Saturday, August 24, 2013

የወጣቱ የመጥለፍ ፖለቲካ በ” ይልቃል አዲሱ ልደቱ…? ” ፀሁፉ ውስጥ

የወጣቱ የመጥለፍ ፖለቲካ በ” ይልቃል አዲሱ ልደቱ…? ” ፀሁፉ ውስጥ

በጥያቄ ምልክትና እና በቃለ አጋኖ የታጀበውን ‘’ይልቃል አዲሱ ልደቱ” በሚል ርዕስ ወጣት ዳዊት ስለሞን በብዕር ስም /አይናለም/ የተፃፈውን ባለ ብዙ ሀሳብ ፅሁፍ አነበብኩት ፡፡ አንድ ፅሁፍ ሲፃፍ አንባቢ ሊታዘብ ይችላል ሰለዚህ እውነት ላይ እና እየታዩ ካሉ ነባራዊ ሁኔታዎች አንፃር መቃኘት አለበት የሚለው ዋና ጉዳይ በዚህ ፀሁፍ ውስጥ ለኔ አልታየኝም ፡፡ በፅሁፉ ውስጥ አንባቢን ለማሳመን የተደረጉ ውጣ ውረዶች ከመጥቀሴ በፊት ፀሀፊው አባል በሆነበት አንድነት ለዴሞክራሲና ፍትህ ፓርቲ ውስጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተመለከትኩትን የሚበረታታ ጉዳይ ከማሳሰቢያው እጠቅሳለሁ፡፡
ማሳሰቢያ ‘’ይልቃል አዲሱ ልደቱ” ፅሁፍ ፀሀፊ ዳዊት ሰለሞን የአንድነት ፓርቲ ልሳን የሆነው ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ ኣዘጋጅ ለመሆኑ አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ የአንድነት አባል ስለነገረኝ ከዚህ በታች የምጠቀመው የብእር ስሙን ሳይሆን ዳዊት የሚለውን ዋና ስሙን መሆኑን አሳውቃለሁ፡፡
መኢአድ ሲባል ኢ/ር ሀይሉ ሻወል፣ ደቡብ ህብረት ሲባል ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ ፣ ኦብኮ ሲጠቀስ ዶ/ር መረራ ጉዲና… የፖለቲካ ተክለ ሰውነት ለብሰው ብቅ ይሉብናል፡፡ ይህ የፖለቲካ ተክለ ሰውነት በአንድት ውስጥም ግዝፈቱን ሳይቀንስ ተንሰራፍቶበት ቆይቷል፡፡ ይህ ማለትም አንድነት ሲባል በየደቂቃው የሚለዋወጥ አቋም ያለው ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው እና ባለመልካም ባህሪው ዶ/ር ሀይሉ አርአያ ድቅን ይሉብን ነበር እነአቶ አስራት ጣሴን አስከትለው፡፡ ወጣት ዳዊትም በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ የሚታዩ ችግሮች ብለው ከጠቀሱዋቸው መካከል የግለሰብ ተክለ ሰውነት መገንባት አንዱ ነው፡፡
እኔም የግለሰብን ተክለ ሰውነት አንዱ መስፈርት አድርጌ ፓርቲዎችን ስገመግም አንድነት አሁን ካሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ የተሻለ ነው እንድል ያደረገኝ ከግለሰብ ትከሻ ላይ ወርዶ አበረታች የሚባል የቡድን ስራ ማክናውን ላይ በመሆኑ ነው፡፡
