Saturday, September 28, 2013

የማለዳ ወግ … በሳውዲ አረቢያ የኢትዮጵያውያን ክራሞት – ከነብዩ ሲራክ (ጋዜጠኛ)


saudi arabia የማለዳ ወግ … በሳውዲ አረቢያ የኢትዮጵያውያን ክራሞት
ከተፈናቃዮች አበሳ እሰከ አሳሳቢው የስደት ፍሬ ልጆቻችን ትምህርት አሰጣጥ ህጸጽ !
አዲሱ አመት ባባተ ማግስት በሳውዲ አረቢያ የከተምን የብዙዎችን ቀልብ የሳበው መረጃ ትኩረት በኮንትራት ስራተኞች መፈናቀል ዙሪያ በጅዳና ሪያድ የሚገኙ ተፈናቃዮች አሳዝኝ ይዞታ ጉዳይ በቀዳሚነት ይጠቀሳል። በጅዳም በሪያድም ግፉአን የሚታደጋቸው ጠፍቶ ኑሯቸው ከፍቷል ፣ ይህንን የከፋ የዜጎች በደል አንስቶ መናገርና መረጃ መስጠት ደግሞ ነውር ሆኗል ፣ በሃላፊዎቻችን ዘንድ በተፈናቃዮች ዙሪያ መረጃ ማቅረብ እንደ ወንጀለኛ ስለሚያስቆጥር ብዙሃኑ ነዋሪ ቀርቦ ተፈናቃዮችን እንዳይረዳና በመፍትሔው ዙሪያ እንዳይመክር ስልታዊ ጫናው በርትቶበታል። ነዋሪው እንዳይቅርብ ፣ እንዲፈራና አንዲሸሽ እየተደረገም ነው። ያን ሰሞን እኔን ጨምሮ በዜጎች መብት ጥበቃና ግልጋሎት አሰጣጥ ላይ የሰላ ሂስ የምናቀርብ ዜጎች በቆንስሉ ስብሰባ እንዳንሳተፍ ተደርጎ ነበር ። ዛሬም ያው እገዳ ቀጥሎ የመንግስታችን ሃላፊዎች ለመብት ጥበቃው እንዲተጉ በአደባባይ የሚናገሩ ወንድሞች በተለያዩ ስብሰባዎች እንዳይገቡ የጅዳው ቆንስል አቶ ዘነበ ከበደ አዘው እየተተገበረ ይገኛል። ያው የጅዳው ቆንስል እገዳ ቀጥሎ ትናንት አርብ ምሽት በጅዳ ቆንስል በተደረገው የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትት የአቶ መለስ ዜናዊ ” ፋውንዴሽን “።መዋጮ ስብሰባ ላይ ለመሳተፍ ወደ ጅዳ ቆንስል የስብሰባ አዳራሽ ጎራ ያሉ ተፈናቃዮችን በመደገፍ የሚታወቁ ወጣቶች በስብሰባው እንዳይሳተፉ መደረጋቸውን ሰምቻለሁ ! ያሳዝናል …
ይህ ግራ እያጋባን ባለበት በዚህ ሰአት ደግሞ ሌላ ሊሰሙት የሚያም መረጃ ከወደ ሪያድ ተሰራጭቷል ። የኢንባሲው ድጋፍ የተነገፋቸው ተፈናቃይ የኮንትራት ሰራተኞች በውስጥ ደወዌ ተጠቅተው በህክምና እጦት እየሞቱ ነው። ኑሯቸውን በሪያድ ያደረጉትም ቢሆን ክራሞታቸው ድስ አይልም። ኢትዮጵያውያን የሪያድ ነዋሪዎች እና የሪያድ ኢንባሲ በትምህርት ቤቱ ዙሪያ ፍጥጫ ገጥመው መሰንበታቸው እውነት ነው ። ብርቱዎች የሪያድ ወላጅ ኮሚቴ አባላት ” በልጆቻችን ለመጣ ወደ ኋላ አንልም !” በማለት ከኢንባሲው ጋር እየዶለቱ የመማር ማስተማሩን ሂደት የሚያደናቅፉ ያሏቸውን በጽናት ተቃውመዋል። ኮሚቴዎች ከማስፈራሪያ ጀምሮ የህዝብ አዳራሽ እስከ መከልክል ቢደርሱም የሪያድ ኢንባሲን ፍትሃዊ ያልሆነ የሚሉትን አሰራር በመቃወም በአስገራሚ ጽናት የመሞገታቸውን ጭብጥ ያለው መረጃ ከፊስ ቡክ ወዳጀ ከ Ethiopia Hagere ለመረዳት ችያለሁ ። ለጊዜውም ቢሆን በሪያድ ስላለው ለሪያዶች ትቸ ለጊዜው ትኩረቴን በጅዳው የኢትዮጵያውያን አለም አቀፍ ትምህርት ቤት እና በትምህርት አሰጣጡ ዙሪያ እየሆነ ስላላው ህጸጽ እና ትኩረት ሳቢ ጉዳይ ላቅና …
