Saturday, August 17, 2013

አጭር ጨዋታ

አጭር ጨዋታ፤ ሆያ ሆዬ እና ኢቲቪ!

ህፃናቶቹ የቡሄን በዓል ለማክበር ተሰባስበዋል። በየ ቤቱ እንደ ሁኔታው የተለያየ ግጥም እያሰናዱ በየደጃፉ ይጨፍሩ ነበር። በዚህ ሁኔታ ሲሄዱ ሲሄዱ አንድ የኢህአዴግ ዋና ካድሬ ቤት ደረሱ። “ይህ ሰው ድርጅቱን ካላቆላመጡለት ጠብ አይለውም፤ ጭራሽ ለፀብ ይጋበዛል እንጂ…” በሚለው ጨፋሪዎቹ ህፃናት ተስማምተዋል። ስለዚህም በራዲዮ እንደሚሰሙት ኢህአዴግን “አውራው ፓርቲ” እያሉ እየጠሩ አሞካሽተው ሳንቲማቸውን ገቢ ለማድረግ ተነጋገሩ… በተኮላተፈ የልጅ አንደበት ጀመሩ…
“መጣና መጣና ደጅ ልንጠና…
እዚህ ቤቶች አንደምን ናችሁ
ባመት አንድ ቀን መጣንላቹ….
“እዛ ማዶ አንድ ፊኛ
እዚህ ማዶ አንድ ፊኛ
አውሪው ፓርቲ አደገኛ”
ብሎ ዘፈን አወጣ  ሌላው ህፃን ቀስ ብሎ ማስተካከያ ተናገረ። “አውራው ፓርቲ ነው የሚባለው!” አለው። ስለዚህ ድጋሚ አስተካክሎ ለመጨፈር ደገመው፤
“እዛ  ማዶ አንድ ፊኛ
እዚህ ማዶ አንድ ፊኛ
አውሬው ፓርቲ አደገኛ”
አሁንም ተሳሳተ። ይሄን ጊዜ ሊሸልሙ የተዘጋጀው አባወራ ካድሬ ከስልክ ከፍ ከራዲዮ ዝቅ ያለ አንዳች መነጋገሪያ አወጣ። ተነጋገረም። ልጆቹ ደነገጡ ዱላቸውን እና ፊታቸውን አዙረው ወደ መጡበት ሮጡ! እግሬ አውጪኝ አሉ። እግራቸው ግን አላወጣቻቸውም አካባቢው ከመቅስፈት በአድማ በታኝ ፖሊሶች ተሞላ። ሁሉም ልጆች በቁጥጥር ስር ዋሉ።
ማታ ላይም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እንዲህ የሚል ዜና ቀረበ።
“ሆያ ሆዬን ሽፋን በማድረግ በማድረግ ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳ ሲያራምዱ የነበሩ ፈልፈላ ግለሰቦችን የፌደራል ፖሊስ እና የብሄራዊ ደህንነትና መረጃ የጋራ ፀረ ሽብር ግብረ ሃይል ከህብረተሰቡ ጋር በመተባበር በቁጥጥር ስር አውሏቸዋል።
ግለሰቦቹ ከሻቢያ፣ ግንቦት ሰባት እና ኦነግ ጋር ጥብቅ ቁርኝት እንደነበራቸው የተደረሰበት ሲሆን አንዳንዶቹም ኤርትራ ድረስ በመሄድ መንግስትን የሚያጥላላ የቡሄ ግጥም ሲለማመዱ እንደነበር ተደርሶበታል” የሚል ዜና ቀረበ!
abetokichaw...........

No comments:

Post a Comment