Thursday, August 22, 2013

የሰማያዊ ፓርቲ ያላቻ ጋብቻ (ከአቶ ይድነቃቸው ከበደ)

መንግስት ተግባሩን ሣይወጣ ቀርቶ መንደርተኛና ቧልተኛ ሲሆን እንዴት ያሳፍራል ! ይህን ለመፃፍ ያነሣሣኝ አዲስ ዘመን ጋዜጣ “ የሰማያዊ ፓርቲ ጥቁር ተግባራት ” በሚል በገፅ 3 አጀንዳ ላይ እንዲሁም በኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪን በተጨማሪ ዛሚ ሬዲዮ ጣቢያ የክብ ጠረጴዛ ውይይት እና በሬዲዮ ፋና በዜና እና በልዩ ዘገባ የሚተላለፉ ፕሮግራሞች፤በተለያዩ አካባቢዎች በሚካሄዱ ጥቃቅን አነስተኛ ስብሰባዎችና ሰልፎች የሚሰሙ መፈክሮች የመንግስትን ፍርሃቱን እና ውንጀላ በሚገባ የሚያሳዩ በመሆናቸው ነው፡፡Yidenachew Kebede
መንግስት ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ለጥያቄ አቅራቢዎች የሚያስርበት እና የሚያሰቃይበት አዋጅ ማውጣት ይቀለዋል፤ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓ.ም መነሻውን 4 ኪሎ የሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት መድረሻውን ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ያደረገ ታላቅ የተቃውሞ ሠልፍ ተደርጓል፡፡ በዕለቱም ለመንግስት የቀረበለት ጥያቄ የሰብዓዊ ጥሰቶች እንዲስተካከሉ፣የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች እንዲፈቱ፣በዓይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት እንዲቆም በዚህም ምክንያት የታሰሩት እንዲፈቱ፣የኑሮ ውድነቱ ማሻሻያ እንዲደረግበት እና የተፈናቀሉ ዜጎች ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ የሚል ጥያቄዎች ናቸው፤እጅግ በሰለጠነ እና ሠላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄው ለመንግስት የቀረበ ሲሆን መንግስትም ለዚህ ምላሽ የሦስት ወር የጊዜ ገደብ ተሰጥቶታል፡፡
ይሁን እንጂ መንግስት ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ስም ማጥፋት ዘመቻውን ቀጥሎበታል፤መንግስት ስም ለማጥፋት ብሎ ያነሳቸው አንኳር ሀሳቦች መሰረታዊ የሰው ልጅ ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ናቸው፡፡ መንግስት ይህን ለመረዳት ተጨማሪ 22 ዓመታት ቢያስፈልገውም ህዝብ ግን ያጣውን ነፃነት ለማግኘት ትግሉን ይቀጥላል፤ ለህዝብ የመብት ጥያቄ የሆኑት መንግስት ለመወንጀል የሚያነሳቸው ሃሳቦች በጥቂቱ እንመልከት፡፡
1ኛ. “በ1997 ዓ.ም በቅንጅት ተሳትፎ ከፍተኛ ሚና የነበራቸው ዛሬ ደግሞ በአዲስ ኮፍያ የሚንቀሳቀሱ” የተባለው ቁጥር አንድ ውንጀላ ነው፤ ምላሹ ደግሞ ፡- ይህ ሀሳብ ከእውነት የራቀ አይደለም ከዛሬ 8 ዓመት በፊት በሺዎች የሚቆጠሩት የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች ይቅሩና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ለነፃነት እና ለመብት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የተደረገበት ወቅት ነው፤ በወቅቱ ለሚፈለገው ነፃነት ደም ተከፍሎበታል፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ባዶ እጁን አደባባይ ወጥቶ “ድምፃችን ይከበር” በማለቱ አገርን ሊወር እንደመጣ ጠላት በመከላከያ ሠራዊት ለዛውም በሰለጠኑ ነፍሰ ገዳይ ታሪክ ሁሌም የሚዘክራቸው ኢትዮጵያውያን በግፍ ገሏል፤ በዚህም ምክንያትና በሌሎች የሚፈለገው ነፃነት ታጥቷል፡፡ እናም ያኔ ያጣነውን ነፃነትና መብት መንግስት በአዲስ ኮፍያ ቢለውም እጅግ በሠለጠነና ሠላማዊ በሆነ መንገድ በአዲስ እስትራቴጂ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በፈቀደው መልክ ተደራጅቶ ይህን አምባገነን ስርዓት ታግሎ ለማሸነፍ የሚያደርገው ጥረት ወንጀል የሚሆነው ምኑ ላይ ነው?