የጅዳ የኢትዮጵያውያን አለም አቀፍ ትምህርት ቤት አዲሱን የ2006 አመት ትምህርት ካስጀመረ ወር ቢደፍንም ልጆቻችን በቂ ትምህርት እየቀሰሙ አይደለም ! ዛሬም እንዳምናና ካች አምናው የትምህርት ጥራት ሊያዘባራን መንገዱ ተጀመሯል። ከአመት አመት የትምህርት ጥራቱ እያደረ መዝቀጥ ሲነሳ ነዋሪው ስብሰባ ይጠራና በቀጣይ ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ይመክራል…
*የመምህራን እጥረት
* የተሟሉ የትምህርት ቁሳቁሶች በተፈለገው ደረጃ አለመሟላት
(የመጽሃፍት ፣ የኮምፒውተር እና የላብራቶሪ እቃዎች አለመሟላት ይጠቀሳል)
* የመምህራን በስራ ገበታቸውን አክብረው አለመገኘት ፣
* የመምህራን ትምህርት ቤቱን እየለቀቁ መሄድ
* በትምህርት አሰጣጡ የመምህራኑ ብቃት ማነስ ቢያንስ ላለፉት ስምንት አመታት በዋናነት በሚጠሩት ስብሰባዎች የሚጠቀስ እየተነሳ የሚጣል ዋንኛ ችግር ነው ።
የጅዳ ወላጆች ነዋሪ በተጠቀሱት ችግሮች ዙሪያ ያለውን መሰረታዊ ቅያሞት አቤቱታውን ሲያቀርብ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር እና አስተዳደር አንድም ጊዜ በወላጅ የሚቀርበው ክስና አቤቱታ ሃሰት ነው ብለው አያውቁም ! ዳሩ ገና አሁንም ቢያንስ ላለፉት ስምንት አመታት ሃላፊዎች ለሚያምኑት ለማይክዱት ስህተት መፍትሄ ሲያመጡ አልተስተዋለም ! ከአመት አመት በሚጠራ ስብሰባ ላይ የትምህርት ቤቱ ሃላፊዎች የማይካደው ስህተት የማይታረምበት እንቆቅልሽ ማቆሚያ መቸ እንደሆነ ለማናችንም ግልጽ አይደለም። በላባችን ያመጣነውን ገንዘብ ከፍለን የምናስተምር ተገልጋይ ወላጆች አቤቱታ የከረመ መሰረታዊ የትምህርት ቤታችን ችግር መፍትሄ ፈላጊ አላገኘምና ዛሬም የምንነጋገረው ያነኑ የሚታወቅ ችግር ነው ።
ትምህርት ቤቱ በባለቤትነት የሚያስተዳድረው ኮሚኒቲ እያደር መጫጫት ለመፍትሄ ፍለጋው መኮላሸት ብቻ ሳይሆን ትምህርት ቤቱ በተፈለገው ፍጥነት ጥሩ ዜጎች ማፍራቱን እንዳይገፋበት ጋሬጣ ሆኖታል። የጅዳ አለም አቀፍ ትምህርት ቤት ከሁለት ሽህ በላይ ተማሪዎችን ያስተናግዳል። ይህ ትምህርት ቤት የብዙዎች ተስፋ ሆኖ የተስፋ ብርሃንን ወጋገን ያደረገልን አንጋፋ ትምህርት ቤት ለመሆን የበቃበት መንገድም ቀላል አይደለም። እንዲህ ብርቱ ፈተናዎችን እያለፈ ዛሬ ላይ ቢደርስም ማደግ ባለበት ፍጥነትና ደረጃ አድጓል ለማለት አይቻልም። ትምህርት ቤቱን በባለቤትነት የሚያስተዳድረው የጅዳና አካባቢዋ ኮሚኒቲ መስሪያ ቤት በተለያዩ ተጽዕኖዎች ስር ወድቋልና አለ አይባልም። ኮሚኒቲው አለ እየተባለ እዚህ ቢደርስም ትምህርት ቤቱ በማህበሩ ተጽዕኖ ስር መውደቁን ተከትሎ እያደር የትምህርት ቤቱ ችግሮች መቋጫ እንዳይገኝላቸው ምክንያት ሆኗል ማለት ይቻላል።
