Tuesday, November 26, 2013

‹‹መወሰድ ያለበት የሚያስፈልግ ዕርምጃ ካለ እንደርስበታለን

‹‹መወሰድ ያለበት የሚያስፈልግ ዕርምጃ ካለ እንደርስበታለን፤ ተመጣጣኝ ዕርምጃ እንደምንወስድ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ፤››

-‹‹ደላሎችና ኤጀንሲዎች አሁንስ ተሰማችሁ?›› ሲሉ ጠይቀዋል

-ከሳዑዲ መውጣት የሚገባቸው ኢትዮጵያውያን ቁጥር 80 ሺሕ ሊደርስ ይችላል

የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የላቸውም በማለት ሰብዓዊ አያያዝ በጎደለው ሁኔታ በኢትዮጵያውያን ላይ ላደረሰው ሥቃይና እንግልት የኢትዮጵያ መንግሥት ተመጣጣኝ ዕርምጃ እንደሚወስድ፣

ቀዳሚው የመንግሥት ትኩረት ግን ለዜጎች በመድረስ ወደ አገራቸው መመለስ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም አስታወቁ፡፡

ሚኒስትሩ ባለፈው ዓርብ ከቀትር በኋላ ለአገር ውስጥ ጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ሳዑዲ ዓረቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ለመመለስ መንግሥት ሥራውን የጀመረው ከአራት ወራት በፊት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

መንግሥት ባደረገው ጥረት ከ38 ሺሕ በላይ ኢትዮጵያውያን በሳዑዲ ሕጋዊነትን እንዲያገኙ መቻሉን፣ ከዓለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት (IOM) ጋር በመተባበር በሳዑዲ ሕጋዊነትን ያላገኙ ኢትዮጵያውያንን ለመመለስ በተደረገው ሙከራ ለመጠቀም ፈቃደኛ የሆኑት 300 ብቻ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ ባለፈው ሐምሌ ወር ውስጥ በእርሳቸው የተመራ ከፍተኛ የኢትዮጵያ መንግሥት ቡድን ሳዑዲ ዓረቢያ በመገኘት ከሳዑዲ መንግሥት ባለሥልጣናት ጋር በመነጋገር ሕጋዊነት የሌላቸው ዜጎችን የማስወጣቱ ተግባር እንዲራዘም ጥያቄ ማቅረባቸውንና መፈቀዱን የገለጹት ዶ/ር ቴድሮስ፣ መንግሥት ባደረገው ከፍተኛ ጥረት ኢትዮጵያውያኑን ከጊዜ ገደቡ በፊት የመመለሱ ተግባር አለመሳካቱን ገልጸዋል፡፡

አንዳንድ ወገኖች የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት በኢትዮጵያውያን ላይ ለወሰደው ዕርምጃ መንግሥት ተለሳልሷል በማለት መተቸታቸውን እየሰሙ እንደሆነ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ይህ ትችት ተገቢ ያልሆነና ሁኔታውን ያላገናዘበ ነው ብለዋል፡፡

‹‹መንግሥት በአሁኑ ወቅት ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ የሚኘው ዜጎቹን ለመመለስ ነው፤ በሳዑዲ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ድረሱልን እያሉ ሌላ ነገር ማስቀደም ተገቢ አይደለም፤›› ብለዋል፡፡

‹‹መጠየቅ ያለበት የለሰለሰ ወይም የጠነከረ ዕርምጃ አይደለም፤ የሚወሰደው ዕርምጃ በእርጋታ የታሰበበትና ተመጣጣኝ መሆኑ ነው፤›› ሲሉ ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡

‹‹መወሰድ ያለበት የሚያስፈልግ ዕርምጃ ካለ እንደርስበታለን፤ ተመጣጣኝ ዕርምጃ እንደምንወስድ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ፤›› ብለዋል፡፡

በሳዑዲ ዓረቢያ እንደሚኖሩ የሚገመቱ ኢትዮጵያውያን መጠን 40 ሺሕ ይሆናል ተብሎ ከሳዑዲ መንግሥት በተገኘ መረጃ ተገምቶ እንደነበር፣ እውነታው ግን አሁንም ድረስ በእርግጥ አለመታወቁን ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡

ከተገመተው ቁጥር ውስጥ ሕጋዊነት የሌላቸው ኢትዮጵያውያን አሥር ሺሕ ተብሎ መገመቱን፣ ነገር ግን የሳዑዲ መንግሥት የሰጠው ቀነ ገደብ ከተጠናቀቀ በኋላ ቤት ለቤት በማሰስ የያዛቸው ኢትዮጵያውያን ቁጥር 23 ሺሕ መድረሱንና ቁጥሩ አሁንም ሊጨምር እንደሚችል የገለጹት ዶ/ር ቴድሮስ፣ አሁን ባለው ግምትም ከ50 ሺሕ እስከ 80 ሺሕ ሊደርስ እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡

በሳዑዲ የሚገኙ ሕጋዊነት የሌላቸውን ኢትዮጵያውያን ትክክለኛ ቁጥር የኢትዮጵያም ሆነ የሳዑዲ መንግሥታት ማወቅ አለመቻላቸውን ዶ/ር ቴድሮስ ተናግረዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን በሃጂ ጉዞ ሄደው እዚያው ያለ ሕጋዊ ፈቃድ የቀሩ በመሆኑና ሌሎቹ ደግሞ በባህር አቋርጠው የገቡ በመሆናቸው መረጃ ማግኘት ባለመቻሉ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በሳዑዲ መንግሥት ሕግ መሠረት ሕጋዊነት የሌላቸው የውጭ ዜጎች የሕጋዊነት ጥያቄ ሳዑዲ ውስጥ እየኖሩ ማቅረብ እንደማይችሉ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ሕጋዊነት ያላገኘ ኢትዮጵያዊ የሕጋዊነት ጥያቄውን ለማቅረብ ከሳዑዲ መውጣት የሚገባው መሆኑ ችግሩን ውስብስብ እንዳደረገው ተናግረዋል፡፡

በመሆኑም አሁን ያለው አማራጭ ኢትዮጵያውያኑን ወደ አገራቸው መመለስ ነው ብለዋል፡፡ በእስካሁኑ ጥረት በርካቶች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ማድረግ መቻሉንና በአሁኑ ወቅትም በቀን ከአራት ሺሕ በላይ ዜጎችን መመለስ የተቻለበት አቅም መፈጠሩን፣ ይህም መጠን በቀሪዎቹ ጊዜያት ሊያድግ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

እስካለፈው ዓርብ ምሽት ድረስ የተመለሱ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከ19 ሺሕ በላይ እንደሚሆን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ወደ አገር የሚመለሱ ኢትዮጵያውያንን ለማቋቋም የፌዴራል መንግሥትና ክልሎች ተባብረው እየሠሩ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

እየተመለሱ ያሉት ዜጎች ወደ ቤተሰቦቻቸውና ቀድሞ ወደነበሩበት አካባቢ በፍጥነት መመለስ የሚፈልጉ በመሆኑ፣ ማንነታቸውን የሚገልጽ ዝርዝር ወደሚሄዱበት ክልል በመላክ እንዲንቀሳቀሱ በመደረግ ላይ ነው ብለዋል፡፡

ከሚመለሱት ኢትዮጵያውያን መካከል የሌሎች ጐረቤት አገሮች ዜጎች እንዳይቀላቀሉ ኃላፊነት ያላቸው የመንግሥት ተቋማት ማጣራት እያደረጉ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ወደ አገራቸው እየተመለሱ የሚገኙት ኢትዮጵያውያን ሕጋዊነት የሌላቸው ብቻ አለመሆናቸውን የጠቆሙት ዶ/ር ቴድሮስ፣ ሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ ያላቸው ኢትዮጵያውያንም ‹‹ለደኅንነታችን ስለፈራን›› በማለት ወደ አገራቸው ለመመለስ በመጠየቃቸው በጉዞው እንዲካተቱ ተደርጓል ብለዋል፡፡

