Tuesday, September 17, 2013

“የትግራይ ህዝብ ህወሓትን ቢጠላም በሌሎች ፓርቲዎች ላይ ጥርጣሬ አለው” (ከ“ሎሚ” መፅሔት ለቀረቡልኝ ጥያቄዎች)

ሎሚ፡- አብርሃ የልጅነት አስተዳደግህን ምን ይመስላል?… ትምህርትሕን የት ተከታተልክ በሚለው ብንጀምርስ?

አብርሃ፡- ተወልጄ ያደግኩት በትግራይ ሓውዜን ወረዳ ነው። የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን በሓውዜን ካጠናቀቅኩ በኋላ የመሰናዶ ትምህርቴን ደግሞ በዓዲግራትና መቐለ ተከታተልኩ። ከዛ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ትምህርት አጠናሁ። መቐለ ዩኒቨርሲቲ ተቀጠርኩ። 
ሎሚ፡- በልጅነት ያደግክበት አካባቢና በወቅቱ የነበረው የፖለቲካ አየር ምን ይመስል ነበር? 
አብርሃ፡- የልጅነት ጊዜዬ በአንድ በኩል የህወሓት ታጋዮች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ ህዝቡ ለትግል እንዲነሳሳ የሚቀሰቅሱበትና ስለነሱ ‘ጀግንነት’ የሚወራበት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የደርግ ወታደሮች ህዝቡ ‘ከወንበዴዎች’ ጋር እንዳይሰለፍ የሚያስፈራሩበት ነበር። ሌላው የልጅነቴ ትዝታ የሓውዜን ህዝብ በገበያ ቦታ በግፍ የተጨፈጨፈበትና እንደውጤቱም አብዛኛው ወጣት ጫካ የገባበት ነበር። 
የደርግ ስርዓት ከተገረሰሰ በኋላ አንፃራዊ መረጋጋት ቢሰፍንም ሰላማዊ ሰዎች “ደርግን ተባብራችኋል፣ የሽፍታ ዘመድ ናችሁ፣ በህወሐት ትግል አልተሳተፋችሁም፣ ለህወሓት ጥሩ አመለካከት የላችሁም…” ወዘተ በሚል ሠበብ ብዙ ሰዎች በግፍ ታስረዋል፣ ተገርፈዋል፣ ተገድለዋል። 
ልጅ ሁኜ ያጋጠመኝን አንድ ነገር ላካፍልህ። በ1985/86 ዓ.ም ይመስለኛል። እኔ ባደግኩበት መንደር “አንድ ለህወሓት እጅ ያልሰጠ ሽፍታ አለ” በሚል ሰበብ 28 የአካባቢው ሰዎች ታሰሩ። አብዛኞቹ እናቶች ነበሩ። አባቴ ከነሱ ጋር ታስሮ ስለነበር እራት ለማድረስ እናቴ ልካኝ ወደ እስር ቤቱ ሄድኩ። እዛ ስደርስ የታሰሩት ሰዎች ይገረፋሉ፤ ይጮሃሉ። ስቃያቸው ምን ድረስ እንደሆነ ከውጪ ሆኜ ከምሰማው ጩኸት መገመት ይቻል ነበር። ታስረው ከተገረፉት ሦስት ነፍሰ ጡር እናቶችና አንድ የእድሜ ባለፀጋ ህይወታቸው ሲያልፍ ሁለቱ ወንዶች አበዱ።
በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትም ተመሳሳይ ነገር ነበር የተፈፀመው። የሓውዜን አስተዳዳሪዎች ማንኛውም ወጣት የተባለ ለውትድርና እንዲሰለፍ አዘዙ። ወጣቶች ፈቃደኛ ካልሆኑና ካልተያዙ ቤተሰቦቻቸው ይታሰሩና ንብረታቸው ይያዝ ነበር። በዚሕ ምክንያት ብዙ እናቶች እስር ቤት ውስጥ እንዲወልዱ ተገደዋል። በሓውዜን እንዲህ ዓይነት ግፍ እስካሁን ድረስ እየተፈፀመ ያለ ነገር ነው። 
ሎሚ፡- አምባገነን የምትለው የሕወሐት ማዕከል መቀሌ ላይ ሆነህ፣ ለዚያውም መንግስት የሚያስተዳድረው ዩኒቨርሲቲ እያስተማርክ፣ ጠንካራና የሰሉ ሂሶች ማቅረብህ ስጋት አያሳድርብህም? ዛቻ፣ ማስፈራሪያና ጥቃት አጋጥሞህስ ያውቃል? 