2ኛ. “በውጭ ከሚገኙ ፅንፈኛ አክራሪ ኃይል ጋር በመቀናጀት በአረቡ ዓለም የታየውን አብዮት ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት” ይህ ሁለተኛው ውንጀላ ነው፤ ሌባ አባት ልጁን አያምንም የሚባለው ተረት ለዚህ ውንጀላ ተስማሚ ይመስለኛል ምክንያቱም ያሁን መንግስት የበፊት አማፅያን (ወያኔዎች) ከሱዳን፣ ከሶሪያና ከግብጽ ከመሳሰሉት አገራት የጦር መሣሪያና ስልጠና እንዲሁም መሸሸጊያ በማግኘት አዲስ አበባ ቤተ መንግስት መግባታቸውን የሚታወቅ ነው፤ እነሱ በክደት የፈጸሙት ሁሉ ሌላው ያደርገዋል የሚል ከንቱ አሳብ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የተመሠረተው በኢትዮጵያውያን ነው ትግሉም ሆነ ዉጤቱ የኢትዮጵያ ህዝብ ነው፤ ሌላው ደግሞ በአረቡ አለም የታየው አብዮት ኢትዮጵያውያን ከ8 ዓመት በፊት በአስደናቂ ሁኔታ የተገበርነው ነው፡፡ ዛሬ ደግሞ ከ8 ዓመት በፊት ያጣነው አብዮት መንግስት አልሰማና አልለወጥ ካለ የአረቡን አብዮት በኛ አገር ተጨባጭ ሁኔታና ማህበራዊ ንቃተ ህሊና ሠላማዊ በሆነ መንገድ በመስቀል አደባባይ ወጥተን ብናደርገው ወንጀሉ ምኑ ላይ ነው?
3ኛ. “ከውጭ አሸባሪ ግንቦት ሰባት ቴሌቪዥን ጣቢያ ‘ኢሳት’ ጋር በመቀናጀት” ይሄ ደግሞ ሦስተኛ ውንጀላ ነው በመሠረቱ በአገር ቤት ያለው የዳኝነቱ ስርዓት እውነተኛ ፍትህ የሚሠጥ ቢሆን ኖሮ “መልካም ስምና ዝናን በማጉደፍ በተጨማሪም መረጃን የማግኘት መብት በመንፈግ” የወንጀል ክስ መመስረት ይቻል ነበር ግን ምን ዋጋ አለው?፡፡ ይህን ለማለት የፈለኩት አንደኛ ኢሳት መረጃን ለተጠሙ በዓለም ላይ የሚገኙ ኢትዮጲያውያን አይንና አንደበት የሆነ ሚዲያ እንጂ የግለሰብ ወይም በተወሰኑ ቡድኖች የሚንቀሳቀስ ሚዲያ አይደለም፡፡ እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ሚዲያው የእገሌ ድርጅት ነው መባሉ የስም ማጥፋት ወንጀል ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ መረጃን ማግኘት ህገ መንግስታዊ መብት ነው፤ ይሁን እንጂ በአገራችን እኛ የመረጥነው ሳይሆን መንግስት የመረጠልን ሚዲያ ነው የምንመለከተው፣ የምንሰማውና የምናነበው ለዚህም ማሳያ በአገር ውስጥ ትክክለኛ መረጃ የሚያስተላልፉ ጋዜጠኞች መጨረሻቸው ስደት ወይም እስራት ነው፤ ከሀገር ውጭ ያሉ ሚዲያዎች ደግሞ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ ይታፈናሉ በዚህ ምክንያት መረጃ የማግኘት መብታችን በኃይል ተከልክለናል፡፡
4ኛ. “የጥቂት ሙስሊም አክራሪዎች አጀንዳ በመደገፍ አደባባይ ይዞ መውጣት” አራተኛ ውንጀላ መሆኑ ነው፤ ጥቂት፣ አነስተኛ፣ ጥቃቅን የመንግስት አፍ መፍቻ ከሆኑ ሰነባብተዋል፤
“ጥቂቶች ቆራጦች ያልተንበረከክነው
ዛሬን እንሞታለን ነገ ታሪክ ምስክር ነው”
የሚለው የእናንተ የትግል መዝሙር አስታወሰኝ እባካችሁ ትላንትና ለጥቂቶች የነበራችሁ ከፍተኛ ግምት ዛሬ የት ገደል ገባ? የሙስሊም ወንድሞቻችን ትግል የጥቂቶች አይደለም የአብዛኛው ኢትዮጵያውያን ሙስሊም የሀይማኖት ነፃነት ጥያቄ ነው፡፡ በመሆኑም ለአገር የቆመ ፓርቲ ለመብትና ለነፃነት በሰላማዊ መንገድ እታገላለሁ እያለ መብትና ነፃነታቸውን ለማስመለስ ደከመን ሰለቸን ሳይሉ “ድምፃችን ይሰማ” ለሚሉ እውነት ነው ድምፃቸው ይሰማ ብሎ ሰማያዊ ፓርቲ ድምፁን ቢያሰማ የሚያስወነጅለው ምክንያቱ ምንድን ነው?
