Thursday, November 28, 2013

የዓለም ዋንጫ አዘጋጇ ብራዚል አሰቃቂ ገመና ሲገለጥ


ዳ ሲልቫ ካንታንሄዴ በአንደኛው እሁድ ከሰዓት ብስክሌቱ ላይ ሲወጣ አባቱ አይተውታል፡፡ እንደልማዱ መንደር ውስጥ እግርኳስ ሊጫወት እየሄደ መሆኑንም አውቀዋል፡፡ ነገር ግን ልጃቸው የተሳለ ቢላዋ ከጀርባው ሲደብቅ አላስተዋሉትም፡፡
አጭሩ እና ቀጭኑ የ19 ዓመት ወጣት ካንታንሄዴ ከታናሽ ወንድሙ ጆጅ ጋር በመሆን በሰሜን ምስራቅ በምትገኘው የብራዚል የገጠር ከተማ አልፈው ወደ ሴንትሮ ዶ ሜዮ ደረሱ፡፡ በቁርጥራጭ ቁሳቁስ የቆሸሸው የመጫወቻ ሜዳ መረብ ባይኖረውም የእንጨት ግቦች አሉት፡፡ የመሬቱ ሳሮች ተጋልጠው አሸዋው ይታያል፡፡ እዚህ የሚደረጉት ጨዋታዎች ይፋዊ አይደሉም፡፡ በተለምዶ ሁለቱ ቡድኖች ወደ ሜዳ ሲገቡ አንደኛው ቡድን ማሊያ ሲለብስ ተጋጣሚው ከወገብ በላይ ራቁቱን ይሆናል፡፡ ውጤት መመዝገቢያ ሰሌዳ ወይም ሌላ መረጃ መሳሪያ የለም፡፡ በሜዳው ዙሪያ የተንዠረገጉት ዛፎች ብቻ ጥላቸውን ይሰጣሉ፡፡
በጨዋታው የመጀመሪያ ግማሽ ካንታንሄዴ በተከላካይ ቦታ ተጫወተ፡፡ በኋላም በጉልበቱ እና ቁርጭምጭሚቱ አካባቢ ህመም ሲሰማው ለደቂቃዎች ጨዋታውን ትቶ ዳኛ ሆነ፡፡ በጁን መጨረሻ በዚያችው ዕለት በ1300 ማይል ርቀት ላይ በምትገኘው ሪዮ ዲ ጄይኔሮ የብራዚል ብሔራዊ ቡድን በኮንፌዴሬሽ ዋንጫ ስፔንን አሸንፏል፡፡ በዚያችው ዕለት በሴንትሮ ዶ ሜዮ የተፈጠረውን ዘግናኝ ታሪክ የዓለም ህዝብ የሰማው ግን ከሳምንት በኋላ ነው፡፡

Fifa-World-Cup-2014-Brazil
ከእረፍት መልስ ጨዋታው 15 ወይም 20 ደቂቃዎች እንደቀጠለ ካንታንሄዴ ለ30 ዓመቱ ጆሴሚር ሳንቶስ አብሬዩ ቢጫ ካርድ አሳይቶ ከጥቂት ቆይታ በኋላ ቀይ ካርድ መዘዘበት፡፡ ካንታንሄዴ እና አብሬዩ ጓደኛማቾች ነበሩ፡፡ ብዙ ጊዜም ለአንድ ቡድን ተጫውተዋል፡፡ ያን ቀን ጠላቶች ሆኑ፡፡ ድብድብ ተጀመረ፡፡ ካንታንሄዴ የደበቀውን ቢላዋ አውጥቶ አብሬዩን ሁለት ጊዜ ወጋው፡፡ አብሬዩ አቅራቢያው ወደሚገኝ ሆስፒታል ቢወሰድም አልተረፈም፡፡ ሞተ፡፡
ገዳዩ ካንታንሄዴ በስነ ስርዓት ፍርድ ቤት የመቅረብ እድል አላገኘም፡፡ የሟቹ አብሬዩ አራት ጓደኞች እጅ ገባ፡፡ አልኮል አብዝተው የወሰዱት እና ፀረ አደንዛዥ ዕፅ የተጠቀሙት ልጆች አልማሩትም፡፡ በመጠጥ ጠርሙስ ፊቱን ደጋግመው መቱት፡፡ ከእንጨት ጋር ካሰሩት በኋላ በሞተር ብስክሌት ገጩት፡፡ በመጨረሻም ጉሮሮውን በስለት ወጉት፡፡ በዚህ አልበቃቸውም፡፡ የእግሮቹን የታችኛው ክፍል ቆርጠው፣ እጆቹን ከሰውነቱ ጋር በቆዳው ብቻ እንዲንጠለጠል አድርገው እና ጭንቅላቱን ቆርጠውት በመጫወቻው ሜዳ ጠርዝ ጥለውታል፡፡
‹‹በመጀመሪያ ይህ በእርግጥ መደረጉን ማመን ተቸግሬያለሁ፡፡ የሰው ልጅ እንዲህ አይነት ክፋት ለመፈፀም አቅም ይኖረዋል ብዬ አላስብም›› ይላሉ የአካባቢው የፖሊስ አዛዥ እና የመርማሪው ቡድን መሪ ቫልተር ኮስታ ዶስ ሳንቶስ፡፡
ለአንድ ሳምንት ያህል ዜናው ታፍኖ ተያዘ፡፡ ሚዲያው ጆሮ ከደረሰ በኋላ ግን ለመራባት አፍታ አልፈጀበትም፡፡ ሁሉም የራሱን አስተያየት እና ስሜት ተናገረ፡፡ ብዙዎቹ ግን ውብ እግርኳስ ይታይባታል የተባለችው ሀገር ያለባትን ጉድ ሰምቶ የቀጣዩን የ2014 የዓለም ዋንጫ እና የ2016 ኦሎምፒክ እጣ ፈንታ ጠየቀ፡፡
እውነታው ከሚታሰበው በላይ የተወሳሰበ ነው፡፡ ክስተቱ በሁለት በዕድሜ የሚበላለጡ ወጣቶች መካከል የተፈጠረ ቁጣን መሰረት ያደረገ ግድያ ይሁን እንጂ አጋጣሚው በብራዚሎች ዘንድ እንደ ባህል የተለመደውን ስለት መሳሪያ የመያዝ እና የበቀል ችግር ቁልጭ አድርጎ ያሳየ ነው፡፡ በዚህ የግድያ ታሪክ ውስጥ የተስፋ ቢስነት እንዲሁም የድህነት እና የሀብት አለመመጣጠን ተስተውሏል፡፡ እርስ በርስ የመተማመን እና በፍትህ ስርዓቱ ላይ እምነት የማጣትን ችግርም መመልከት ይቻላል፡፡
የሴንተሮ ዶ ሜዮ ነዋሪዎች አፍረዋል፡፡ የዓለም ህዝብ የአካባቢውን ነዋሪ ጭምትነት አያውቅም፡፡ አሁን ሁሉም ሰው በዚህች ምድር የሆነውን ሰምቷል፡፡ እዚያው ብራዚል ውስጥ ያሉ አቅራቢያ ከተሞች እና ክልሎች ሳይቀሩ ሴንትሮ ዶ ሜዮ የተረገመች ቦታ ስለመሆኗ ያምናሉ፡፡ የ13 ዓመቷ ለቫኔቴ ሳንቶስ በምትኖርበት አካባቢ ላሉት የትምህርት ቤት ጓደኞቿ ምን እንደተፈፀመ ስትነግራቸው አንዳንዶቹ ልጆች ያማትቡ ነበር፡፡ ‹‹ራሳቸውን ከእኛ መጠበቅ እንዳለባቸው ያምናሉ›› ትላለች ሳንቶስ፡፡

የሜዳ ላይ ረብሻ
ራይሙንዶ ሳ ከዛሬ 10 ዓመት በፊት በዳኝነት የመሩትን አንድ አማተር ጨዋታ ያስታውሳሉ፡፡ የፊሽካውን ድምፅ አሰምተው ለአንደኛው ቡድን የፍፁም ቅጣት ምት ሰጡ፡፡ ጉዳዩ ያስቆጣቸው እና ፍፁም ቅጣት ምቱ የተሰጠባቸው ተጨዋቾች ከበው ጮሁባቸው፡፡ እንዲሁም አስፈራሯቸው፡፡ ‹‹ከዚህ በህይወት አትወጣም›› አለው አንደኛው ተጫዋች፡፡ ሌላኛው ተከተለና ‹‹ፖሊስ ነው፡፡ ምናልባትም ሽጉጥ ታጥቆ ይሆናል›› አለ፡፡