አብርሃ፡- እኔ በምፅፋቸውና በምናገራቸው ነገሮች እዚሕ ግባ የሚባል ዛቻ ወይም ማስፈራሪያ ደርሶብኝ አያውቅም። በስልክ እንዲሁም በፌስቡክ በኩል ማንነታቸውን ደብቀው የሚሳደቡ የተወሰኑ አሉ። በጓደኞቼ በኩል ማስጠንቀቂያዎች እንዲደርሱኝም ይደረጋል። ጥቃት ግን አጋጥሞኝ አያውቅም። በአጠቃላይ ህወሐት እስካሁን ድረስ ቀጥተኛ የሆነ ተፅዕኖ አላሳደረብኝም።
ሎሚ፡- የሕወሐት መስራቹ አስገደ ገ/ስላሴ ተቃውሞ በማሰማታቸው በቤተሰቦቻቸው ላይ ሳይቀር ጥቃት ሲዘነዘር፣ ሕወሐት አንተን በጸጥታ ለመመልከት የተገደደበት ምክንያት አለ ብለሕ ታስባለሕ? 
አብርሃ፡- “ህወሓት ለምን በአንተ ላይ ፀጥታን መረጠ?” የሚለው ጥያቄ ህወሐቶችን የሚመለከት ይመስለኛል። ምክንያቱም ስለ እነሱ ውሳኔ ምክንያታዊነት የሚያውቁ እነሱ ስለሆኑ። እኔ መገመት ብቻ ነው የምችለው። እንደኔ እምነት… እኔ ለዓቅመ-መታስር አልደረስኩም። እኔ የማንፀባርቃቸው ሐሳቦች ለህወሐቶች ስጋት የሚደቅኑና ለእስር የሚዳርጉ አይደሉም ብዬ አስባለሁ። በህወሓት ለመታሰር ጠንከር ያለ ትችት ማቅረብ ወይም ለስልጣን ስጋት መሆን አለብህ። ስለዚህ አንደኛው ምክንያት እኔ ስለማላሰጋቸው ሊሆን ይችላል። እኔን አስረው ምን ይጠቀማሉ?… ሁለተኛው መላምት በህወሐቶች እምነት ከኔ በላይ ለፓርቲው ስጋት የሚሆኑት የራሳቸው አባላት አሉ፤ ውስጣቸው በስብሷል። ስለዚህ በራሳቸው አባላት ላይ ተጠምደዋል። የስጋታቸው ምንጭ ውስጣዊ ማንነታቸው ከሆነ በኔ ላይ የሚያተኩሩበት ምክንያት አይታየኝም።
ሎሚ፡- የትግራይ ሕዝብ ተቃውሞ ሊሰማ ያልቻለው ሚዲያዎች ስለማይዘግቡት ነው የሚል አቋም አለሕ፤ የሌሎቹ ክልሎችን ችግሮች ሚዲያዎች ከዘገቡ፣ የትግራዩን ተቃውሞ እንዳይዘግቡ ምን ከልክሏቸዋል ብለሕ ታምናለሕ? መፍትሄውስ ምንድነው?