የተመለከትኩትን ጠንካራ ጎን ከገለፅኩ በኋላ የፓርቲው አባል የሆኑት ወጣት ዳዊት ፅሁፍ ላይ ላተኩር፡፡ ሀሳብን በነፃነት ለመግለፅ ያደረገውን ጥረት በማድነቅ ፅሁፉ መጀመሪያ ላይ የጠቀሱት የደርግ/ የኢህአፓ /የመኢሶን ፖለቲካዊ መጠላለፍ ዛሬ ላይ እንዲመጣ ወይም ዛሬ ላይ ያለው የመፈራረጅ ፖለቲካ እንዲቀጥል ታጥቀው የተነሱ ነው የሚመስለው፡፡ እንዴት! ማለት ጥሩ….. በአዲስ መስመር ከመቀጠሌ በፊት እኔ የሰማያዊ ፖርቲ አባልም ደጋፊም አለመሆኔ ሊታወቅ ይገባል፡፡
አንባቢን ለማሳመን እና ሰማያዊ ፓርቲ የወጣቶች ስብስብ መሆኑን ለማጣጣል የአቶ ልደቱ ወጣት መሆን በመጥቀሥ በጥሩ ሁኔታ እየተቀሰቀሰ ያለውን ፖለቲካ ለመጥለፍ ‹‹አዲሶቹ ጎጆ ወጪዎች ከመጀመሪያው ቤታቸው ሲወጡ በአብዛኛው ባዶ እጃቸውን አይሆኑም፣የእናት ፓርቲያቸውን የፖለቲካ ፕሮግራም፣አደረጃጀትና አባል ይዘው ሹልክ ይላሉ፡፡ለዚህ እንደምሳሌ ኢዴፓና ሰማያዊ ፓርቲን መውሰድ ይቻላል፡፡›› ይሞክራሉ፡፡ እኔም አንድ የመጥለፉ መንገድ ልከተልና ፀሀፊውን ልጠይቀው፡፡ ቅንጅት የአራት ፓርቲዎች ጥምረት ነው፡፡ መሪዎቹ ታስረው ሲፈቱ በጋራ መቆም አቃታቸውና የየራሳቸውን ደጋፊና አባል በመያዝ ለአራት ተሰነጣጠቁ፡፡ከግንቦት 7 በስተቀር ሁሉም የሰላማዊ ትግል መርጦ የቅንጅቱን መንፈስና ፕሮግራም ለማስቀጠል በያለበት ይንቀሳቀሳል፡፡ ከነዚህ ውስጥም አንድነት አንዱ በመሆኑ የእናት ድርጀቱን አባል ፕሮግራም ይዞ ሹልክ አለ ማለት ነው ወይስ አንድነት የተለየ ፕሮግራም አረቀቀ? ይህን ለመመለስ የቅንጅትንም የአንድነት በደንብ ፕሮግራሞች ማየት ያስፈልጋል እንዳትረሳው!
የሰማዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር ላይ ያስቀመጠው ቅሬታ / ግን ሰይጣናዊ ቅናት ብለው በትክክል ይገልፀዋል/ ጠቅለል አርጌ ለመግለፀ በሁለት መክፈል እፈልጋለሁ፡፡ ሊቀመንበሩ ላይ የቀረበው ቅሬታ ለፖለቲካው በማሰብ በሚል እና ፀሀፊው ጎልቶ ለመውጣት ባለው ጉጉት የሚከተላቸው መንገዶች በሚሉ ፡፡
ለፖለቲካው በማሰብ
ኢ/ር ይልቃል /የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር/ “ፓርቲዎች አሉ ብለን አናምንም ተባበሩ የምትለን ከማን ጋር ነው ? መድረክ ምን ሰራ አንድነትና መድረክ እየተባሉ አይደለም? አንድነት ውስጥ የገባው ብርሃን ወጥቷል እኛ ከማን ጋር እንተባበር ? ብለዋል ብሎ ወጣት ዳዊት ይኮንናል፡፡ የኢ/ር ይልቃል ንግግር ላይ ያለውን ስህተት ለማሳየት ፓርቲዎቹ የሰሩትን ምንም መረጃ ማቅረብ ስላልቻለ በደፈናው በህብረት ለመስራት አንፈልግም ብለዋል ሲል ተንከባሎ ያልፋል፡፡ የመድረክ አባል ፓርቲዎች የደቡብ ህብረት ከፕ/ር በየነ ሳምሶናት ውስጥ መውጣት ሳይችል፣ ኦፍዴን ከአቶ ቡልቻ የግል ንብረትነት ሳያልፍ፣ ኦብኮ ከዶ/ር መራራ የኮሜዲ ምሽት ሳይላቀቅ ፣አረና አባላቱ በነፃ ዝውውር ለሰማያዊ ፓርቲ እየፈረሙ ባሉበት ሰአት እና አንድነት በኣዛውንቶችና በወጣቶች መሀክል በሚደረግ ገመድ ጉተታ ፖለቲካ ውስጥ ነው ያለው ስለዚህ ከማን ጋር በህብረት ይስራ ነው የሚባለው፡፡ በተጨማሪም ብርሀንም ከአንድነት የወጣው ገመድ የጉተታ ውጤት ይዞት የሚመጣው ጦስ አስግቶት ነው፡፡ ታዛቢ ስላለ እውነቱ ይህ መሆኑን መግለፅ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ የተቀረበው ቅሬታ ለፖለቲካው በማሰብ አደለም ለማለት እደፍራለሁ፡፡
በተጨማሪም አንድነትን ጨምሮ ሁሉም የመድረክ ፓርቲዎች ጥርት ያለ የፖለቲካ ፕሮግራም ስለሌላቸው መስማማት አልቻሉም ፡፡ ይህንን ስል በስሜት አለመሆኑን ለማስገንዘብ ሁለት ምሳሌ ልጥቀስ፡፡ የመሬት ጥያቄና የመገንጠል መብት ፓርቲዎቹ ከግንባርነት እንዳያልፉ ማነቆ ሆነው ስራ እዳይሰሩ ያደረጋቸውን ብቻ ማንሳት በቂ ነው፡፡ ይህም እውነት ሲገለጽ በሰማያዊ ፓርቲ ፕሮግራም ላይ የተቀረበው ቅሬታ ለፖለቲካው በማሰብ አይደለም ለማለት እገደዳለሁ፡፡
ጎልቶ ለመውጣት የሚደረግ ጥረት
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አንድነት ከላይ እንደጠቀስኩት ከግለሰብ ስብእና ራሱን በማፅዳት የቡድን ስራን በመጀመር የሚያበረታታ እንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ ይህም የቡድን እንቅስቃሴ ባለፉት ግዚያት እንደተመለከትነው በተለያዩ የክልል ከተሞች በመንቀሳቀስ የቀዘቀዘው የህዝብ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ዳግም እንዲያንሰራራ ሚዛን የሚደፋ አስተዋፆ አድረጓል፡፡ ለዚህም አበረታች ጅማሮ ከፊትም ከኋላም በመሆን ከፍተኛ አስተዎ ያደጉትን ግርማ ፣ዳንኤል እና በላይን የመሰሉ ወጣት ፖለቲከኞችን ማመስገን ያስፈልጋል፡፡ በዛውም ልክ ይልቃል ጎልቶ ለመውጣት ይፈልጋል ተብሎ እንደተከሰሰው በአንድነት ህዝባዊ ንቅናቄም ውስጥም በበርካታ ወጣቶች ላይ ጎልቶ የመታየት ፍላጎት ሲከሰት ከርሟል፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ ወጣት ዳዊት ይግኝበታል፡፡ እንዴት የሚል ጥያቄ ከተነሳም መልሱን ክዚህ በፊት ወጣቱ የሚያድጋቸውን ጎልቶ ለመውጣት የሚደረግ ድርጊቶች ላሳይ፡፡ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ አንድነት ፓርቲ ውስጥ የተመለከታቸውን ህፀፆች እንደጋዜጠኝነቱ እንዲታረሙ በበሳል ብእሩ ሲጠቁም የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች የጋዜጠኛውን ጥቆማ በመቀበል የታዩትን ችግሮች