Wednesday, August 21, 2013

የኢትዮዽያ ሙስሊምና ክርስትያን ግንኙነት እስከየት ድረስ?


የኢትዮዽያ ሙስሊምና ክርስትያን ግንኙነት እስከየት ድረስ?
በመስፍን ጌታቸው (የሰው ለሰው ድራማ ደራሲ)፤ ዕንቁ መፅሔት….ነሐሴ 2005
[ሁሉም ሊያነበው የሚገባ ምርጥ ጽሑፍ]

Image
…. ሰሞኑን ለንግሥና ለሥራ ጉዳይ ወደ ምስራቁ የአገራችን ክፍል አቅንቼ ስለነበር፤ ከዚያ ያገኘሁትን ላካፍላችሁ፡፡ የቁልቢ ከተማ በታላቁ የቅዱስ ገብርኤል የንግሥ በዓል ሞቅ ደመቅ ብላ ነበር፡፡ እኔም በሥፍራው በመገኘት ጸበል ተረጭቼ በዓሉን አክብሬያለሁ፡፡
ታዲያ ሁሌ ቁልቢ በሄድኩና ስለቁልቢ ባሰብኩ ቁጥር በውስጤ ይመላለስ የነበረው አንድ ሐሳብ፤ ዛሬም ጠንከር ብሎ አእምሮዬን ተቆጣጠረው፡፡ እስኪ በዓይነ ኅሊናችሁ የቁልቢውን ገብርኤል ለአፍታ አስቡት … ከወዲህ ከአዋሽ ጀምሮ እስከ አገራችን ድንበር ድረስ ሃይማኖታቸውን በሚያከብሩ ንጹህ ሙስሊሞች ተከብቦ፤ ከርቀት በቀላሉ መታየት በሚችልበት ተራራ ላይ ጉብ ብሏል፡፡ ነገር ግን እነዚያ ታቦቱን ከብበው የሰፈሩ ሙስሊም እህቶቻችንና ወንድሞቻችን አንድ ጊዜም የሃይማኖታቸው ተቃራኒ የሆነውን ታቦት ሲተናኮሉትም ሆነ ሲያጉረመርሙበት ተሰምቶ አያውቅም፡፡ እንዲያውም ለበዓሉ ድምቀት ከሕዝበ ክርስቲያኑ እኩል ወገባቸውን ሸብ አድርገው ደፋ ቀና ሲሉ ይገኛሉ፡፡ በሌላው አገር ቢሆን ኖሮ፤ ይሄ እውነታ ለትልቅ ግጭትና ብጥብጥ መነሻ ይሆን ነበር፤ ቤተ ክርስቲያኑም ገና ድሮ ከሥፍራው በጠፋ ነበር፡፡ እዚህ ግን ታሪኩ የተለየ ነው፡፡ ሙስሊምና ክርስቲያን ወንድማማች ሕዝቦች የራሳቸውን ማንነት በመጠበቅ፤ የወንድሞቻቸውን ሃይማኖት አክብረው በጽኑ ፍቅርና ሠላም ተቻችለው ይኖራሉ፡፡ ይሄን እውነት በምሳሌ ብናጠነክረውስ?

እኔ የሐረር ልጅ ነኝ፡፡ ወርቃማ የዕድሜዬን ዘመን ያሳለፍኩት ሐረር ውስጥ ነው፡፡ ታዲያ በዚህ ወቅት ብዙዎቻችን የረመዳንን ፆም ሙሉ በሙሉም ባይሆን በመጠኑ እየፆምን እናግዛቸው ነበር፡፡ እነሱም ለቁልቢ ገብርኤል ክብረ በዓል ከሐረር እስከ ቁልቢ ያለውን 60 ኪሎ ሜትር መንገድ አብረውን በእግር በመጓዝ ታቦቱን አንግሰው ይመለሳሉ፡፡