5ኛ. “ሰማያዊ ፓርቲ ሠልፍ ላይ መካከለኛ እድሜ ላይ ያሉና አዛውንቶች ጭራሹንም በሰልፉ ላይ የሉም በአብዛኛው ለአክራሪዎች ወግኖ የቆመ ኃይል ነው” ይሄ በአምስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ከውንጀላ ይልቅ በኢህአዴግ ቋንቋ የሠልፉን ገፅታ ጥላሸት ለመቀባት ነው፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ታላቅ የተቃውሞ ሠልፍ ሁሉንም የህብረተሠብ ክፍል ያካተተ እንደነበር የአለም ሚዲያ የዘገበው ነው፤በጣም የሚገርመው በ1997 ዓ.ም አደባባይ የወጣውን ወጣት “ አደገኛ ቦዘኔ ” በማለት ሠልፈኛውን እና የሠልፉን ዓላማ የተለየ ለማድረግ መንግስት ያልፈነቀለው ድንጋይ የለም፡፡ አሁን ደግሞ ከ8 ዓ.ም በኋላ በተካሔደው የተቃውሞ ሰልፍ ወጣቱ ብቻ ነው የተገኘው በማለት ለወጣቱ ያለውን ንቀት መንግስት በድጋሚ አረጋግጧል፡፡ እኔ የምለው! ወጣቱ ስለሀገሩ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳይ አያገባውም እንዴ? በተጨማሪም ተገፋን፣ ተበደልን ከሚሉ ሰዎች ጋር ወግኖ መቆም ጥፋቱ ምን ላይ ነው? በኢትዮጵያ ውስጥ በመንግስት ታስቦና ታቅዶ የሚፈፀም በደልና መገፋት በኔ አልደረሰም ተብሎ እንዴት ይታለፋል፤ ዛሬ ከተገፉትና ከተበደሉ ወገኖች ጋር ወግኖ ያልቆመ ነገ ለሱ ማን ሊቆምለት ነው?
በአጠቃላይ ከላይ የተገለፁት ሀሳቦች በመንግስትና ካድሬዎች እና ሚዲያዎች የሚነዙ አሉባልታ ወሬዎች መሆናቸውን ለማሳያት ለመንደርደሪያነት የቀረበ ፅሁፍ ነው፡፡ መንግስት ከሰሞኑ የተያያዘው ነገር ቢኖር ከስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍ ባለ ሁኔታ የሃይል እርምጃ መውሰድ ነው፤ለዚህም ማሳያ በተለያዩ ከተሞች በእስልምና እምነት ተከተዮች ላይ ግድያ እና ድብደባ እንደሁም እስራት እየተካሄደ ነው፤ ቀጣዩ ደግሞ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮች መሆናቸው የዘፈን ደርዳርታ እስክስታ ነው እንደሚባለው ከጠቅላይ ሚኒስተሩ ጀምሮ እስከታችኛው የስልጣን እርከን የተቃዋሚ ፓርቲ በተለይ ሰማያዊ ፓርቲን መንግስት የነገር አባት ( ሽማግሌ) በመሆን በቅርብ ከማያገኛቸው ነገር ግን እንዲህ አይነቱን ውንጀላ ለመፈረጅ ከሚመቻቸው ከግንቦት ሰባት እና ከሙስሊም አክራሪዎች ጋር ፓርቲውን እየዳሩት ይገኛል ፤ጋባቻው ግን ያላቻ ጋባቻ ነው፡፡
በመሆኑም መንግስት በተሠጠው ጊዜ አላፊነቱን በመወጣት እኛ ተበዳዮቹ ብቻ ሳንሆን እናተም በዳዮቹን በጋር በነፃነትና በእኩልነት የምንኖርበት አገር በማቅናት ሁሉ በህግ ፊት እኩል ሆኖ የሚዳኝበትን ጊዜ እናቅርበው፤ አለበለዚያ የምትፈሩት ህዝባዊ አብዮት መምጫው ቀን እሩቅ አይደለም፡፡
ይድነቃቸው ከበድ

No comments:

Post a Comment