አብርሃ፡- በሁለት ምክንያቶች ነው። አንደኛ ትግራይ የህወሐት መሰረት ነው። ህወሐት ትግራይን ማጣት አይፈልግም። ምክንያቱም ትግራይን ካጣ ሌላ የሚደበቅበት ስፍራ የለውም። ስለዚህ ህወሐት በትግራይ ህዝብ የሚያደርሰው ጭቆናና ግፍ እንዲጋለጥ አይፈልግም። በመሆኑም ህወሐት ከትግራይ የሚወጣ መረጃን ይቆጣጠራል። በትግራይ ‘ሁሉም ነገር ሠላም’ እንደሆነ አስመስሎ ለማቅረብ ይሞክራል። ሌላው ቀርቶ በ’ፖሊስና ህብረተስብ’ የተሌቪዥን ኘሮግራም ሊቀርቡ የሚገባቸው ወንጀሎች በትግራይ ክልል የተፈፀሙ ከሆነ አብዛኞቹ ተገቢው ሽፋን አይሰጣቸውም። 
ሁለተኛ ከመንግስት ሚዲያ ውጪ ያሉ የዜና አውታሮች ስለትግራይ ትክክለኛ ምስል የላቸውም። የትግራይን ሁኔታ በትክክል የሚያውቁ የሚዲያ ሰዎች አንድም በመንግስት ሚዲያ ውስጥ የሚሰሩና አፈናውን እንዲያጋልጡ የማይፈቀድላቸው ናቸው፤ አለያም ደግሞ ከሚዲያ የራቁ ናቸው። 
ከመንግስት ቁጥጥር ውጪ ያሉ የሚዲያ ሰዎች ደግሞ የትግራይን ህዝብ ከሌላው ኢትዮጵያዊ የተለየ ጥቅም እንደሚያገኝና ምንም ዓይነት ጭቆና የማይደርስበት የተለየ ህዝብ አድርገው ስለሚያስቡ ወደ ትግራይ መጥተው በአካል ለመታዘብና ለመዘገብ ተነሳሽነቱ ያንሳቸዋል። ምክንያቱም አንዴ “የትግራይ ህዝብ የስርዓቱ ተጠቃሚ ነው” ብለው ፈርጀዋልና።
መፍትሔው መሆን ያለበት “የትግራይ ህዝብ የስርዓቱ ደጋፊና ተጠቃሚ ነው” ከሚል መሰረት የሌለው መላምት ወጥተን፣ የትግራይን ህዝብ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ አይተን ችግሩን መካፈልና መዘገብ እንዲሁም ከህወሓት ለያይተን ማየት አለብን። የትግራይ ሰዎችም ፍርሓታችንን ሰብረን እውነታውን ማጋለጥ መቻል ይኖርብናል። 
ሎሚ፡- የትግራይ ሕዝብ በሕወሐት ተጠቃሚ እንዳልሆነ ብዙ ጊዜ ትገልጻለሕ፤ ኤፈርት እንደ መሰቦ ሲሚንቶ፣ አልመዳ ጨርቃጨርቅ፣ መስፍን ኢንዱስትሪያል….. ወዘተ ትልልቅ ኩባንያዎች መክፈቱን (ህዝቡ ስራ በማግኘት ጭምር ተጠቃሚ ስለሚሆን) የሚገልፁ ወገኖች ብአዴን ከዳሽን ቢራ ውጪ ትልቅ ኩባንያ አለመክፈቱን ለንጽጽር በማቅረብ ያንተን አቋም ይተቻሉ፤ ለዚሕ ያንተ ምላሽ ምንድነው? 
አብርሃ፡- ህወሓት የኤፈርት ኩባንያዎች ትግራይ ውስጥ ስለተከለ የትግራይ ህዝብ በተለየ ሁኔታ ተጠቃሚ ነው ማለት አንችልም። አንደኛ የትግራይ ህዝብ እንደማንኛውም ሌላ ህዝብ በአካባቢው ፋብሪካዎች ተተክለው የስራ ዕድል የማግኘት መብት አለው። ህወሓት ባይኖር ኖሮ በትግራይ ፋብሪካዎች አይኖሩም ነበር ማለት አንችልም። እንዲያውም ህወሓት ባይኖር እነዚህና ሌሎች ተጨማሪ ኩባንያዎች በማቋቋም ሰፊ የስራ ዕድል መፍጠር እንችል ነበር። 
