Friday, November 29, 2013

አራምባና ቆቦ ወይስ ወላፈንዳ (ቦጋለ ዳኜ)



ቦጋለ ዳኜ ከካሊፎርኒያ
ሥጋ ሜዳ፤ ሽሮ ሜዳ፤
እሚቀመስ የለም ጓዳ።

ሳይኖር አውራ፤ ዶሮ ሲካካ፤
እንቁላል ፋብሪካ።

እንቁላል ሾላ፤ ፋብሪካ ጉለሌ፤
እንጀራ አዲሳባ መሶብ መቀሌ።
(ገበያ መርካቶ፤ ሲሚንቶ መቀሌ።)

ስንቅ አቀባይ ባሌ፤ እስረኛ ሰንቀሌ፤
"ዘይገርም ሻሸመኔ፤ ትብስ ኮፈሌ።"

ታዳሚ አገር ፍቅር፤ ብሔራዊ ቲያትር፤
ድራማ ሰቱድዮ፤ ማስታወቂያ ሚኒስቴር።

ባለ ጉዳይ ይፋት፤ የዳኛ ቀጠሮ፤
ጉዳይ ባሕር ዳር ባዲሳባ ዞሮ።

አስለቃሽ ደኅንነት፤ ቀብር ቀራንዮ፤
ሟች ራሱ አልቃሽ፤ ደረት ጥሎ ወዮ።

በጸጥታ ጩኸት፤ በደኅንነት ችግር
አልገናኝ አለ፤ መጠርያና ተግባር።

ይካፈል በልማት፤ ያገባዋል ሕዝብ፤
ልማቱን ለኛ ተው ብር ብቻ ሰብስብ።

ሥልጣን በምርጫ ነው፤ ዐዋጅ ተመዝገቡ፤
የምርጫ ካርዱን ግን፤ ሁሉን ለኔ አግቡ።

ሁሉ በእኩል ይታይ፤ መልካም አስተዳደር፤
ብሔር ብሔረ ሰብ፤ ባዶ መፈክር።

ደኑ አይጨፍጨፍ፤ ትውልድ እንዳይወቅስ፤
እየሰሙ ዝም፤ጆሮ ዳባልበስ።

ወደ ክልልህ ሒድ፤ ውጣ ከመሬቴ፤
ባዕዳን ሕንድ ቻይና፤ ኑ ግቡ በሞቴ።

ለሳውዲ ሲሰጥ የተንጣለለ እርሻ፤
ተጠራርጎይውጣ ከሳውዲ አበሻ።

ቦጋለ ዳኜ ከካሊፎርኒያ

eth iopiazare

No comments:

Post a Comment