በእርግጥም ይህንን ታሪክ ሳኦ ሉዊስ ውስጥ በሚገኝ ቢሯቸው ተቀምጠው የሚተርኩት ሳ አሁን የፖሊስ ኮሎኔል ናቸው፡፡ በሴንትሮ ዴ ማዮ አካባቢ በፕሮፌሽናል ጨዋታዎች ጊዜ የሚፈጠሩ ረብሻዎችን በስራቸው ካሉ ባልደረቦቻቸው ጋር የመቆጣጠር ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ይሁን እንጂ አሁን በአካባቢያቸው የተፈጠረው ግድያ የሀገራቸው የእግርኳስ ውብ ገፅታ እንደማይበርዘው ያምናሉ፡፡
የጨዋታ ዳኛ ሽጉጥ እንዲይዝ መብት የለውም፡፡ ሆኖም ብዙ ጊዜ ይህ ያጋጥማል፡፡ በሳኦ ሉዊስ ፖሊስ በማይመጣባቸው ቦታዎች የሚደረጉ አማተር ጨዋታዎችን የሚዳኙ ሰዎች ራሳቸውን ለመጠበቅ ሰንጢ እንዲሁም አይን ላይ የሚረጭ የበርበሬ ስፕሬይ ይይዛሉ፡፡ ይህንን ሳ ራሳቸውም ያረጋግጣሉ፡፡ እዚህ ግባ የማይባል ገንዘብ የሚከፈላቸው እነዚህ ዳኞች ‹‹ለዚህችስ ብዬ ህይወቴን አላጣም›› እንደሚሉም ይገልፃሉ፡፡
የሶቪዮሎጂ ምሁራን የጥናት ውጤት እንደሚጠቁመው ከሆነ በብራዚል በደጋፊዎች ረብሻ ምክንያት የሚከሰተው ሞት በሌላ በየትም ሀገር በተመሳሳይ መልኩ ከሚፈጠረው በእጅጉ ይበልጣል፡፡ አሁን ደግሞ ይበልጥ ተባብሷል፡፡ ከ10 ዓመት በፊት በዓመት በአማካይ የ4.2 ሰዎችን ነፍስ ይቀጥፍ የነበረው ሰበብ አሁን ቁጥሩን በ2012 ወደ 23 አድርሶታል፡፡
የብራዚሉ ሳምንታዊ የእግርኳስ ጋዜጣ ላንሴ ከ1988 እስከ 2012 ድረስ የዘገበባቸው የእግርኳስ ተያያዥ ግድያዎች 155 ቢደርሱም ጥፋት አድርሰዋል ተብለው በህግ የተያዙት ሰዎች 27 ብቻ ናቸው፡፡ በእርግጥ ከእነዚህ ግድያዎች መካከል ብዙዎቹ ከድጋፍም ያለ የውንብድና ህይወት ውስጥ ገብተው ከክለቦች እና ከፖሊሶች ጋር ችግር ባለባቸው የረብሻ ቡድኖች መካከል የተፈጠሩ ናቸው፡፡
በሳልጋዶ ደ ኦሊቪዬራ ዩኒቨርሲቲ ሶሺዮሎጂስቱ ማውሪሲዮ ሙራድ በብራዚል የሚፈፀሙትን ግድያዎች ከስፖርቱ ጋር ማያያዝ ተገቢ እንዳልሆነ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ከእግርኳስ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት የለውም፡፡ መጠት ቤትን ጨምሮ በሌላ በየትኛውም ቦታ ሊፈጠር የሚችል ነገር ነው፡፡ የእግር ኳስ ረብሻ ብለን መጥቀስ ያለብን ሁለት የተቃራኒ ቡድን ደጋፊዎች እርስ በርስ የሚገቡበትን ቀጥተኛ ግጭት ነው፡፡ ከእግርኳስ ረብሻ ይልቅ አሁን በብራዚል ያለው ‹‹ረብሻ›› ነው፡፡
ብራዚሊያን ሴንተር ፎር ላቲን አሜሪካን ስቲዲስ በተሰኘ የምርምር ማዕከል ባለፈው ጁላይ ይፋ የተደረገ ጥናት እንደመሰከረው ከሆነ ብራዚል በዓለም ሰባተኛዋ የረባሾች ሀገር ነች፡፡ ትልልቅ ግድያዎችን የፈፀሙ ሰዎች እና ሙስና ውስጥ የተፈቁ ባለስልጣናት ያለ ችግር ይንቀሳቀሱበታል፡፡ ግድያዎች በትልልቆቹ ከተሞች ሪዮ እና ሳኦ ፖሎ ቢቀንሱም በሰሜን ምስራቅ ብራዚል ተባብሷል፡፡ በዚህ ጥናት መሰረት የግድያዎቹ ዋነኛ ምክንያት የቡድን ወንጀለኝነት ወይም የአደንዛዥ መድሃኒት ሳይሆን በጓደኞች፣ በጎረቤቶች እንዲሁም በባል እና ሚስት መካከል የሚፈጠሩ ቀላል አለመግባባቶች ናቸው፡፡
ማራንሆ በተሰኘችው ቦታ ብቻ ከ2001 እስከ 2011 በ100 ሺ ነዋሪዎች መካከል የግድያው ቁጥር በዓመት ከነበረበት 9.4 ወደ 23.7 አድጓል፡፡ በእርግጥ ይህ አካባቢ በቂ የፖሊስ ቁጥር የማይመደብለት እንደሆነ መናገር ይቻላል፡፡ ለ6.7 ሚሊዮን ነዋሪ የተመደቡት ፖሊሶች 11 ሺ ብቻ ናቸው፡፡ በኒውዮርክ ከተማ 34,500 ፖሊሶች እንደሚገኙ አስተውሉ፡፡ የማራንሆ አካባ ፍትህ ቢሮ ኃላፊው ሴባስቲያዎ አልባኩሌኬ ኡቾ አካባቢው ስድስት ሺ ተጨማሪ ፖሊሶች እንደሚያስፈልገው ያምናሉ፡፡ አንቶኒዮ ሊማ ዲ ካርቫልሆ የተሰኙት የቦታው ፖሊስ ‹‹አለመታደል ሆኖ የሚጎድሉን ነገሮች ብዙ ናቸው፡፡ የፖሊስ መኪና፣ የሰው ኃይል፣ መሰረተ ልማት፣ ስልኮ፡፡ ሌላው ቀርቶ ራዲዮኖች እንኳን የሉንም›› ይላሉ፡፡
የስለት መሳሪያ እና ፍትህ
ሴንትሮ ዶ ሜዮ በመንግስት ብዙ ቃል ተገብቶላት ጥቂት የተፈፀመባት አካባቢ ነች፡፡ በቦታዋ ሞተር ብስክሌቶች ባልተጠረገው እና በድንጋያማው እና አቧራ ባለው መንገድ ላይ ሲበሩ ይውላሉ፡፡ የቀንድ ከብቶች በየሜዳው የሚጋጥ ሳር ፍለጋ ይፈስሳሉ፡፡ የአካባቢው ሙቀት ሲያይል ነዋሪዎቹ አነስተኛ ወንበሮች እየያዙ ዛፎች ስር ይቀመጣሉ፡፡ ሙቀቱን መቋቋሚያ የአየር ሁኔታ መቆጣጠሪያ ያልተገጠመባቸውን ቤቶቻቸውን በሮች እና መስኮቶች ይከፍታሉ፡፡ አይኖቻቸው እና ጆሮዎቻቸውም ከውጪ የሚመጡ እንግዶች ቢኖሩ ብለው እንደተከፈቱ ይጠበቃሉ፡፡
ጎብኚዎች ወደ አካባቢው ሲመጡ ፀሐይዋን ተጠልለው የሚቀመጡበት ወንበር ይሰጣቸዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜም ምሽትን የሚያሳልፉበት በወንፊት ጨርቅ የተከለለ ማረፊያ ይቀርብላቸዋል፡፡ ህፃናት በፓፓያ ዛፍ ቅርንጫፍ የተሰራ ‹‹ዋሽንት›› ይጫወታሉ፡፡ ልጃገረዶችም በተለያዩ ጨዋታዎቻቸው ቦታውን ካርኒቫል ያስመስሎታል፡፡
