Wednesday, November 27, 2013

የሞተው ሀገር ነው (አንዱዓለም በቀለ)

የሞተው ሀገር ነው (አንዱዓለም በቀለ)


አንዱዓለም በቀለ 
ምነው ህልሜ ከፋ ... መተኛት አቃተኝ፣
እሚታየው ሁሉ ... ድንግርግር አለብኝ፣
እሚሰማው ሁሉ ... ተአምር ሆነብኝ፣
እውን ነው? ቅዠት ነው? ... አልጨበጥ አለኝ፣
ኡ ኡ ያገር ያለህ ... ልጩህ ቢወጣልኝ፤
አትጩህ አትበሉኝ ... እጮሀለው በጣም፣

አታልቅስ አትበሉኝ ... አለቅሳለሁ በጣም፣
ከዚህ የበለጠ ... አሥር ሞት አይመጣም፣
ከዚህስ የከፋ ... መዋረድ አይመጣም፤
እጮሃለሁ እንጂ ... እላለሁኝ ዋይ ዋይ፣
ላሥር ስትደፈር ... እህት ሥትሰቃይ፣
ወገኔ ሲታረድ ... በጠራራ ፀሀይ፣
ደራሽ ወገን ጠፍቶ ... ዘራፍ የሚል ከልካይ፣
እንዴት አያስጮህም ... አያሰኝም ዋይ ዋይ?!
ከየትኛው ዘመን ... የትኛው ለይ ደረስን!
ከየተኛው ውርደት ... የትኛው ተሻለን?
ሁሉን የሚሸከም ... ምን ትከሻ ሰጠን!
የምን ልክፍት ነው ... እንዲህ ያደረገን?
እህት ስትደፈር ... እንደ ፊልም እያየን፣
እንደ በግ ሲቀላ ... ወገንን እያየን፣
ሶፋ ላይ ተቀምጠን ... ከንፈር ብቻ መጠን፣
ኦ አምላኬ ባክህ ... ከዚህስ ሰውረን፣
በሩቁ ያዝልን ... ብለን እንዳላየን፣
ወደ አልጋ ስንሮጥ ... እንቅልፍ የሚወስደን፣
አቤት ያንተ ያለህ ... እንደምን ቢያስችለን!
ፊልም እኮ አደለም ... ባይናችን ያየነው፣
ተውኔት አይደለም ... ደራሲ የጻፈው፣
እንደ ሬት ቢመርም ... የምንቀበለው፣
የሁላችን ዕዳ ... ሸሽተን የማንሸሸው፣
በገሃድ የታየ ... መራር እውነታ ነው።
ክብሩን ግንባሩ ላይ ... አሥሮ የወደቀው፣
አረብ በረሃ ላይ ... ውሻ የተባለው፣
እውነት ... አንድ ሰው ነው??
እውነት ሀገር ያጣ ... ውዳቂ ውሻ ነው?
ካልሳትነው በስተቀር ...
የዛች ኩሩ ሀገር ... መጠሪያ ዜጋ ነው፣
እንደኔ እንደናንተ ...
ህይወት የሚያባርር ... ንፁህ ኢትዮጵያዊ ነው፤
መቼ ይህ ብቻ ነው ...!
የሦስት ሺህ ዘመን ... አኩሪ ታሪክ ያለው፣
የጥቁሮች ኩራት ... መመኪያ የሆነው፣
ያልበገሬነት ... ማህተም የሆነው፣
ከአፍሪቃ አልፎ ... በዓለም ከፍ ያለው፣
ዛሬ ሁላችንም ... አርገን የምንኮራው፣
የማንነታችን ... መለያ የሆነው፣
ዛሬ አረብ ምድር ... እንዲህ የተናቀው፣
ሰንደቅ ዓላማችን ... ክብራችን እኮ ነው፤
ውሻ የተባለው ... ኢትዮጵያዊነት ነው፤
እንዲህ የረከሠው ... ማንነታችን ነው፤
አንድ ሰው አደለም ... ወድቆ የምናየው፣
ደጋግሞ ደጋግሞ ... የሞተው ሀገር ነው፤
ሀገር ነው የሞተው ... አብረን ነው የሞትነው።
እና ለምን አልጮህ ... ተወው አትበሉኝ፣
ይልቅ የኔን ጩኸት ... አንድ ላይ ካልጮህን፣
እንዲህ ስንዋረድ ... በጋራ ካልቆምን፣
ከኛ በላይ ለኛ ... ታዲያ ማን ይምጣልን?
የሰው ልጅ መገኛ ... መሠረት የሆነች፣
ዘርፈ ብዙ ታሪክ ... ገድል የፈፀመች፣
ዛሬ ለሚገሉን ... ገነት የነበረች፣
ዛሬ ውሻ ላሉን ... ምፅዋት የሰጠች፣
እስላም ክርስቲያኑን ... በፍቅር ያኖረች፣
የሐበሻ ምድር ... ቅዱስ የተባለች፣
እቺ ኩሩ ሀገር ... ምነው እንዲህ ሆነች?!
ከምን ላይ ተነስታ ... እምን ላይ ደረሰች?
ከሁሉም ከሁሉም ... እጅጉን የሚያመው፣
ሳያንስ የተገፋው ... ሳያንስ የተደፋው፣
ለሞተው ወገኔ ... ልጩኽለት ላለው፣
አብሬው ባለሞትም ... ላልቅስለት ላለው፣
የወገንን ጩኸት ... ዳግም እሚያፍነው፣
የሟቾችን እናት ... መልሶ ሚገርፈው፣
መታደጉ ቢቀር ... ለቅሶ የነፈገው፣
ይህ ነው መንግሥታችን ... ከገዳይ ያበረው፤
ይህ ነው መንግሥታችን ... ለሀገር የቆመው፤
እርግጥ ነው ... እውነት ነው፣
እነሱ ምን ያርጉ ... ተመችተናቸው፣
ጫንቃችን ደንድኖ ... ተሸክመናቸው!
እስቲ በቃ እንበል ... በቃችሁ እንዲለን፣
መጠላለፍ ይቅር ... አንድ ላይ ያቁመን፣
ከወሬ ባለፈ ... ተግባር ይፈትሸን፣
እንዲህ በሚጮኹት ... በወገኖቻችን፣
መሬት በወደቀው ... ሰንደቅ ዓላማችን፣
እስቲ እንማማል ... ይያያዝ እጃችን፣
ይብቃ ስደታችን ... ይብቃ ውርደታችን፣
ብሔራዊ ክብር ... ይታደስ ስማችን፣

No comments:

Post a Comment