መኖሪያ በተሠራው ውስጥ ከነልጆችዋ ለተወሰነ ጊዜ እንድትኖርና አኔ የባንኩን ዕዳ ወደኔ አዛውሬ ለአስዋ ደግሞ ትንሽ ገንዘብ እንድሰጣት ነበር፤ በእኔ በኩል ዕዳውን ማዛወሩም ሆነ ለሴቲቱ የሚከፈለውን ለመክፈል በጣም ቀላል ነበር፤ የቸገረኝ ሌላ ነገር ነበር፤ እኔ ከነልጆቼ እዚያ ቤት ውስጥ ገብቼ ስኖር ባለቤቲቱ ከነልጆችዋ ለሠራተኞች በሠራችው ውስጥ ስትኖር በአየኋት ቁጥር የሚሰማኝ ኩራት ይሆናል ወይስ እፍረት? በዚች በወጣት እናት ችግር እኔ ሀብት አልሸምትም ብዬ ተውሁት፤ ጓደኞቼ የሚሉትን ሁሉ አሉኝ፤ ሌላ ሰው ይገዛዋል አንዳሉት ከጥቂት ቀናት በኋላ አንድ ፊታውራሪ ገዙት ሲባል ሰማሁ፤ እኔ ከኅሊናዬ ጋር እንበለ ቤት አለሁ፤ ባለቤቲቱ እንዴት እንደሆነች አላውቅም፤ የገዙትም ፊታውራሪ ሀብታቸው ምን እንዳተረፈላቸው አላውቅም።
ተናግሬው የማላውቀውን ታሪክ ያወራሁት ለመመጻደቅ አይደለም፤ የሚመስላችሁም ካላችሁ ደስ ይበላችሁ፤ ምክንያቴ ‹‹የሥላሴዎች እርግማን — አዳክሞ ማደህየት›› በሚል ርእስ የጀመርኋቸው ጽሑፎች ናቸው፤ በቅርቡ በኢትዮ ምኅዳር (ሐምሌ 17/2005) ጋዜጣ ላይ ‹‹የቤተ መንግሥት ደጃፍ ግፎች›› በሚል ርእስ ተጽፎ ያነበብሁት ምን ዓይነት የመንፈስ አዘቅት ውስጥ እንደወደቅን የሚያሰየኝ በመሆኑ ነው፤ በአራት ኪሎ አምስት ትውልድ ያህል ያሳደገ የሕዝብ ሰፈር ሲፈርስ እዚያው ያደጉ የሰፈሩ ጎረምሶች ጥቅም ለማግኘት የበሉበትንና የጠጡበትን ቤት ለማፍረስ ሲሻሙ የሰው ልጅ ውሻ ያልደረሰበት ደረጃ መድረሱን ገመትሁ፤ ይህንን በደሀነት ግፊት ልናማካኘው እንችላለን፤ ደሀዎች፣ ለጫትና ለኮካ ኮላ ገንዘብ የሌላቸው የእናቶቻቸውን ቤቶች በማፍረስ ለሱሳቸው የሚገብሩ ናቸው፤ የደሀዎቹ ቤቶቹ በፈረሱበት መሬት ላይ ታላላቅ ሕንጻ የሚሠሩት ሀብታሞችስ በመንፈስ ደሀነት ከደሀዎቹ በምን ይሻላሉ? ሁለቱም እኩል የመንፈስ ደሀዎች ናቸው፤ የወገኑን ግፍ እንዳያይ ዓይኑን የጋረደውን የፎቅ ባለቤትነት ሱስ ያሳደረበትና ያደገበትንና የበላበትን ቤት እንዳያይ ዓይኑን የጋረደው የጫትና የኮካ ኮላ ሱስ ያለበት አንድ ናቸው፤ ከራሳቸው ውጭ ሰው የለም፤ በቅርቡ እኔ በምኖርበት አካባቢም የማፍረሱ ትእዛዝ በየቤቱ ሲደርሰን አንደሰማሁት የሰፈሩ ጎረምሳዎች ለአፍራሽነት እየተመዘገቡ ነበር አሉ፤ ከዚህ የባሰ የመንፈስ ደሀነት አዘቅት ምን አለ?