የሚገርመው ግን ይሄ አይደለም፤ በሌሊት በሚደረገው ጉዞ፤ ከሐረር እስከ ቁልቢ ያለው መንገድ ላይ የሚኖሩ ሙስሊም ኦሮሞዎች በብዛት በየሁለት መቶ እና ሶስት መቶ ሜትር ርቀት ሰብሰብ ብለው በመቀመጥ ሌሊቱን ሙሉ እሳት አንድደውና የቁጢ ሻይ አፍልተው የደከመውን ተጓዥ በማሳረፍ፣ ሻይ አጠጥተው ቂጣም፣ ብርቱካንም አብልተው ጠንከር ሲልም እግራቸውን እና ወገባቸውን በማሻሸት አቅማቸውን አዳብረው ስለታቸውን እንዲያደርሱ መርዳታቸው ነው፡፡ ቢበዛም አርአያነቱ መልካም ስለሆነ አንድ ልጨምር፤ ገብርኤል የሄድነው አንዲት የሦስት ወር ህፃን ልጅ ይዘን ነበር፡፡ ብዙ ጊዜያችንን ያሳለፍነውም ሐረር የሚገኙት ሆዳን እና ያሲን የሚባሉ ሙስሊም ወዳጆቻችን ቤት ነው፡፡ ታዲያ በዚህ ሁሉ ጊዜ ህፃኗን ዞር ብለን አይተናት አናውቅም፡፡ የሆዳን እናት ኡማ፤ “እስኪ ትንሽ ተንፈስ ትበል…” በሚል ዳይፐሯን ፈታተው እግራቸውን በማጣመር ድሪያቸው ላይ ጋደም አድርገው እያጫወቷት ነበር ጊዜው ያለቀው፡፡
ያቺ ህፃን ከዚያ በፊት እንዲያ ደስተኛ ሆና አይቻት አላውቅም፡፡ ይህ ስሜት የእናቷም ጭምር ነው፡፡ ሦስተኛ ወሯን ያከበረችው ህፃን፤ “ኧረ ካካ ልትልቦት ትችላለች!” ሲባሉ፤ “ብትልስ!? ታዲያ ውሃ አይደል እንዴ የሚያጠራው!?” ባሉት በኡማ እቅፍ ውስጥ ሆና ለአፍጢር በተዘጋጀው ጥብሳ ጥብስና በጣፋጭ ቴምር ተከብባ ነበር፡፡

አሁንም ይሄ አይደለም የሚገርመው፤ ኡማ ህፃኗ ክንድ ላይ በጨርቅ የታሰረውን ነገር ምንነት ጠይቀው እምነት መሆኑ ሲነገራቸው፤ “ታዲያ ጨርቁ ለምን ነተበ?” በሚል እምነቱን ፈትተውና ከሚያምር ድሪያቸው ጫፍ ላይ ጨርቅ በመቅደድ በጥንቃቄ አስተካክለው ሕፃኗ ክንድ ላይ መልሰው ማሰራቸው ነው፡፡ ይህ ጽሑፍ ለማሳመር ተብሎ የቀረበ የፈጠራ ጽሑፍ አይደለም፡፡ እኔ ራሴ በዓይኔ በብረቱ ያየሁት እውነት ነው፡፡ ዑማ የእምነቱን ምንነት ያላወቁ የመሰለው አንባቢ ካለ ተሳስቷል፡፡ ቤታቸው ከመድኃኔዓለም ጀርባ ያለ በመሆኑ፤ እንኳን እምነትን ያህል ነገር ቀርቶ እያንዳንዷን የቤተ ክርስቲያኗን ሥርዓት ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ እሳቸውም ለቤተ ክርስቲያን እምነት አዲስ ድሪያቸውን የቀደዱት፤ ከላይ ያየናቸው ሙስሊም ወንድሞችም
ሌሊቱን ሙሉ እሳት በማንደድ ጀበና ጥደው የስለት መንገደኛ ተቀብለው እያበረቱ ሲሸኙና ሌላ ሲቀበሉ የሚያድሩት ባለማወቅ ሳይሆን በፍቅር ነው፡፡ ገብርኤልም ቁልቢ መካከል ከነግርማ ሞገሱ በኩራት የተቀመጠው በፍቅር ኃይል እንጂ በቆርቆሮ እና በሲሚንቶ ብቻ አይደለም፡፡

No comments:

Post a Comment