‹‹ይህ የተረጋጋ ቦታ ነው›› ይላል የ30 ዓመቱ ጆዜ ኩንሀ ዛፍ ስር እንደተቀመጠ፡፡ ‹‹አልኮል ብዙ ጠጥተህ መንገድ ላይ ብትወድቅ ችግር አይደርስብህም፡፡ ቤቴ ብትመጣ እና ረሃብ ቢሰማህ ዶሮዎቻችንን አርደን እናበላሃለን›› በእርግጥ ይህቺ አካባቢ በቅርብ ዓመታት ያስተናገደችው ግድያ አንድ ብቻ ነው፡፡ በቦታዋ ፀጥታ ቢሰፍንም ጥበቃ የሚደረግላት በሰባት ፖሊሶች እና ሁለት የፖሊስ መኪኖች ብቻ ነው፡፡ አንዳንዶቹ የቦታዋ ነዋሪዎች የመንግስት ባለስልጣናት እያገዟቸው አለመሆኑን ያስባሉ፡፡
በቅርቡ የ31 ዓመቷ ኤድና ማሪያ ዶስ ሳንቶስ ከተቀመጠችበት ዛፍ ስር አንዲት አይጥ ስታልፍ ተመለከተች እና ወንዱ ልጇን አባርሮ እንዲይዛት ነገረችው፡፡ ልጇ የታዘዘውን ችላ ብሎ ቆሞ መቅረቱን የተመለከተችው ኤድና ‹‹አንተ ማለት ልክ እንደ ፖሊስ ነህ›› ብላ ልታበሳጨው ሞከረች፡፡
በሴንትሮ ጩቤ ታጥቆ መንቀሳቀስ የተለመደ ነው፡፡ ከወንዶቹ ካናቴራ ስር በቀላሉ ይታያል፡፡ የ67 ዓመቱ ጆአኪም አሩዳ አምስት ኢንች የሚረዝም ጩቤ በጅንስ ሱሪያቸው ሸጉጠው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ሰውዬው ስለራሳቸው እና ስለሌላ ሰው ሚስት ገጠመኛቸው ሲናገሩ በመዳፋቸው፣ በክንዳቸው እና አንገታቸው ላይ ያለውን ጠባሳ ‹‹የፍቅር ታሪክ ነው›› ብለው ይስቃሉ፡፡
‹‹ብርቱካን እና አናናስ ለመብላት ጩቤው ያገለግልሃል፡፡ ራስህም ትከላከልበታለህ›› ይላሉ አሩዳ፡፡ ‹‹ፖሊስ ማንንም ረድቶ አያውቅም›› የኤድና ባል የሆነው የ30 ዓመቱ ሜሮኤል ዶስ ሳንቶስ የመንደሩን ቆሻሻ እያነሳ የሚተዳደር ሰው ነው፡፡ ዶስ ሳንቶስ የፖሊስ ጣቢያውን የተጠራቀመ ቆሻሻ ሲያነሳ ብዙ ጊዜ ማጠራቀሚያው ውስጥ ጩቤዎች እንደሚያገኝ ይመሰክራል፡፡ በሳኦ ሴባስቲያኦ ሆስፒታል የሚሰሩት ዶክተሮች እና ነርሶችም በየወሩ አንድ ወይም ሁለት በጩቤ የተወጋ ሰው እንደሚያጋጥማቸው ይናገራሉ፡፡
አልኮል፣ ማሪዋና እና ኮኬይን በአካባቢው በብዛት ጥቅም ላይ እንደሚውል ባለስልጣናት ይናገራሉ፡፡ ነርሷ አልሜርንዳ አልቬሽ ሶውሳ ባለማወቅ አደንዛዥ ዕፆችን እየተጠቀሙ ችግር ውስጥ ገብተው የሚመጡ እንዲሁም አዕምሯቸው የተቃወሰባቸው እና እይታቸው የተበላሸባቸው ወጣቶች እንደሚያጋጥሟት ትመሰክራለች፡፡ ‹‹ሰዎች ሁል ጊዜም ከቤታቸው የሚወጡት ከሰው ጋር ግጭት ውስጥ ላለመግባት እየፈሩ ነው›› ትላለች የ27 ዓመቷ ሶውሳ፡፡
