Wednesday, August 21, 2013

ኢትዮጵያዊቷን አሰቃይታ የገደለች አሰሪ በ3 ዓመት እስራት ተቀጣች

በመስከረም አያሌው
 
ኢትዮጵያዊት የቤት ሰራተኛዋን ለረጅም ጊዜ አሰቃይታ ለሞት የዳረገች የአቡዳቢ አሰሪ በሶስት ዓመት እስራት ተቀጣች።
ብሉምበርግ ከአቡዳቢ እንደዘገበው አሰሪዋ ኢትዮጵያዊቷን በየእለቱ የፈላ ውሃ ላይዋ ላይ በመድፋት፣ በፀጉር ማድረቂያ የኤሌክትሪክ መሣሪያ በመደብደብ እና አይኗ ውስጥ በርበሬ በመጨመር ስታሰቃያት ቆይታለች። ኢትዮጵያዊቷ ወደዚች አሰሪዋ ቤት ከገባችበት ጊዜ ጀምሮ በዚህ አይነቱ ስቃይ ውስጥ የነበረች ሲሆን በስቃዩ ብዛትም ህይወቷ ሊያልፍ ችሏል። አሰሪዋም ባለፈው የካቲት በቁጥጥር ስር ውላለች።
ጉዳዩን ሲመረምር የቆየው የሀገሪቱ ፖሊስም አሰሪዋ ጥፋተኛ ናት ሲል ባለፈው ነሐሴ አንድ በሶስት ዓመት እስራት እንድትቀጣ ወስኗል። አሰሪዋ ሰብዓዊነት እና ርህራሄ በጎደለው መልኩ ኢትዮጵያዊቷ ላይ በየእለቱ ለፈፀመችው ስቃይም ሆን ብላ መሆኑን ከስነልቦና ባለሞያዎች የተገኘው ውጤት ያመለክታል ብሏል። የስነ ልቦና ባለሞያዎች ሪፖርትም አሰሪዋ ጤነኛ እና የምታደርገውን ነገር የምታውቅ ሴት መሆኗን አረጋግጠዋል።
ህይወቷ ያለፈው ኢትዮጵያዊት ቤተሰቦችም አሰሪዋ ላይ የሞት ቅጣት እንዲፈረድ እና 200ሺ ድሪሃም የደም ካሳም እንዲከፍላቸው ጠይቀዋል።
በተያያዘ ዜና አንድ ኢትዮጵያዊ በካሮሊና በባለቤታቸው እና በሁለት ወንድ ልጆቻቸው ላይ በፋስ እና በቢላዋ ጉዳት ማድረሳቸውን ደብልዩ ቢ ቲቪ ዘግቧል። አቶ ምሩጽ ሃይሉ የተባሉት የ57 ዓመቱ የካሮሊና ነዋሪ ባለፈው ሳምንት ሰኞ ምሽት ላይ ባለቤታቸውን እና ሁለት ታዳጊ ወንድ ልጆቻቸው ላይ ፋስ እና ቢላዋ ተጠቅመው ጉዳት አድርሰው በቁጥጥር ሥር ውለዋል።
ምሽት ሁለት ሰዓት ተኩል ገደማ ከአንድ የተረበሸ የ16 ዓመት ልጅ በደረሳቸው የስልክ ጥሪ ወደ አቶ ምሩፅ ቤት ያመሩት ፖሊሶች ጊቢው ውስጥ ሲደርሱ የ15 ዓመት እድሜ ያለው ልጅ በረንዳ ላይ ወድቆ እንዲሁም የልጁ እናት መኝታ ቤት ውስጥ ተዘርራ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ፖሊስ አቶ ምሩፅን በቁጥጥር ስር ካዋለ በኋላ በግቢው ውስጥ ባደረገው ፍለጋ አንድ የስጋ ቤት ቢላዋ እና ሌላ የስጋ ቢላዋ ከአልኮል ጠርሙስ ጋር ቆሻሻ ውስጥ ተጥሎ ተገኘቷል።
ጉዳቱ የደረሰባት የልጆቹ እናት ሁኔታው አሳሳቢ በመሆኑ እርዳታ እየተደረገላት ሲሆን የ16 ዓመቱ ታዳጊ ልጅም በካሮሊናስ የህክምና ማእከል ቀዶ ህክምና ሊደረግለት በዝግጅት ላይ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል።
አቶ ምሩፅ ድርጊቱን የፈፀሙበት ምክንያት እስከ አሁን ድረስ ያልታወቀ ቢሆንም፤ ግለሰቡ ሆን ብሎ ለመግደል በማሰብ በመሳሪያ መዋጋትን ጨምሮ የተለያዩ ስድስት አይነት ክሶች እንደተመሰረቱባቸው ተገልጿል። ጉዳያቸው በፍ/ቤት እንዲታይ ባለፈው ማክሰኞ ተቀጥሮ የነበረ ቢሆንም ጉዳያቸውን ሊያስረዳላቸው የሚችል አስተርጓሚ በማስፈለጉ ሌላ ቀጠሮ ተሰጥቷል።
ምንጭ፡-ሰንደቅ ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment