Saturday, August 24, 2013

“አገራችንን በእርቅ እንታደጋት” ዶ/ር ተጋ “ዋስትና የናፈቃቸው ባለስልጣናት አሉ”

“አገራችንን በእርቅ እንታደጋት” ዶ/ር ተጋ “ዋስትና የናፈቃቸው ባለስልጣናት አሉ”

የኢህአዴግ ባለስልጣኖችና ደጋፊዎች ከየትኛውም ዜጋ በላይ ዋስትና እንደሚፈልጉ በመግለጽ ዶ/ር ተጋ ለንዳዶ ለጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ ተናገሩ። በአገራቸው ጉዳይ ላይ በተለይም በዕርቅ ዙሪያ በርካታ ጽሁፎችን ሲያቀርቡና ሲንቀሳቀሱ የቆዩት ዶ/ር ተጋ ለንዳዶ በኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ በኃላፊነት ሲሰሩ የቆዩ ሲሆን ከአገራቸው ውጪም በኬንያ፣ በሞዛምቢክ፣ በስዊትዘርላንድና በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች በከፍተና ኃላፊነት ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ በተለይም በዎርልድ ቪዥን፣ በተባበሩት መንግሥታ፣ በዓለምአቀፍ አብያተክርስቲያናት ካውንስል፣ … የሰጡት የዓመታት አገልግሎት ተጠቃሽ ነው፡፡ በአገር ውስጥና በውጪ አገራት የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ከፍተኛ ትምህርታቸውን የተከታተሉት ዶ/ር ተጋ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የዕርቅ፣ የሰላምና የፍትሕ ሒደት ውስጥ የተጫወቱት መጠነኛ ሚና በአገራቸው ተግባራዊ ሆኖ ለማየት የሚመኙና ለዚያም የሚቻላቸውን ጥረት ሁሉ ሲያደርጉ መቆየታቸው እስካሁን የሠሩት ሥራ ምስክር ነው፡፡ ከዚህም ሌላ ዶ/ር ተጋ ለንዳዶ የአገር ውስጥና የውጭ ስድስት ቋንቋዎችን አቀላጥፈው የሚናገሩ ናቸው፡፡
“እውነተኛ እርቅ የሚያስፈልግበት ወቅት ላይ ነን” የሚሉት ዶ/ር ተጋ የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በመረዳት አገራችን ከምትገኝበት አደጋ መታደግ የሁሉም ዜጋ ግዴታ እንደሆነ አመልክተዋል። በማያያዝም በደል ሲበዛ ህዝብ እንደሚያምጽ በመጠቀስ ሳይረፍድ ሁሉም ወገኖች ለእርቅ ራሳቸውን እንዲያዘጋጁ ጠይቀዋል።
እርቅና ሰላም ለማውረድ የሚችሉ ዜጎች አድፍጠው መቀመጣቸውን የጠቆሙት ዶ/ር ተጋ “የፖለቲካ መናኞች” ያሉዋቸውን እነዚህ ዜጎች ከተደበቁበት በመውጣት ባገራቸው ጉዳይ ተሳታፊ ሊሆኑ እንደሚገባ አሳስበዋል።
እውነተኛ እርቅ ቢጀመርና፣ ለማስታረቅ የሚመጥን ስብእና ያላቸው ወገኖች የሚካተቱበት አስታራቂ ቢሰየም ህዝብ እውቅና ለመስጠት እንደማይቸገር ያስታወቁት ዶ/ር ተጋ “ከኢህአዴግ ወገን እርቅ የሚፈልጉና ለልቡናቸው የቀረቡ ሰዎች አሉ። እነሱም ሰው ናቸውና ሰላም ይፈለልጋሉ። ራሳችሁን መናኝ ያደረጋችሁ ከተደበቃችሁበት ውጡና ኢትዮጵያን እናድን” ሲሉ ጥሪ አስተላልፈዋል። ሙሉ ቃለ ምልልሳቸው እንደሚከተለው ተቀናብሯል።
ጎልጉል፦ በተደጋጋሚ ስለ እርቅ ይናገራሉ። በርግጥ መፍትሔ ይኖረዋል? ዶ/ር ተጋ፦ ከእርቅ ውጪ ምንም አማራጭ የለም። አለ?
ጎልጉል፦ አሁን ኢህአዴግ ከያዘው አቋም አንጻር “እርቅ ዋጋ የለውም” የሚሉ አሉ፤ ዶ/ር ተጋ፦ ስለነዚህ ወገኖች በተለይ የምለው ነገር የለም። በኔ እምነት እርቅ፣ ትክክለኛው የእርቅ መንገድ ተሞክሯል የሚል እምነት የለኝም። ስለዚህ ትክክለኛው እርቅ፣ እውነተኛው አርቅ መሞከር አለበት። እኔ እንደምረዳው ከሁሉም ወገን ትክክለኛ እርቅ ከቀረበ ተቀባይ የማይሆንበት ምክንያት የለም።
ጎልጉል፦ትክክለኛ እርቅ ሲሉ ምን ማለትዎ ነው? ዶ/ር ተጋ፦ ከፍቅርና የሚመነጭ ፍርሃት ሰዎች አምነው እንዲገዙ ያደርጋቸዋል። ፍርሃት ስል አምነው ለሰየሙት መንግሥት ክብር መስጠትና መገዛትን ነው። በሌላ በኩል ደግሞ መሳሪያ ያላቸውና ህግ ያረቀቁ ክፍሎችም ህዝብን መግዛት ይችላሉ። እነዚህ ክፍሎች እኔን ምሰል። እኔ የምልህን አድርግ። አንተ ቦታ የለህም። የአንተ ድርሻ መገዛትና መገበር ብቻ ነው። አንተ ዝም ብለህ ከመገዛት ውጪ ሌላ ተግባርና ድርሻ የለህም በማለት በጉልበት ይገዛሉ። ልክ አሁን እንደሚደረገው ማለት ነው። በሌላ ወገን “አማራጭ ነን”  ብለው በጉልበት እየገዛ ያለውን ለመገልበጥ የሚታገሉ አሉ። ገለልተኛ ሆነው የሚኖሩና የሸሹ ወገኖች አሉ። እነዚህ የሸሹ ሰዎች “የፖለቲካ መናኞች” ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ሌሎችንም አካትቶ ለመታረቅ ሲስማሙ ትክክለኛው እርቅ ይመጣል። ሳይሞከር አይሳካም ማለት አይቻልምና እንሞክረው።
ጎልጉል፦ ያልተቻለው እኮ እነዚህን ወገኖች ማሰባሰብ ነው? በተለይም ኢህአዴግን ወደ እርቅ የሚገፋው ጉዳይ የለም የሚሉም ወገኖች አሉ። ኢህአዴግ ምን አስፈርቶት ወደ እርቅ ይመጣል? የሚሉ አሉ፤ ዶ/ር ተጋ፦ ለጊዜው ሃይል አለኝ ብሎ ከተራራ ላይ አልወርድም። መሳሪያ አለኝና እርቅ አይበጀኝም። ጡንቻ አለኝና ሰላም አያሻኝም በማለት ኢህአዴግ የሚያከር ከሆነ የተጎዱ፣ የተረገጡ፣ የተገፉ፣ የከፋቸው፣ የባሰባቸው ቀኑ ሲደርስ “አታስፈልግም” ብለው ይነሳሉ። ዓለም ብዙ አሳይታናለች። የህዝብ ቁጣ ሲነሳ የሚደርሰው አደጋ የከፋ ነው። እኔን ዘወትር የሚያስጨንቀኝ ይህ ነው። የኢህአዴግ ሰዎችም ቢሆኑ ሰዎች ናቸውና ከደጋፊዎቻቸው ጭምር ይህንን ሳያስቡት ውለው ያድራሉ ብዬ አላስብም። ደግሞም ያስባሉ። እንደውም ከማንኛቸውም በላይ የኢህአዴግ ደጋፊዎች እውነተኛ እርቅ የሚመኙበት ወቅት ላይ ለመሆናቸው ጥርጥር የለውም። ዋናው ጉዳይ ግን እንዴት …
tegga
ዶ/ር ተጋ ለንዳዶ
ጎልጉል፦ ኢህአዴግ እርቅ ይፈልጋል እያሉ ነው? ዶ/ር ተጋ፦ በሚገባ። የኢህአዴግ አመራሮችና ደጋፊዎች እኮ ሰዎች ናቸው። አሁን አገሪቱ ላይ ያለው አደጋ ያሰጋቸዋል። ከሁሉም በላይ ሰላም ለነሱም ያስፈልጋቸዋል። ያለ ስጋት ተራ ሰው ሆነው መኖር የሚፈልጉ አሉ። የግፍና የጭቆና መጠን ሲያልፍ ህዝብ እንደሚነሳ ጠንቅቀው ያውቃሉ። የግፈኛ መሪዎች መጨረሻ ምን እንደሚመስል ይረዳሉ። ችግሩ ያለው እነሱና ደጋፊዎቻቸው ወደ እርቅ እንዲመጡ የሚኬድበት መስመር አግባብ ያለው መሆኑ ላይ ነው። የመተማመን ችግር አለ።
ጎልጉል፦ እርቅ የጀመሩና አሁንም እየሰሩ ያሉ አሉ? ዶ/ር ተጋ፦ ካሉ ጥሩ ነው። እኔ ግን የማወራው ሌሎች ስለጀመሩት እርቅ አይደለም። እኔ የምናገረው የእውነተኛው እርቅ መንገድ ለገባቸው፣ የእርቅ ሃሳብ ላላቸው፣ ያልተነካኩና ለእርቅ ተግባር ቢነሱ የህዝብ ይሁንታና አመኔታ ማግኘት ለሚችሉ፣ ኢህአዴግም አክብሮ ሊያነጋግራቸው ፈቃደኛ ይሆናል ብዬ ለማምንባቸው ክፍሎች ነው። እርቅ ጀመሩ የሚባሉትን እነዚህን ሰዎችም ሆኑ ክፍሎች አላውቃቸውም። የምናገረው ቢጀምሩት ይሳካላቸዋል ብዬ ለማምንባቸው ሰዎች ለህሊናቸው ነው። የአገራችን ጉዳይ ያገባናል ለሚሉ ጨዋ ስብዕና ላላቸው ወገኖች ነው። እንግዲህ ይህንን ስል ከሁሉም ወገን ኢህአዴግን ጨምሮ ነው። አሁን አገራችን ያለችበት አሳሳቢ ወቅት ጤና ለነሳቸው፣ የወደፊቱ ትውልድ እድልና እጣ ፈንታ ግራ ላጋባቸው የኢትዮጵያ ልጆች ነው።
ጎልጉል፦ እውነተኛ እርቅ ምንድ ነው? ዶ/ር ተጋ፦ ስለ አቀራረቡ መናገሩ የሚሻል ይመስለኛል። ከላይ የጠቀስኳቸው ክፍሎች ውስጥ አገራችንን ሊታደጉ የሚችሉ፣ የመጪውን ትውልድ መከራ ሊገፉ የሚችሉ ነገር ግን ዝምታን የመረጡ የተከበረ ስብእና ያላቸው ወገኖች አሉ። እነዚህ ዝምታን የመረጡ ወገኖች ዝምታን የመረጡበት በርካታ ምክንያቶች ይኖራቸዋል። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከውስጥም ሆነ ከውጪ ስድድብ ነው። አንዳንዴ ቃላት እንኳ አይመረጥም። ሰው በስድብ ፖለቲካና ባለመከባበር የሚደረገው አተካሮ የሰለቸው ይመስለኛል። አንግዲህ እንዲህ ያለው መንገድ አልመች ብሏቸው ዝም ያሉትን ከተሸሸጉበት እንዲነሳሱ ማድረግ የመጀመሪያው ስራ ነው። ሌላው እርቅ የምትጠይቀውን ክፍል ማክበር ነው። እየዘለፍክና እያዋረድክ እርቅ መጠየቅ በባህላችንም ቢሆን አያስኬድም። በመከባበር ልዩነትን ማሳየትና ተቃውሞን መግለጽ የሚቻልበት መንገድ ሲፈጠር አድማጭ ማግኘት ይቻላል። በዚህ መልኩ መነጋገር ይጀመራል። እውነተኛ እርቅ የሚጀመረው የእርቁ አጀማመር ክብር የተሞላበት ሲሆን ነው። ሲጀመር መከባበርና የህዝብን ይሁንታ ማግኘት ከተቻለ የቀረው ጉዳይ ሂደት ነው የሚሆነው። ራሳቸውን ያከበሩና የጸዳ ማንነት ያላቸው ወገኖች ከየትኛውም ወገን ድጋፍ አላቸው። ከበሬታም አይነፈጉም። ኢህአዴግ ራሱም ቢሆን ሊገፋቸው አይችልም። አላማቸውና መሰረታቸው እርቅ ማውረድ መሆኑ ከተረጋገጠ ሊገፉ ወይም እምቢ ሊባሉ የሚችሉበት መንገድ የለም። ሁሉም ነገር የሚመነጨው ከስብዕናቸው ነውና ስብዕናቸው ያማረ ሰዎች ተሰባስበው እርቅ ላይ ቢሰሩ የሁሉም ስጋት ተቀረፈ ማለት ነው። ሌላ ትርጉም ካልተሰተው በቀር እርቅ አሁን ላለችው ኢትዮጵያ ፈውሷ ነው።
ጎልጉል፦ የሐይማኖት መሪዎች ሚና ምን ሊሆን ይችላል? ዶ/ር ተጋ፦ የሐይማኖት መሪዎች ነው ያልከው? እንደው ለመሆኑ እዛ ደረጃ የደረሱ አሉ? ካሉ ጥሩ ነው። እኔ ግን እስካሁን አላየሁም። የራሳቸው የግል አመለካከት ቢኖራቸውም ለጊዜው እሱን ወደ ጎን አድርገው ለእርቅ ቢሰሩ ደግ ነው። ግን …
ጎልጉል፦ ቄስ ገመቺስና ቄስ ኢተፋ ጎበና የጀመሩት እርቅ ነበር፤ ዶ/ር ተጋ፦ ለትግል መንስዔ የሆኑ ሰዎች የእርቅ አፋላላጊ መሆን የሚችሉ አይመስለኝም። ከጅምሩ የህዝብን ይሁንታ ማግኘትና አለመነካካት ያልኩት እዚህ ጋር ይመጣል። ከቤተክርስቲያን ሃላፊነት በላይ በእርቅና በሰላም ፍልስፍና ማመን ይቀድማል። ራሳቸውን ለሰላምና ለእርቅ ፍልስፍና ያስገዙ ሰዎች የእርቅን ሂደትና የሚያስከፍለውን ዋጋ ስለሚረዱ እንዲህ አይነት ሰዎች ቢሆኑ ይመረጣሉ ባይ ነኝ። አሁን የጠቀስካቸው ወገኖች የጀመሩት ስራ ድጋፍ የሚያሻው ደረጃ ከደረሰም ማገዝ ነው።
ጎልጉል፦ በአንድነት ያምናሉ? ዶ/ር ተጋ፦ አንድነት የተሰጠን ነው። እምነት ነው። በፍጹም ሊፋቅ አይችልም። አንድነት ውስጥ ልዩነት፣ በልዩነት ውስጥ ደግሞ አንድነት አለ። የምናምረው በልዩነታችን ነው። በልዩነታችን ውስጥ የሚፈጠረው አንድነት ደግሞ ያደምቀናል። ልዩነት በየጊዜው የሚያድግ፣ ወደፊትና ወደኋላ የሚለጠጥ የላስቲክ ይዘት ያለው ነው። ስለዚህ ይህንን እንደ ላስቲክ የሚለጠጥ ልዩነት ስንይዘው፣ “ያንተ ማንነት እኔን አይረብሸኝም” የሚለው እሳቤ ውስጥ ሁልጊዜም መኖር እንችላለን። ያንተ ቋንቋ፣ ማንነት፣ አስተሳሰብ፣ አያስፈልገኝም የሚል ጉዳይ ከተነሳ የላስቲክ ይዘት ያለውን ልዩነት ባህሪውን ወደሚሰበርና የሚቀነጠስ ቁስ ይቀይረዋል። እንዲህ ያለው እርምጃ አደጋ አለው። እኔ እንግዲህ እንዲህ ያለውን አስተሳሰብ ከሚቃወሙ የአንድነት አማኞች ውስጥ ነኝ …
ጎልጉል፦ ስለ እርቅ እንመለስና የውጪ ሃይሎች /መንግስታት/ ካልገቡበት አይሆንም የሚሉ አሉ፤ በተለይም ተጽዕኖ ፈጣሪ አገሮች፤ ዶ/ር ተጋ፦ እስከማውቀው ሕዝብ እውቅና የሰጠው እርቅ ስለመከናወኑ አልተሰማም። እኔ በግል ህዝብ እውቅና የሰጠው እርቅ ስለመኖሩ መረጃ የለኝም። በመጀመሪያ እርቅ በጓዳ ሲሆን ክብር የለውም። እርቅ በግልጽና ባደባባይ መሆን አለበት። ከላይ የገለጽኳቸው ወገኖች ከተሸፈኑበት መጋረጃ ከወጡና ለእርቅ ከሰሩ ብዙ ርምጃ መራመድ ይቻላል። የውጪ ሃይሎችን ማካተት ተገቢ የሚሆንበት አግባብ ብዙ ነው። እንደውም በገሃድ እርቁ ሲጀመር ለእርቁ ስራ የሚተባበሩ አገራትም አብረው መገለጽ አለባቸው። ለምሳሌ በኤርትራ ጉዳይ ላይ ኖርዌይ ብዙ ሚና ተጫውታለች። በወቅቱ ሚናዋ ደስተኛ ባልሆንም አስፈላጊ የሆኑ አገሮች እንዲካተቱ ማድረግ ተገቢ ይመስለኛል።
ጎልጉል፦ በተደጋጋሚ ዝምታን የመረጡ እንዲነሱ ይጠይቃሉ። በውል ስም ጠርተው ለዚህ ተግባር ተነሱ የሚሏቸው ወገኖች ካሉ? ዶ/ር ተጋ፦ ብዙ ታሪክ መለወጥ የሚችሉ ወገኖች አሉ። ራሳቸውን ከአገራቸው ፖለቲካ አግልለው የመነኑ አሉ። ራሳቸውን የፖለቲካ ባህታዊ ያደረጉ አሉ። እነዚህ ባህታዊ ፖለቲከኞች እንዴት እንዲቀሳቀሱ ማድረግ እንደሚቻል ያሳስበኛል። ብዙ እርቅ ላይ መስራት የሚችሉ ወገኖች አሉ። እነዚህም ወገኖች ከሸፈቱበት የ”አያገባኝም” መንገድ ተመልሰው ማየት እፈልጋለሁ። ስለዚህ ድንገት ቢሰሙኝ ብዬ ነው ደጋግሜ የጠቀስኳቸው።
ጎልጉል፦ ፖለቲከኛ ነበሩ? አሁንስ? ዶ/ር ተጋ፦ ፖለቲከኛ አይደለሁም። አጥብቄ የምጠየፈው ነገር ነው። አንዴ እዚህ፣ አንዴ እዚያ የመርገጥ ባህሪ የለኝም። የመገለባበጥ ነገር አይገባኝም። አቋራጭ ብሎ ነገር አላውቅም።
ጎልጉል፦ ግን በቂ ልምድ ያለዎት ይመስላል፤ ዶ/ር ተጋ፦ (ሳቅ ብለው) … ልምድ!! ስለ አገራችን ፖለቲካ አንድ ነገር ልበል። የእኛ ህዝብ ቦይ ነው። መንገድ ካሳየኸው ዝም ብሎ ይጎርፋል። አሁን ታዲያ ቦዩ በዛ። ቦዮቹ ደግሞ ትንንሽ ሆኑ። ትንንሽ ስም ያላቸው ሆኑና እንደ ስማቸው ትንሽ፣ ትንሽ ሰዎችን ይዘው ቀሩ። እነዚህ ትንንሽ ቦዮች የጥቂት ብልጣብልጦች መጠቀሚያ ሆኑ። ባህሪያቸውና ተፈጥሯቸው ትንሽ በመሆኑ ጥቂቶች አትራፊ ሆኑና አብዛኞች ከሰሩ። ይህ አካሄድ ያላስደሰታቸው አብዛኞች ራሳቸውን አቀቡ። አድፋጮች በዙና /silent majority/ ተባሉ። ከስማቸው እንደምንረዳው እነሱ ይበዛሉ። አሁን ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት እነዚህ ዝምተኛ፣ ባህታዊ ፖለቲከኞች፣ የመነኑ ዜጎች ተመልሰው ለእርቅና ለሰላም እንዲሰሩ ማሳሰብ የሁሉም ቀና ዜጋ ተግባር ሊሆን ይገባል። እኔ እንግዲህ እንደዚህ አስባለሁ። የተደበቁ ተመራማሪዎች አሉ። ሌሎች አገራትን የሚጠቅሙ ክቡር ዜጎች አሉን። አገራቸውን የሚወዱ ህዝብን የሚፈሩ አሉ። ከሁሉም በላይ ለህሊናቸው የሚኖሩ ዜጎች አሉ። ኢትዮጵያ የልጆች ደሃ አይደለችም። እነዚህ ዜጎች ለህዝብ ሲሉ፣ አገራቸው ሰላምና እርቅ እንዲወርድላት ሲሉ ከተደበቁበት ሊወጡ ይገባል።