ለማረም ደፋ ቀና ብለዋል፡፡ ነገር ግን ፍየል ከመድረሷ ቅጠል መበጠሷ የተባለው ብሂል በወጣቱ ዳዊት ላይ ተተግብሮ ‹‹ ተመስገን ደሳለኝ ሲያዳልጠው›› በሚል ጽኁፍ በአደባባይ ፓርቲውን ለምን ነካ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ በማለት እፍኝ እውቅና ለማግኘት ሲታገል መድከሙ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ ይህ ተግባር በተመስገን ላይ ብቻ የተገደበ እይደለም ፡፡ ብዙ መጥቀስ ይቻላል ነገር ግን ዝም በመባሉ ያሸነፈ ስለመሰለው በተመሣሳይ ላሞኛችሁ አይናችሁን ጨፍሁ ብሎ በኢ/ር ይልቃል ላይ እንዲህ ሲዘምት ጎልቶ ለመውጣት በሚደረግ ጥረት የሚቀዘቅዘው የወጣቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ስላሳሰበኝ ነው ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ የተገደድኩት፡፡
በአጠቃለይ የወጣቱ ፅሁፍ ለሀገራችን ፖለቲካ በማሰብ የቀረበ ሀሳብ ሳይሆን ጎልቶ ለመውጣት የሚደረግ ጥረት በመሆኑ የተጀመረው የህዝብን የማንቃት ስራ አዳክሞ ሀገሪቱን በአንባገነንነት ለሚመራው ኢህአዴግ ነው የሚጠቅመው፡፡ ስለዚህ ወጣት ዳዊት ገና ብቅ ብቅ የሚሉ ወጣት ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኛ ተመስገን ላይ በመፃፍ እውቅናን ለማግኘት ከመጣር ከላይ በአንድነት ውስጥ ከባድ እንቅስቃሴ እያደረጉ ያሉትን ምሳሌ በማድረግ ስራቸውን ማጉላት ላይ ብታተኩሩ ወይንም እነሱ ልምድ ካላቸው ፖለቲከኞች ጀርባ ሆነው ልምድ ቀስመው ዛሬ ለሀላፊነት የበቁበትን መንገድ መከተል በሳልነት መሆኑን ሳልጠቁም አላልፍም፡፡ በመጨረሻም ሰማያዊ ፓርቲ አዲስ መስመር…
ምስረታ ጀምሮ አወዛጋቢ የሆነው ሰማያዊ ፓርቲ 8 አመት ሙሉ የቀዘቀዘውን የሀገሪቱ ፖለቲካ ሚዛን በሚደፋ መልኩ ለማሞቅ ( ለማንቀሳቀስ) ጥረት እያደረገ ነው፡፡ ነገር ግን የፓርቲውን አላማና ፕሮግራም እና በፓርቲው ውስጥ ያሉት አመራሮች ከሊቀ መንበር ውጪ ያላቸው የፖለቲካ ብስለት በሰፊው ለህዝብ ስላላደረሰ አውዛጋቢነቱ እንዲቀጥል አድርጎታል ፡፡ ይህም የፓርቲውን አላማና ፕሮግራም እንዲሁም በፓርቲው ውስጥ ያሉት ወጣት አመራሮች ያላቸው የፖለቲካ ብስለት ለሰፊው ህዝብ ካልደረሰ በሀገራችን ለዘመናት ለቆየው የመጠለፍ ፖለቲካ ጭዳ ይሆናል ባይ ነኝ፡፡ በተጨማሪም እንታገልለታለን ለምትሉት ህዝብ የማሳወቅ ፓርቲው ግዴታም አለበት፡፡
Mastewal  Brihsnu
source....https://freedom4ethiopian.wordpress.com/2013/08/23/8767-2/

No comments:

Post a Comment