እናቶቻቸውንና አባቶቻቸውን፣ ዘመድና ወዳጆቻቸውን፣ ራሳቸውንም ጭምር ለጊዜያዊ ጥቅም ለውጠው፣ ኅሊናቸውን አፍነው፣ አእምሮአቸውን አደንዘው፣ መንፈሳቸውን አዋርደው፣ ሰውነታቸውን አርክሰው ነገ በእነሱና በሌሎች ላይ የሚደርሰውን ሳያውቁ በደመ-ነፍስ ለሆዳቸው መሣሪያ እየሆኑ ጥቃትንና ግፍን የሚያራምዱ ወጣቶች ተንጋሎ የተፋ ለራሱ ከፋ እንደሚባለው ይሆናሉ፤ እስከመቼ ተንጋለው ይቆያሉ? እስከመቼ በራሳቸው ላይ ይተፋሉ? በትናንሽ ጊዜያዊ ጥቅም ወይም ምቾት እየተደለሉ የራስ ሥራ በራስ ላይ ለዘለቄታው የሚያመጣውን ጉዳት ወይም ጥፋት አለመገንዘብ ትልቅ የመንፈስ ደሀነት ነው፤ እንዲያውም የደሀነት ዋናው መሠረት የመንፈስ ደሀነት ነው ማለት ይቻላል፤ አብዛኛውን ጊዜ የውጭ ጠላቶች መሣሪያ አድርገው የሚጠቀሙበት የመንፈስ ደሀነትን ነው፤ የመንፈስ ደሀነት ለማይረካ የምኞት ባርነት ይዳርጋል፤ የመጨረሻ ውጤቱም የሰውን ልጅ ወደርካሽ ዕቃነት ለውጦ በገንዘብ የሚሸጥና የሚለወጥ ማድረግ ነው፤ ነቢዩ ኢሳይያስ የሚከተለውን ይላል፡—
የእግዚአብሔር ቀን ቀርቦአልና አልቅሱ፤ ሁሉን ከሚችል አምላክ ዘንድ እንደሚመጣ ጥፋት ይመጣል፤ ስለዚህ እጅ ሁሉ ትዝላለች፤ የሰውም ሁሉ ልብ ይቀልጣል፤ ይደነግጣሉ፤ ምጥና ሕማም ይይዛቸዋል፤ እንደምትወልድ ሴትም ያምጣሉ፤ … እነሆ ምድሪቱን ባድማ ሊያደርግ ኃጢአተኞችዋንም ከእርስዋ ዘንድ ሊያጠፋ ጨካኝ ሆኖ በመዓትና በጽኑ ቁጣ ተሞልቶ የእግዚአብሔር ቀን ይመጣል፤ የሰማይም ከዋክብትና ሠራዊቱ ብርሃናቸውን አይሰጡም፤ ጸሐይም በወጣች ጊዜ ትጨልማለች፤ ጨረቃም በብርሃኑ አያበራም፤ ዓለሙን ስለክፋታቸው፣ ክፉዎችንም ስለበደላቸው እቀጣለሁ፤ የትዕቢተኞችንም ኩራት እሽራለሁ፤ የጨካኞቹንም ኩራት አዋርዳለሁ፤ የቀሩትም ከጥሩ ወርቅ ይልቅ የከበሩ ይሆናሉ፤ ሰውም ከአፊር ወርቅ ይልቅ የከበረ ይሆናል።
አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ በችጋር እየተቆላ፣ ከመኖሪያው እየተፈናቀለ በየትም ወድቆ በሚኖርበት፣ የዕለት ጉርሱን ለማግኘት ሌት-ተቀን እየደከመ የሚያገኘውን በሰበብ አስባቡ እየበዘበዙት ኑሮው ይበልጥ እያሽቆለቆለ በሚሄድበት ዘመን የጥቂቶች ሰዎች የተንደላቀቀ ኑሮ የሚያሳፍር እንጂ የሚያኮራ፣ አንገት የሚያስደፋ እንጂ የሚጀነኑበት አይደለም፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንባውን ወደሰማይ እየረጨ የሚጸልየውን ጸሎት ነፋስ ይዞት አይሄድም፤ በአምላክ ፊት እንደጎርፍ ይወርዳል፤ አምላክም ጊዜውን ጠብቆ ይፈርዳል፤ አይቀርም፤ የሥላሴዎች እርግማን ነውና!

No comments:

Post a Comment