ሁለተኛ “በህወሓት ተግባር የትግራይ ህዝብ ተጠቃሚ አይደለም” ስንል የኤፈርት ኩባንያዎች ትግራይ ውስጥ የሉም እያልን አይደለም። “እነዚህ ኩባንያዎች ቢያንስ ለትግራይ ህዝብ የስራ ዕድል ይፈጥራሉ…” የሚል ሓሳብ አንስተሃል። ጥሩ ነው። ግን “የስራ ዕድል” ምን ማለት ነው? የኤፈርት ሰራተኞች ግልፅ የክፍት ስራ ማስታወቂያ ወጥቶ፣ ተወዳድረው የሚገቡ ይመስልሃል? ማንም የትግራይ ሰው በኤፈርት ተቀጥሮ የመስራት መብት ያለውስ ይመስልሃል? ኤፈርት ለትግራይ ህዝብ የስራ ዕድል ከፍቷል ማለት የምንችለው ማንም የትግራይ ሰው በሙያው፣ ፍትሓዊ በሆነ መንገድ ተወዳድሮ ገብቶ መስራት ሲችል ብቻ ነው። ይሄ ነገር በኤፈርት መንደር የለም። 
እንዲያውም ኤፈርት ለትግራይ ህዝብ የስራ ዕድል ከመክፈት ይልቅ የስራ ዕንቅፋት የፈጠረ ይመስለኛል። ኤፈርት ባለሃብቶች በትግራይ ክልል ኢንቨስት እንዳያደርጉ ዕንቅፋት ሆኖባቸዋል። ምክንያቱም የኤፈርት ድርጅቶች በሙስና የተጨማለቁ ስለሆኑ ትርፋማ አይደሉም፤ ራሳቸውን ችለው ተወዳድረው ትርፍ ማግኘት አይችሉም። ሌሎች የግል ባለሃብቶች በትግራይ በተመሳሳይ ዘርፍ ከተሰማሩ ደግሞ የኤፈርት ድርጅቶች በወድድር ከገበያ ይወጣሉ፣ ይከስራሉ። ኤፈርት ከከሰረ ደግሞ የህወሓት ባለስልጣናት የገቢ ምንጫቸው ይደርቃል። 
ለዚህ ሲባል የህወሓት ባለስልጣናት ባለሃብቶች ትግራይ ውስጥ ኢንቨስት እንዳያደርጉ የተለያዩ አስተዳደራዊ መሰናክሎች በመፍጠር ከትግራይ እንዲወጡ አስገድደዋል። በትግራይ የግል ኢንቨስትመንት አይበረታታም። በዚህ መንገድ የትግራይ ህዝብ የስራ ዕድል ያጣል። ስለዚህ ኤፈርት ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል ባይ ነኝ። 
ህወሓትና ብአዴንን ለማነፃፀር ሞክረሃል። ለኔ ሁለቱም ያው ናቸው። በአንድ ስርዓት ስር ናቸው። አሰራራቸው ተመሳሳይ ነው። ህወሓት ኤፈርት አለው፤ ብአዴን ‘ጥረት’ አለው። ህወሓት ጉና ንግድ ድርጅት አለው፤ ብአዴን አምባሰል ንግድ ድርጅት አለው። ህወሓት ትራንስ ኢትዮጵያ አለው፣ ብአዴን ጥቁር አባይ ትራንስፖርት አለው። ህወሓት ህይወት እርሻ ሜካናይዜሽን አለው፣ ብአዴን ዘለቀ እርሻ ሜካናይዜሽን አለው። ህወሓት በወጋገን ባንክ ሼር አለው፣ ብአዴን በአባይ ባንክ ሼር አለው። እናም በጣም ይመሳሰላሉ። የማን ይበዛል፣ የማንስ ያንሳል አይደለም። ማጭበርበር በዛም አነሰም ማጭበርበር ነው።
ሎሚ፡- አቶ ገብቱ አስራትና ወ/ሮ አረጋሽ አዳነ የሕወሐት ተቃዋሚ መስለው ከቆዩ በኋላ ዕውነተኛው ተቃውሞ ሲገለጥ፣ (በምርጫ 97 ሰሞን) በሚያዘጋጁት “ህዝባዊ” የተሰኘ ጋዜጣ ላይ ኢህአዴግን ሳይሆን ቅንጅትን ነበር ክፉኛ የሚነቅፉት፤ ከአየር ኃይል አዛዥነት የተባረሩት ጄነራል አበበ (ጆቤ)ም በአዲስ አበባ የትግራይ ተወላጆችን (በምርጫ 97) ሰሞን ያስተባብሩ እንደነበር ተገልጿል፡፡ ይህም የቀድሞ ሕወሐቶች ሌላ ወገን ወደ ሥልጣን ከሚመጣ ምንም ቢሆን ሕወሐት ይሻለናል የሚሉ ያስመስላቸዋል የሚል አስተያየት ሲያየሰጥ ነበር፤ አንተ ይህን ጉዳይ እንዴት ተከታተልከው? 
አብርሃ፡- በጥያቄሕ “ተቃዋሚ መስለው ከቆዩ” እንዲሁም “እውነተኛው ተቃውሞ ሲገለጥ” የሚሉ አባባሎች ተጠቅመሃል። በመሰረቱ “ተቃዋሚ መምሰል” ምን ማለት ነው? “እውነተኛ ተቃውሞስ” ምንድነው?