በኢትዮጵያም ሆነ በተለያዩ አገሮች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለወገኖቻቸው እያሳዩ የሚገኘውን መቆርቆር ሚኒስትሩ አድንቀዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሳዑዲ ኤምባሲ ፊት ለፊት ተቃውሞ ለማድረግ የሞከሩ ኢትዮጵያውያን በፖሊስ እንዲበተኑ መደረጋቸውን አስመልክቶ በሰጡት አስተያየት፣ ሠልፍ ማድረግ የሚቻልበት ሕጋዊ አሠራር በአገሪቱ በመኖሩ ሊከለከሉ መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

‹‹ሠልፍ የወጡት ለበጎ አልያም ለሌላ ዓላማ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በሕጋዊ መንገድ መጠየቅ አለበት፤›› ብለዋል፡፡ በሳዑዲ ያለውን ሁኔታ ለፖለቲካ ጥቅም የማዋል ዝንባሌ በአንዳንድ ወገኖችና በተቃዋሚ ፓርቲዎች በኩል ሊኖር እንደሚችል ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

ነገር ግን ‹‹ይህንን ችግር ለፖለቲካ መጠቀም ኢትዮጵያዊነት አይደለም፡፡ በእነዚህ ወገኖቻችን ላይ መቀለድ ነው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

‹‹መንግሥት ባለው ይፋዊ መረጃ መሠረት በሳዑዲ መንግሥት ፀጥታ አስከባሪዎች የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ሦስት ነው፣ ነገር ግን ከዚህ በላይ ከሆነ ማጣራትን ይጠይቃል፤›› ብለዋል፡፡

ፀጥታ አስከባሪዎቹ በመጀመሪያው ቀን ባደረጉት የቤት ለቤት አሰሳና ኢትዮጵያውያኑን ወደ ካምፕ የመውሰድ እንቅስቃሴ ላይ በተከሰተ ግጭት በፖሊስ ስለተገደለው ኢትዮጵያዊ መንግሥት ማብራሪያ መጠየቁን ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያዊው ከፖሊስ መሣሪያ ሊቀማ በመሞከሩ መገደሉን የሳዑዲ መንግሥት ምላሽ የሰጠ ቢሆንም፣ ተጨማሪ ማጣራት ተደርጎ ማብራሪያ እንዲሰጥ በኢትዮጵያ በኩል በድጋሚ ተጠይቋል ብለዋል፡፡

በአጠቃላይ ይህ ሁኔታ በሌሎች አገሮች እንዳይከሰት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አምባሳደሮች ጥሪ ተደርጎላቸው ማከናወን ስለሚገባቸው ተግባር መመርያ እንደተሰጣቸው አብራርተዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው ውጪ የደረሰባቸው ሥቃይ እጅግ አሳዛኝ መሆኑን ዶ/ር ቴድሮስ ተመላሾቹን በማነጋገር መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ በአገሩ የሸቀጣ ሸቀጥ ሱቅ እንደነበረው አንድ ወጣት እንደገለጸላቸውና ንብረቱን ሽጦ ወደ ሳዑዲ ከገባ 12 ዓመታት በኋላ ዛሬ ባዶ እጁን ወደ አገሩ መመለሱን ወጣቱ እንዳጫወታቸው አስረድተዋል፡፡ ‹‹ኢትዮጵያውያንን ወደ ውጭ በመላክ ንግድ ላይ የተሰማራችሁ ደላሎችና አንዳንድ ኤጀንሲዎችን አሁንስ ተሰማችሁ? የሚል መልዕክት ማስተላለፍ እፈልጋለሁ፤›› ብለዋል ሚኒስትሩ፡፡

‹‹ለወገኖቻችሁ ስትሉ ከአሁን በኋላ ከዚህ ድርጊት እጃችሁን ሰብስቡ፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹አሁንስ ተሰማችሁ? አሁንስ ተሰማን ወይ? ለሁላችንም ጥያቄ መሆን አለበት፤›› በማለት አጋጣሚውን ለመልካም ተግባር ለመጠቀም በስፋት መንቀሳቀስ ተገቢ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

መንግሥት ማንኛውንም ጥረት ቢያደርግ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን እንግልት፣ እንዲሁም አሁንም ያለውን ስደት ያለ ኅብረተሰቡ ተሳትፎ ማስቀረት እንደማይቻል ገልጸዋል፡፡ reporter amharic

GOOGLGULE

No comments:

Post a Comment