ለበርካታ አስርት ዓመታት በብራዚል የጆዜ ሳርኔይ ቤተሰቦች በፖለቲካው ትልቅ ድርሻ ነበራቸው፡፡ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ልጅ ሮሴይና ሳርኔይ የማራንሆ ገዢ ነበረች፡፡ በእነዚያ ዓመታት ገዢዎቹ ብዙ መሬት የያዙ እንዲሁም ሚዲያውን የተቆጣጠሩ ነበሩ፡፡ የሳርኔይ ቤተሰብ ህዝቡን ‹‹ጥገኛ፣ ዝቅተኛነት የሚሰማው እና የተተወ›› መሆኑን እንዲቀበል አድርጎት እንዳለፈ የብራውን ዩኒቨርሲቲ ምሁሩ ጀምስ ግሪን ይናገራል፡፡
የጆዜ ልጅ
የካንታንሄዴ እና አብርዲን ህይወት የቀጠፈው አጋጣሚ ከመከሰቱ በፊት የሁለቱ ልጆች መንደር ሰዎች አንዳቸው ለሌላቸው እንደ ባይተዋር መተያየት ጀምረው ነበር፡፡ እንዲያውም ካንታንሄዴ ወደዚያች መንደር ሄዶ ኳስ ሊጫወት መሆኑን ያወቁት አክስቱ እንዳይሄድ ጠይቀውት ነበር፡፡ ከሞቱ ሁለት ቀናት በፊትም ሴትየዋ ወደዚያ መሄድ ይቅርብህ ብለው ሲመክሩት ‹‹አትጨነቂ! ልጆቹ ጓደኞቼ ናቸው›› ብሏቸዋል፡፡
ካንታንሄዴ ያደገው ከአባቱ፣ ወንድሙ እና እህቱ ጋር መካከለኛ ደረጃ ባላት የሳንቶ አንቶኒዮ አካባቢ መኖሪያ ቤታቸው ነው፡፡ በሳምንቱ ቀናት ልጁ በማለዳ ዶሮ ሲጮህ ተነስቶ ከብቶችን ወደ ግጦሽ ሲያሰማራ እግረ መንገዱንም ለአጥር የሚሆን እንጨት ለማግኘት ዛፎች ይቆርጣል፡፡ ማታ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ይከታተላል፡፡ ወደፊት አካውንታንት ለመሆንም ይመኛል፡፡ ‹‹አዎ ትልቁ ህልሙ ይህ ነበር›› ትላለች የ27 ዓመቷ ታላቅ እህቱ ለሴሊያ ስራይቫ፡፡
የሳምንቱ መጨረሻ ቀናት የእግርኳስ ናቸው፡፡ ካንታንሄዴ በራዮ ከሚገኙት ፕሮፌሽናል ክለቦች አንደኛው የሆነውን ፍሉሚኔንሴ ይደግፋል፡፡ በግል ደግሞ ለኔይማር አድናቆት ነበረው፡፡ የባርሴሎናው ኮከብ ብሔራዊ ቡድኑ ስድስተኛውን የዓለም ዋንጫ እንዲያነሳ እንዲያግዝ ይመኝ ነበር፡፡
በጁን ወር የመጨረሻዋ ቀን ካታንሄዴ ምሳውን ከበላ በኋላ ወደ ጨዋታው ከመሄዱ በፊት ጥቂት እንቅልፍ ተኛ፡፡ ሲነሳም ካናቴራውን እና ሰማያዊ ጂንስ ቁምጣውን ለበሰ፡፡ ከጉልበቱ በታች የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ቼልሲ አርማ ያለበትን የግጭት መከላከያ አደረገ፡፡ አባቱ የመጨረሻ ልጃቸው ሲወጣ ከጀርባው መጠነኛ ቦርሳ መሸከሙን ብቻ እንዳዩ ይገልፃሉ፡፡ ‹‹ቤት ውስጥ ወዲያ ወዲህ ሲል የነበረው ጩቤ ታጥቆ ነው ብዬ ማመን ያስቸግረኛል›› ይላሉ ጆዜ ሬይመንዶ ሮድሪጌዝ ካንታንሄዴ፡፡ ‹‹ምናልባት ታጥቆ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አላየሁትም›› ሌሎች ግን አይታውታል፡፡ የ14 ዓመቱ የጎረቤታቸው ልጅ ፊሊፔ ፍራንካ ቀደም ብሎ አንድ ቀን ካንታንሄደ ጩቤ ይዞ ቤታቸው ፊት ለፊት ተቀምጦ እንዳገኘው ተናግሯል፡፡ ሌላው ጓደኛው የ14 ዓመቱ ጉስታቮ ሄንሪኬም በሌላ ጊዜ ካንታንሄዴ ኳስ ለመጫወት ሲል እንዲመቸው ብሎ የጩቤውን ቦታ ከጎኑ ለማድረግ ሲያስተካክል አስተውሎታል፡፡
