Wednesday, August 28, 2013

ቦርጭ አደጋ አለው! ቦርጫችን ለድንገተኛ የሞት አደጋ ሊያጋልጠን ይችላል Belly Fat is Dangerous!



ካሣዬ, AddisAdmassnews.com
ቦርጫችን ለድንገተኛ የሞት አደጋ ሊያጋልጠን ይችላል
አደጋው በዕድሜ ከገፉ ሰዎች ይልቅ በወጣቶች ላይ ይከፋል
ችቦ አይሞላም ወገቧ
ማር እሸት ነው ቀለቧ፡፡
የምትለዋ የዘፈን ስንኝ ቆየት ባሉት ዓመታት የቆንጆ ቅርፅና የተስተካከለ አቋም ባለቤት የሆነችዋን ኮረዳ ለማወደስ አገልግሎት ላይ የዋለች የዘፈን ስንኝ ነች፡፡ በዘፈኑ የምትወደሰዋ ቆንጆ፣ የተስተካከለ የሰውነት ቅርፅ እንዲኖራት ወይንም ወገቧ ችቦ እንዲሞላ (ቦርጫም) እንዳትሆን ያደረጉት የምትመገበውን ምግብ መምረጥ መቻልዋና ያገኘችውን ሁሉ ወደአፏ ባለማድረግዋ መሆኑንም ዘፈኑ በገደምዳሜ ይገልፅልናል፡፡ የወገቧ ቅጥነት፣ የዳሌዋ ስፋት እያልን የምናደንቃት ኮረዳ ቦርጫም ባለመሆኗ ያተረፈችው ውበቷን ብቻ ሳይሆን ህይወቷንም ጭምር ነው፡፡
የቦርጭ አለመኖር ከሚሰጠው ያማረ ቅርፅና የተስተካከለ ሰውነት በተጨማሪ ጤናማ በመሆን በህይወት የመቆየታችንን እድል ከፍ ለማድረግ እንደሚያስችለን የሚያረጋግጡ መረጃዎች እየወጡ ነው፡፡
ዘ ኒው ኢንግላንድ ጆርናል ኦፍ ሜዲስን በቅርቡ ይፋ ያደረገው አንድ መረጃ እንደሚጠቁመው፤ በወገባችን ዙሪያ (በሆዳችን) አካባቢ የሚከማቸው ስብ (ቦርጭ) ለከፍተኛ የጤና ችግር ባስ ሲልም ለሞት ሊዳርገን ይችላል፡፡ ብዙዎቻችን በሆዳችን ዙሪያ የሚታየው ቦርጭ ውበታችንን ወይም የአለባበስ ስታይላችንን በማበላሸቱ ወይንም ያሻንን እንዳንለብስ እንቅፋት በመሆኑ ከመበሳጨት ወይንም ከመማረር በዘለለ ችግሩ በጤናችንና በህይወታችን ላይ ስለሚያስከትለው መዘዝ ስንጨነቅ አንታይም። ቦርጫችንን አንዳንዴም የሃብት መለኪያ አሊያም የኑሮ ምቾት ማሳያ በማድረግ የምንኮራበት ጊዜም ይኖራል፡፡ በእርግጥ ይህ ሁኔታ ዛሬ ዛሬ እምብዛም ተቀባይነትን አጥቷል፡፡ የውፍረት (ቦርጭ) መንስኤ ሰውነት ለሃይል አቅርቦት ከሚፈልገው መጠን በላይ ምግብ መመገብ ሲሆን፤ ምግቡ በስብ መልክ በሰውነታችን ውስጥ ስለሚከማች ለቦርጭ መፈጠር ምክንያት ይሆናል፡፡ የምንመገበው ምግብ ለሰውነታችን የሃይል ምንጭ የሚሆነው በምግብ ስልቀጣ ስርዓት ወደ ጉሉኮስነት በመቀየር ነው፡፡ ሰውነታችን የሚያስፈልገውን ያህል ከተጠቀመ በኋላ ከሚፈልገው በላይ የሆነውን ምግብ በሰውነታችን ውስጥ በስብ መልክ እንዲከማች ያደርጋል። እነዚህ የስብ ክምችቶች በተለያዩ የሰውነታችን ክፍሎች ውስጥ በስጋ ላይ እየተለጠፉ (እየተደረቡ) ይቀመጣሉ፡፡
ሰውነታችን የምግብ እጥረት ሲያጋጥመው ወይንም በቂ ኃይል ሊሰጠን የሚችሉ ምግቦችን ለማግኘት ሳንችል ስንቀር፣ ሰውነታችን እነዚህን የስብ ክምችቶች እያቀለጠ ለሃይል ምንጭነት ይጠቀምባቸዋል፡፡ በሰውነታችን ውስጥ የሚገኘው የስብ ክምችት መጠን በየጊዜው እየጨመረ ሲመጣ፣ በሆዳችን አካባቢ በመበራከት ቦርጭን ይፈጥራል፡፡ ይህም ለቦርጫማነትና ተያያዥ ለሆኑ የጤና ችግሮቹ እንድንጋለጥ ያደርገናል፡፡