ኢህአዴግን መቃወም ማለት’ኮ ማንኛውም ኢህአዴግን ለሚቃወም ሌላ ግለሰብ ወይ ድርጅት ድጋፍ መስጠት ማለት አይደለም። አቶ ገብሩና ወ/ሮ አረጋሽ ኢህአዴግን ይቃወም የነበረውን ‘ቅንጅት’ የተሰኘ የፖለቲካ ድርጅት ስለነቀፉ ኢህአዴግን የሚቃወሙ ግለሰቦች አይደሉም ማለት አይቻልም። ምክንያቱም ኢህአዴግን እየተቃወሙ ሌሎች ፀረ-ኢህአዴግ የሆኑ ድርጅቶችን ሊነቅፉ ወይ ሊደግፉ ይችላሉ። ኢህአዴግን የምትቃወም ከሆነ ኢህአዴግን የሚቃወሙ ኃይሎችን አትንቀፍ የሚል ሎጂክ የለም። 
አቶ ገብሩና ወ/ሮ አረጋሽ ቅንጅትን ተቃውሞው ከሆነ የተቃወሙበት ምክንያት ምንድነው? ብለን መጠየቅ ሊኖርብን ነው። ቅንጅትን የነቀፉበት ምክንያት ቅንጅት ኢህአዴግን ስለተቃወመ ከሆነ እነ ገብሩን መውቀስ እንችል ይሆናል። ግን ቅንጅትን የነቀፉበት ሌላ የራሳቸው አሳማኝ ምክንያት ቢኖራቸውስ? ስለዚህ ምክንያታቸውን ሰምተን፣ መርምረን ነው አቋማቸውን መገምገም የምንችለው። ስንደግፍ ወይ ስንቃወም በምክንያት መሆን አለበት። ትክክለኛ ተቃዋሚ ወይም ደጋፊ የሚያሰኝ መስፈርት ምክንያታዊነት ነው። 
ገብሩና አረጋሽ ከህወሓት የወጡት በግለሰባዊ ጥላቻ አይደለም፤ የትግራይን ህዝብ ጠልተውም አይደለም። በመርህ ልዩነት ነው የተለያዩት። ስለዚህ ገብሩና አረጋሽ የህወሓት ተቃዋሚዎች እንጂ የህወሓት ጠላቶች አይደሉም። ተቃውሞ ጠላትነት አይደለም፤ የአቋም ልዩነት መያዝ ነው። ስለዚህ ድምዳሜ ከመስጠቴ በፊት ቅንጅትን የነቀፉበት ምክንያት መስማት እፈልጋለሁ። 
“አንተ ይህን ጉዳይ እንዴት ተመለከትከው?” ብለህ ላነሳኸው ጥያቄ እኔ ለህዝብ ነው የምቆመው። ለህዝብ ነፃነት ሲባል አማራጭ ፓርቲዎች እንዲኖሩ እፈልጋለሁ፤ ያለ አማራጭ ፓርቲዎች መኖር ዴሞክራሲ ስለማይኖር። ያለ ዴሞክራሲም የህዝብ ነፃነት እውን ስለማይሆን። ስለዚህ ተቃዋሚዎችን እደግፋለሁ። የምደግፍበት ምክንያት ግን ኢህአዴግን እንደምቃወም ለማሳየት ሳይሆን የነሱ መኖር ለህዝብ ስለሚጠቅም ነው። የህዝብና የፓርቲዎች ፍላጎት ከተጋጨ ግን ህዝብን ነው የማስቀድመው። ህዝብን ማስቀደም ካለብኝ የትግራይ ህዝብም ህዝብ መሆኑ መርሳት የለብንም። በትግራይ ህዝብ ላይ የተቃጣ አደጋ ካለ ከትግራይ ህዝብ ጋር መቆሜ አይቀርም። በአማራ፣ ኦሮሞ… እንዲሁም በማንም ኢትዮጵያዊ ዜጋ ላይ ያነጣጠረ አደጋ ካለ ከህዝቡ ጋር እቆማለሁ። በ1997 ዓም ሀገራዊ ምርጫ አንዳንድ የቅንጅት አመራር አባላት ኢህአዴግ በሰላማዊ መንገድ ስልጣን እንደማያስረክባቸው ሲረዱ፣ የትግራይ ህዝብና ህወሓትን መለያየት አቅቷቸው እንደነበር የሚታወስ ነው። ግን ማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ፀረ ህዝብ አቋም ከያዘ ልንተቸው ይገባል። ምክንያቱም የመጨረሻ ግባችን የህዝቦች ደህንነት መጠበቅ ነው።
ሎሚ፡- አሁን የአረና አባል ሆነሃል፤ በፓርቲው ውስጥ ያለህ ተሳትፎ ምን ይመስላል? የአረና ጥንካሬና ድክመትስ ምንድነው? በትግራይ የምታካሂዱት እንቅስቃሴ ምን ደረጃ ላይ ይገኛል? 
