Thursday, August 29, 2013

ሚካኤል ፀጋዬ

ፎቶ አንሽው ሚካኤል ፀጋዬ በተለያዩ አገሮች አውደ ርዕይ አሳይቷል። ከዚህ ባሻገር ፎቶዎቹ በታዋቂው ሳምንታዊ የጀርመን መፅሄት «ዴር ሽፒግል» ታትመው ወጥተዋል። ሮይተርስን እና ብሉምቤርግን የመሳሰሉ የመገናኛ ብዙኋንም በፎቶዎቹ ተጠቅመዋል።
የአንድን ሀገር ባህል ወይንም የአኗኗር ዘይቤ በመረጃ ጠብቆ ለማቆየት ቪዲዮ፣ ስዕል ወይንም ፎቶ ጥሩ ዘዴዎች ናቸው። የዛሬው የባህል መድረክ እንግዳችን ሚካኤል ፀጋዬ ከአዲስ አበባ ዮኒቨርስቲ በቀለም ቅብ ተመርቋል። ለአንድ ዓመት ያህል በቀለም ይስል ነበር በኋላ ግን ፎቶ አንሺነትን መርጧል።
የሚካኤል ፎቶዎች ሁለ ገብ ናቸው። ክረምት እና በጋ፤ ህፃናት እና አዛውንት፣ ሰዎች በስራ ወይንም በእንቅስቃሴ ላይ ሳሉ የሚያሳዩ ናቸው። ሚካኤል ለአውደ ርዕይ ካቀረባቸው ፎቶዎች መካከል፣ በብዛት የአዲስ አበባ ከተማ የመሬት አቀማመጥ፣ የህንፃ እና የመንገድ ገፅታዎች ይገኙበታል። « ታሪክን እንደመፃፍ ነው የማየው» ይላል ፎቶአንሽው። ሌላው ፎቶዎቹ መስታወታቸው የተሰበሩ መቃብር ላይ ያሉ ምስሎች ናቸው። እነዚህ ፎቶዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በአውደ ርዕይ ደረጃ አልቀረቡም። እስካሁን አንጎላ እና ፈረንሳይ ውስጥ ብቻ ሲሆን የታዩት ፤አብዛኞቹ ተመልካቾች የሰጡት አስተያየት ፎቶዎቹ ሁኔታውን በአግባቡ የሚያሳዩ ፤ነገር ግን የሚያሳዝኑ እና የሚረብሽ ስሜት የሚፈጥሩ መሆናቸውን ነግረውታል ። ሌሎቹ ሚካኤል ያነሳቸው ፎቶዎች በአዲስ አበባ የሚገኙትን የሴተኛ አዳሪዎችን አኗኗር ያሳያል።
ሚካኤል በፎቶው ማስተላለፍ ወይንም ማሳየት ስለሚፈልገው መልዕክት፣ በተለያዩ ሀገራት ለአውደ ርዕይ ስላበቃቸው ፎቶዎች እና ስለ ፎቶ አንሺነት ሙያ ሚካኤል ፀጋዬ ገልፆልናል። ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
አርያም ተክሌ

No comments:

Post a Comment