ቦርጫችን ከቁመታችን ተመጣጣኝ ካልሆነና ከተገቢው መጠን እየጨመረ ከሄደ ከፍተኛ የአደጋ ምልክት ውስጥ መሆናችንን አመላካች እንደሆነ ይኸው መረጃ ይፋ አድርጓል፡፡ የቦርጭ ልክንና የስብ መጠን ክምችቶችን ለማወቅ የሚረዱ ሶስት አይነት መንገዶች መኖራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ እነዚህ ዘዴዎች መፍትሄ ለመሻት እንደሚረዱም ጠቁሟል።
የሰውነታችን ክብደት ከቁመታችን ጋር ተመጣጣኝ መሆኑን፣ በከፍተኛ አደጋ ውስጥ መሆን አለመሆናችንን መለኪያ መስፈርቱ BMI (body max index) ያረጋግጥልናል፡፡ ይህ ዘዴ በሆድ አካባቢ የሚገኘውን የስብ ክምችት መጠን ለማወቅም እንደሚረዳን ይኸው መረጃ ይጠቁማል። ሌላው ችግሩን ማወቂያ መንገድ የወገብን ዙሪያ ክብ (ክበባዊ መጠን) ለማወቅ የሚያስችለን ሲሆን በዚህ ዘዴ በሆዳችን አካባቢ የተከማቸውን የስብ መጠን ለማወቅና ችግሩ በጤናችን ላይ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ ለመረዳት ያስችለናል፡፡ ይህንኑ ቦርጭ ሳቢያ የሚፈጠርብን አደጋ ለማወቅ የምችልበት ሌላውና አስተማማኝ ዘዴ የወገባችንን ዙሪያ ልኬት ለዳሌያችን ልኬት በማካፈል የሚገኘው ውጤት ነው። ይህ ውጤት ለሴቶች 0.8፣ ለወንዶች ደግሞ ከ0.9 -1 ድረስ መሆን ይኖርበታል፡፡ ልኬቱ ከዚህ መጠን ከበለጠ በሆዳችን ላይ ከባድ የስብ ክምችት (ቦርጭ) መኖሩን ያመለክተናል። ይህ መንገድ አስተማማኝ ዘዴ በመሆኑ ትክክለኛ ውጤቱን በማሳየት ወደሞታችን የምናደርገው ጉዞ ምን ያህል የቀረበና የራቀ እንደሆነ ለማወቅ እንደሚረዳን መረጃው አመልክቷል፡፡
ቦርጭ በሰውነታችን ውሰጥ ጎጂ የሆኑ የኮሌስትሮል ክምችቶች እንዲኖሩ በማድረግ ለከፍተኛ የደም ግፊትና የልብ በሽታ ችግሮች ሊያጋልጠን ይችላል፡፡ ሰውነታችን በኢንሱሊን እንዳይታዘዝ በማድረግም ለስኳር ህመም ያጋልጠናል፡፡ በአጥንት መገጣጠሚያዎቻችን ላይ ጫና በመፍጠር ለተለያዩ ህመሞች እንድንጋለጥ ያደርገናል፡፡
ለአንጀት፣ ለጡት፣ ለማህፀንና ለፕሮስቴት ካንሰሮች ሊያጋልጠን ይችላል፡፡ ለአተነፋፈስ ችግሮች፣ ለስትሮክና ለሀሞት ጠጠር በሽታም ሊዳርገን ይችላል፡፡
በሆዳችን ውስጥ የተከማቸው ስብ (ቦርጫችን) ያለ ጊዜያችን የመሞት እድላችንን በእጅጉ የሚያፋጥን መሆኑን የጠቆመው መረጃው፤ ችግሩ በእድሜ ከገፉ ሰዎች ይልቅ ወጣቶችን ወደ ሞታቸው እንደሚወስዳቸው ገልጿል፡፡ በቦርጭ ሳቢያ ለሚከሰተው ሞት ዋንኛ ምክንያቱ በደም ውስጥ የሚገኘው የቅባት መጠን መጨመር ሲሆን ይህም ደማችንን በማወፈር ልባችን በደም መርጨት ሂደቱ ላይ ጫና እንዲደርስበት ያደርገዋል፡፡ ይህም የልባችንን ደም የመርጨት አቅም በመፈታተን ለአደጋ እንድንጋለጥ ያደርገናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በሆዳችን አካባቢ የተከማቸው ስብ በራሱ የሚያመነጫቸው ኬሚካሎች በተፈጥሮአቸው ስር ሰደው የሚቆዩ በሽታዎችን የማባባስና እንዲነሳሱ የማድረግ ባህሪይ አላቸው፡፡ በአጠቃላይ ቦርጭ ወደ ሞታችን የምናደርገውን ጉዞ በማሳጠር ያለ ጊዜያችን ለህልፈተ ህይወት ሊዳርገን የሚችል መሆኑን በመገንዘብ ቦርጫችንን በመቀነስ (በማጥፋት) ከአካላዊ ውበታችን በላይ ለህይወታችን መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ቦርጫችን ህይወታችንን ሊያስከፍለን አይገባምና!
ምንጭ  sodere

No comments:

Post a Comment