አብርሃ፡- ዓረና በሰለማዊ ትግል የሚያምን፣ በኢትዮጵያ ሰለማዊ የስልጣን ሽግግር እንዲኖርና ዴሞክራሲ አብቦ ዜጎች በእኩልነት፣ በነፃነትና በመከባበር የሚኖሩባት ሀገር እውን ለማድረግ የሚንቀሳቀስ የፖለቲካ ድርጅት ነው። ስትራቴጂው በሰላማዊ መንገድ በህዝብ ተመርጦ፣ ከሌሎች ተመሳሳይ የፖለቲካ አቅጣጫ የሚያራምዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በመዋሃድ በኢትዮጵያ ልማትና ነፃነት ማረጋገጥ እስከሆነ ድረስ በእንቅስቃሴው ህዝቡ የፖለቲካ ግንዛቤው የሚያድግበትን ሁኔታ በማመቻቸት ላይ ይገኛል። 
ፓርቲያችን በኢትዮጵያ ፖለቲካ ለውጥ ማምጣት ይፈልጋል። ለውጥ የምናመጣው ስልጣን ስንይዝ ነው። ስልጣን የምንረከበው ከጠመንጃ አፈሙዝ ሳይሆን ከህዝብ ድምፅ ነው። ስልጣን ከህዝብ ለመረከብ ህዝቡ የስልጣን ባለቤት መሆን አለበት። ህዝቡ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን ስልጣን የሚሸከምበት አቅም ሊኖረው ይገባል። አቅም እንዲኖረው ማስተማር አለብን። አቅሙ ካለውና ገዢዎቹን መጠየቅ ከቻለ ህዝቡ የስልጣን ባለቤት ይሆናል። ህዝቡ የስልጣን ባለቤት ከሆነ ለፓርቲዎች የስልጣን ምንጭ ሆነ ማለት ነው። ስልጣን ከህዝብ ተበድረን ለውጥ የምናመጣበት መንገድ ለማመቻቸት ህዝቡን እያስተማርንና እያደራጀን እንገኛለን።
የዓረና ጥንካሬ ብዬ የምለው የህወሓትን ተፅዕኖ ተቋቁሞ፣ የትግራይን ህዝብ የለውጥ ፍላጎትና ተነሳሽነት በአግባቡ ማደራጀትና መምራት መቻሉ ነው። የዓረና ፈተና፡ በትግራይ ውስጥ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማድረግ ከባድ መሆኑ ነው። ምክንያቱም በትግራይ መንቀሳቀስ ለህወሓቶች ከባድ ፈተና ማዘጋጀት ነው። ስለዚህ ህወሓት በዓረና አባላት ላይ ችግር መፍጠሩ ፈተናችን ነው። 
ሎሚ፡- ከሰሞኑ ሕወሐት በመቀሌ ስብሰባ መቀመጡን መረጃ ደርሶናል፤ የሕወሐትን መረጃ ለማግኘት ካለሕ ቅርበት አንፃር በምን ጉዳይ እንደተሰበሰቡና ተሰብሳቢዎቹ ምን ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ብትገልጽልን? 
አብርሃ፡- የተሰበሰቡት እርስ በርሳቸው ተገማግመው ራሳቸውን ለመፈተሽ ነው። ከግምገማው በተጨማሪ “አዳዲስ” የፓርቲና የመንግስት አደረጃጀቶች ስለማዋቀር ይወያያሉ። አሁን ምን ደረጃ ላይ እንደደረሱ የተሟላ መረጃ ባይኖረኝም ስብሰባው “በድል” ከተጠናቀቀ አዳዲስ ሹመቶችና መዋቅሮች እንደሚኖሩ ይጠበቃል።
ሎሚ፡- ሕወሐት በዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል በሚመራው የአዲስ አበባው ቡድንና በአቶ አባይ ወልዱ በሚመራው የመቀሌ ቡድን ሽኩቻ ውስጥ ገብቷል ይባላል፤ ስለዚህ ጉዳይ ያለህ መረጃስ ምን ይመስላል?