የጅዳ ኮሚኒቲ በትምህርት ቤቱ ከአመት እስከ አመት የሚነሱትን አንኳር አንኳር ችግሮች መፍታቱ ይቅርና በውስጥ አስተዳደር ክፍተት ለሚናጠው ትምህርት ቤት መፍትሄ መስጥት ያለቻለ የስም ብቻ ባለቤት አድርጎታል። ከሁሉ አስቀድሞ በመንግስት ለሚደራጁት የልማት ማህበራት ቅድሚያ እየተሰጠ ኮሚኒቲው ሽባ እንዲሆን መደረጉን መካድ አይቻለም ። ዛሬ ዛሬ ከመንግስት ደጋፊነት ቅርበት ካላቸው ወገኖች የሚሰጠን ገደምዳሜ መረጃ ” የትምህርት ቤቱ ባለቤት ኮሚኒቲውን ለማጠናከር ሌላ አደረጃጀት ያስፈልገዋል !”በሚል የዱባይ ኮሚኒቲ ተሞክሮ ትግበራ ውስጥ ውስጡንም ቢሆንም ጥናት ላይ መሆኑን ያመለክታል። “ኮሚኒቲው አስተዳዳሪ ከሃገር ቤት ሊመጣለትም ነው !” መባሉን እየሰማን ነው! ያም ሆነ ይህ ማህበረሰቡ በኮሚኒቲው ያጣውን እምነት መመለስ እሰኪቻል የትምህርት ቤቱን ችግር ለመፍታት ከኮሚኒቲው መስሪያ ቤት በኩል የሚጠበቀው መፍትሄ ተስፋ የሚጣልበት አለመሆኑን ብዙዎች ይሰማሙበታል።
በዚህም ሆነ በዚያ የታዳጊዎች ልጆቻችን ጉዳይ ያገባኛል የሚል ጠፍቷል። ኮሚኒቲው ካለ አይቆጠርም እንኳን ቢባል በትምህርት አሰጣጡ ሂደት ችግር መኖሩን መርምሮ መፍትሔ ማፈላለግ ያለበት የወላጅ ኮሚቴ የት እንደገባ አናውቅም ! ይህን የምለው የትምህርት ቤቱ ጉዳይ የነዋሪው ሰፊ መወያያ እየሆነ መጥቶ እያለ ብዙሃን የመረጣቸው የወላጅ ኮሚቴዎች እንዲወገዱ ተደርገው በመንግስት ድጋፍ የወላጅና መምህራን ህብረት ኮሚቴ ካች አምና የተተኩት ተመራጮች “የዝሆን ጀሮ ይስጠኝ ” በሚል መንፈስ ዝም ፣ ጭጭ ማለታቸውን መታዘቤ ነው ። ትምህርት ቤቱ ከቅጥር ፣ ምዝገባና አሁን ወደ ትምህርት አሰጣጡ ቅሬታዎች ሲቀርቡበት የወላጅ እና መምህራን ህብረት ኮሚቴው የት ነው ያለው? በተለይ የትምህርት ጥራቱን ሊያጎድሉ በሚችል ሁኔታ አብዛኛው ተማሪዎች የተሟላ ትምህርት ሳይሰጣቸውና ባዶ ክፍል እየዋሉ ለመመለሳቸው ኮሚቴ እኛን ሆኖ መናገር እና መሞገት አልቻለም ። ለምን ? ችግሮችን ለመቅረፍ ሃላፊነት ያለበት የወላጅ እና መምህራን ህብረት ኮሚቴ ሃላፊነቱን መወጣት ካልቻለ በስሙ ብቻ አለ መባሉ ፋይዳ የለውም!
የትምህርት ግብይቱ በያዝነው አዲስ አመት ልክ የዛሬ ወር ሲጀመር ክፍያ ተጨምሯል ተባለ፣ ወላጅ አይኑን ሳያሽ ጭማሪ ክፍያውን ተቀበለ ፣ ይህ በሆነ ማግስት አስፈላጊውን መስፈርት አሟልቶ የሚልካቸው ልጆቹ ግን በቂ ትምህርት እያገኙ አይደለም ! መምህራን የሉም እና ሌላም ሌላ ምክንያቶች ዛሬም ሊቀርቡ ይችሉ ይሆናል ። ይህንምም ምክንያት ከመቀበል ሌላ አማራጭ የለምና ምክንያቱ ተቀነባብሮ እስኪነገረን ” ሳይደርቅ በእርጥቡ! ” እንደሚባለው ያሉት መምህራን በሃላፊነት እና በአግባቡ ትምህርት እየሰጡ ለመሆኑ ትምህርት ቤቱ ቁጥጥር ያደርግ ዘንድ እንማጸናለን! በቁጥጥር ማነስ ፣ በእንዝህላልነት እና የመሳሰሉት ሃላፊነትን ካለመረዳት የሚስተዋሉ ችግሮች እየጎዱን ነውና ጊዜ ሳንሰጥ መፍትሄ ሊፈልግላቸው ይገባል ! በአሳር በመከራ በአረብ ሃገር ስደት የምናሳድጋቸው የስደት ፍሬ ልጆቻችን አብዛኛው የትምህርት ሰአት እየባከኑ ነውና እባካችሁ ተማለዱን !
ቸር ያሰማን !
ነቢዩ ሲራክ

zehabesha

No comments:

Post a Comment