ጎልጉል፦ ከህወሃት ሰዎች ጋር ይተዋወቃሉ? ዶ/ር ተጋ፦ የቀድሞውን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ስዩም መስፍንን አውቃቸዋለሁ፤ አብረን ተምረናል። ባለስልጣን ከሆኑ በኋላ ተገናኝተንም ነበር። በግል በእርቅ ዙሪያ ላነጋግራቸው እችላለሁ። ሌሎችም ሰዎች አሉ። ኢህአዴግ ውስጥ ቀና ሰዎች እንዳሉ መታመን አለበት። ቀና የትግራይ ልጆች አሉ። የወደፊቱ ችግር የሚያሳስባቸው ጥቂት አይደሉም። ደጋግሜ እንደነገርኩህ ዋስትና የሚናፍቁ ባለስልጣኖች ብዙ ናቸው። ሰላም የሚመኙ ብዙ ናቸው። መንገዳቸውን መመርመር የሚፈልጉ ጥቂት አይደሉም። ግን በስድብና በጥላቻ ሊሆን አይችልም። በመከባበር የሚመሰረት መቀራረብ ወደ አንድ የእርቅ ሃሳብ ያመጣል። ጊዜ ቢወስድም መጀመር አለበት። ሲጀመር ግን በክብር መሆን አለበት። ህዝብም እውቅና የሚሰጠው ሊሆን ይገባል።
ጎልጉል፦ እርስዎ የሚያምኑበት እርቅ በዋናነት ምን መያዝ አለበት? ዶ/ር ተጋ፦ እርቅና ሰላም ከፍትህ ጋር። ፍትህ የሌለበት እርቅ ዋጋ የለውም። ሰላምም አያመጣም። ግብጽ ጥሩ ምሳሌ ናት። አሁን የተነሳውን የፕሬዚዳንት ሙርሲን ደጋፊ ምን ታደርገዋለህ። ፍትህ ካላገኘ ለመሞት ተነስቷል። በሌላ በኩል ሙርሲን አውርደው የተቀመጡ አሉ። ለሙርሲ ደጋፊዎች ምላሽ ቢሰጥ አውርደው የተቀመጡትና የፈለጉትን ለመምረጥ ጊዜ ገደብ የተቀመጠላቸው ይነሳሉ። ሲጀመር ፍትህና እርቅ ተጣምረው ባለመከናወናቸው ችግሩ እየተባበሰ ሄደ። ስውር ጉዳዮች እንዳሉ ሆነው ማለቴ ነው። ስለዚህ እርቅና ፍትህ የሚለያዩ ነገሮች አይደሉም። ፍትህ ያለበት እርቅ እንዲሰፍን ተግተን መስራት አለብን። አገራችን ያለችበት ሁኔታ ቸል የሚባልበት አይደለም። በኋላ ሁላችንንም ይቆጨናል። እርቅ ላይ ትኩረት ማድረግ ግድ ነው። የፖለቲካ ለውጥ እንኳን ቢኖር የተዘራውን ክፉ ዘር ለማክሰም እርቅ ግድ ነው።

ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (http://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡
posted by Aseged Tamene
source.. https://freedom4ethiopian.wordpress.com/2013/08/22/1181/

No comments:

Post a Comment