አብርሃ፡- የነ አባይ ወልዱ ቡድን የአዲስ አበባዎቹን የትግራይ ክልል መንግስታዊ መዋቅር ተጠቅመው ከህዝብ ለመነጠል ሲችሉ፣ እነ ዶ/ር ደብረፅዮን ደግሞ በሙስና ሰበብ እያሰሩ ከስልጣናቸው እያፈናቀሏቸው ይገኛሉ። ባጠቃላይ “ዴድሎክ” ላይ ናቸው። 
ሎሚ፡- ሕወሐት (በጥቅሉ ኢህአዴግ) በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ግንባታ ሂደት ላይ ያለውን አቋም እንዴት ትገልጸዋለሕ? በዋናነት ለሀገሪቱ ምን ሰርቷል፣ ምንስ አሳጥቷል? 
አብርሃ፡- በጣም ሰፊ ጥያቄ ነው። ኢህአዴግ ‘ዴሞክራሲ ያመጣ መንግስት’ ተብሎ በኢትዮጵያ ህዝብ እንዲወደስ ይፈልጋል። ከዛ በላይ ግን በስልጣን መቆየት ይመርጣል። ዴሞክራሲ ለማምጣት ሲፈልግ ስልጣኑን የሚያጣበት መንገድ ስለሚያመቻች ከዴሞክራሲ ማስፈን በስልጣን መቆየትን ይመርጣል። በዚህ ሁኔታ “ዴሞክራሲያዊ” ለመባል በከፈተው መስኮት የገቡ ዜጎች ዋናውን በር ዘግቶ በማፈን ነፃነታቸውን ነፍጎ፣ ህልውናቸውን አደጋ ላይ ይጥላል። ኢህአዴግ አስፋልት መንገዶችን ሰርቶልናል፤ ነፃነታችንና የባህር በራችንን አሳጥቶናል። 
ሎሚ፡- ስለቀድሞ ቀዳማይት እመቤት አዜብ መስፍን ያለህ መረጃ ምን ይመስላል? እናንተ አካባቢ (በትግራይ) ስለእሳቸው ምን አስተያየት ይሰማል? 
አብርሃ፡- ወ/ሮ አዜብ መስፍን የባለቤቷን “ስም” ተጠቅማ “በመለስ ራዕይ” ስም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ትልቅ እጅና ሚና እንዲኖራት ትፈልግ ነበር። ግን የሚሳካላት አይመስልም። ወ/ሮ አዜብ በትግራይ ህዝብ ዘንድ አጀንዳ አይደለችም። 
ሎሚ፡- ሕወሐት በአሁኑ ወቅት ከትግራይ ህዝብ ጋር ያለው ግንኙነት ምን ይመስላል? 
አብርሃ፡- በአሁኑ ሰዓት የትግራይ ህዝብ በህወሓት እምነት የለውም። ይህ ማለት ግን የትግራይ ህዝብ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ከህወሓት በላይ ያምናል ማለት አይደለም። በትግራይ ህዝብ እምነት ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለትግራይ ህዝብ ጥሩ አመለካከት የላቸውም። ምክንያቱም የትግራይ ህዝብ በህወሓት ዘመን የተለየ ጥቅም ያገኛል ብለው ስለሚያስቡና ህዝቡና ፓርቲን አንድ አድርገው ስለሚቆጥሩ። በዚህ ምክንያት የትግራይ ህዝብ ህወሓትን ቢጠላም በሌሎች ፓርቲዎች ላይ ጥርጣሬ አለው።
ሎሚ፡- ገዢው ፓርቲ እስካሁን የተጓዘበትን መንገድ እንዴት ቃኘኸው? ወደፊት በሀገሪቱ የዲሞክራሲያዊ መስመር ግንባታ ለማካሄድ ፈቃደኛ የሚሆን ይመስልሃል? 
አብርሃ፡- ገዢው ፓርቲ እስካሁን የተጓዘበት መንገድ ኮረኮንች ነው፣ አባጣ ጎርባጣ ነው። የዴሞክራሲን መስኮት ገርበብ ያደርጋል፤ እንደገና ጥርቅም አድርጎ ይዘጋል። 
ኢህአዴግ የዴሞክራሲ መስመር ግንባታ ለማካሄድ ፈቃደኛ የሚሆንበት ዕድል ሊኖር ይችላል። በፈቃደኝነት የፖለቲካ ስልጣን ለማስረከብ ግን ፍፁም ፈቃደኛ አይሆንም። ስልጣን ለህዝብ ለማስረከብ ፈቃደኛ ያልሆነ መንግስት ደግሞ የዴሞክራሲ መስመር መገንባት አይችልም። ምክንያቱም የዴሞክራሲ ፅንሰ ሐሳብ የፖለቲካ ስልጣን በፈቃደኝነት ለህዝብ ማስረከብ መቻል ነው። 
መደረግ ያለበት ነገር ቢኖር የተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንድነት ቆመው፣ ጠንካራ ድርጅት መስርተው፣ በጥላቻና ቂምበቀል ሳይሆን በሓሳብ ሚዛናዊነትና ምክንያታዊነት የኢትዮጵያን ህዝብ ለሰላማዊ ትግል በአግባቡ ቀስቅሰው፣ ኢህአዴግን የህዝብ ድጋፉን በማሳጣት፣ ገዢው ፓርቲ ስልጣኑን ለህዝብ እንዲያስረክብ ሊያስገድዱት ይችላሉ።
ኢህአዴግ የዴሞክራሲ መንገድን በመዝጋት የዜጎችን ነፃነት በሃይል እያፈነ፣ ተቃዋሚዎችን እንዲዳከሙ ካደረገና ከተሳካለት ግን ገዢውን ፓርቲ በሃይል ከስልጣን የሚያባርሩትን ታጣቂ ሃይሎች እየጋበዘ ነው ማለት ነው። ይህ ከሆነ ገዢው ፓርቲ ስልጣን ለህዝብ ከማስረከብ ይልቅ ለሌሎች ታጣቂዎች ለመስጠት ወስኗል ማለት ነው። እንዲህ ከሆነ በሃይል እስኪባረር ድረስ በስልጣኑ ይቆያል ማለት ነው። 
ሎሚ፡- የተቃዋሚ ፓርቲዎችን አካሄድ እንዴት ትገልጸዋለህ? እነሱስ ለዲሞክራሲያዊ ሂደት ግንባታ እያበረክቱት ያለው ጠንካራ/ደካማ ጎን ምንድነው? ከህዝቡስ ምን ይጠበቃል? 
አብርሃ፡- የተቃዋሚ ፓርቲዎች የተናጠል አካሄድ የሚያስደስት ባይሆንም እንደ አማራጭ የፖለቲካ ፓርቲ ሆነው ለህዝብ መቅረባቸው በራሱ ጥሩ ነገር ነው። ፓርቲዎቹ የእርስ በርስ አለመተማመን፣ መጠላለፍና በአንድነት ያለመቆም ችግራቸውን ለህዝብ ብለው ማስወገድ ይኖርባቸዋል። 
ተቃዋሚዎች ስለ ኢትዮጵያ አንድነት ሲያስቡ መጀመሪያ ስለ ፓርቲዎች አንድነትና ውህደት ማሰብ አለባቸው። በፓርቲዎቹ መካከል አንድነት ሳይኖር ለኢትዮጵያ ህዝብ አንድነትና መግባባት ያመጣሉ ብለን ለማመን እንቸገራለን። ስለዚህ ተቃዋሚዎች አንድነትና ጥንካሬ ፈጥረው ህዝብ በነሱ ብቃት እንዲተማመንና ድጋፍ እንዲሰጣቸው ከሰውኛ ፖለቲካ ወጥተው፣ መርህን መሰረት ያደረገ የፖለቲካ ጨዋታ መጀመር አለባቸው።
ከህዝቡ የሚጠበቀው ስለ ነፃነቱ መጠየቅ አለበት። በፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች በመሳተፍ የስልጣን ባለቤት የሚሆንበት መንገድን ማመቻቸት አለበት። እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱን ሃላፊነት በራሱ ትከሻ መሸከም አለበት። የፖለቲካ ስልጣን ወደ ህዝብ እንዲመለስ በገዢው ፓርቲ ላይ በሰላማዊ መንገድ ተፅዕኖ መፍጠር አለበት። የፖለቲካ ስልጣን የህዝብ መሆን ስላለበት፣ ህዝብ የስልጣን ባለቤት የመሆን መብቱን በጋራ መጠየቅ ይኖርበታል። ካልሆነ ግን ሸክሙ ለህዝቡ ይደርሳል። 
አመሰግናለሁ፡፡
It is so!!!

https://freedom4ethiopian.wordpress.com/2013/09/16/76-4/

No comments:

Post a Comment