የልጁ ህይወት ምናልባትም ብዙዎች ከገመቱት በላይ የተወሳሰበ ነበር፡፡ ባለፈው ፌብሩዋሪ በአካባቢው የተከበረው የካርኒቫል በዓል ላይ ካንታንሄዴ በሌላ ሰው በጩቤ ክንዱ እና ከጆሮው አካባቢ መወጋቱን አባቱ ያስታውሳሉ፡፡ በዚህም በሆስፒታል አንድ ሌላት አሳልፎ ቁስሎ ተሰፍቶለታል፡፡
‹‹የወጋው ሰው ካንታንሄዴ ሌላ ከሚፈልገው ሰው ጋር ተመሳስሎበት ነበር›› የሚለው የ20 ዓመቱ ሊዮኒልዶ ሲማ ነው፡፡ በካርኒቫሉ ጊዜ ከካንታንሄዴ ጎን ቆሞ የነበረው ሊማ አጋጣሚው የተፈጠረው በስህተት እንደነበር ይናገራል፡፡ ሌላኛው የካንታንሄዴ ጓደኛ የ18 ዓመቱ ሀድሰን ሮኒ ኦሊቪዬራ ሊማ ግጭቱ የተፈጠረው በእንስት ምክንያት ሳይሆን እንደማይቀር ይጠረጥራል፡፡ ሆኖም ‹‹ካንታንሄዴ ከዚያ ግጭት በኋላ ፈርቶ ነበር›› ይላል፡፡
ካንታንሄዴ ከእናቱ ሞት በኋላ ተስፋ ቢስነት ይሰማው እንደነበር እህቱ ትናገራለች፡፡ እናቱ ወሊዳ ማርኬዝ ዳ ሲልቫ በ46 ዓመታቸው ከሁለት ዓመታት በፊት ሲሞቱ የህልፈት ህይወታቸው ሰበብ አንድ የከባድ መኪና በዋና ጎዳና ከሚያሽከረክሩት ብስክሌት ጋር መትታቸው ነበር፡፡ ለካንታንሄዴ ‹‹የእናቱ ሞት እጅግ አስደንጋጭ ሆኖበት ነበር›› የምትለው ሳራቪያ ነች፡፡ ከባድ መኪና ሹፌሩ አደንዛዥ ዕፅ ሳይወስድ እንዳልቀረ የካንታንሄዴ ጓደኛ ሊማ ይጠረጥራል፡፡ ‹‹ይህንን መበቀል እንዳለበት ያስብ ነበር››
የማሪያ ልጅ
እንደ ጆሴሚር አብሬዩ እናት ምስክርነት ከሆነ ልጃቸው ከቤቱ የወጣው ጨዋታ ለማየት ብቻ ነበር፡፡ ሆኖም በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ሊያማ ብቻ የተገኘበት ጨዋታ ላይ እንዲሳተፍ ተጋበዘ፡፡ አብሬዩ የ30ኛ ዓመት ልደቱን ያከበረው ከሁለት ቀናት አስቀድሞ ነበር፡፡ በልደቱ ዝግጅት ከፀለየ በኋላ ከሚስቱ ጋር ኬክ እና ለስላሳ መጠት ተቃመሰ፡፡ አብሬዩ የልጅ አባት የሆነው ገና በታዳጊነቱ ነበር፡፡ ስለዚህም ትምህርቱን አቋርጦ ለስራ ተነሳ፡፡ በትዳር የተጣመራት እንስት መምህር መሆኗ ጠቅሞት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ወደ መጨረሱ ተቃርቦ ነበር፡፡ ከማሪያ አምስት ልጆች ሶስተኛው አብሬዩ ዘመዶቹን እጅግ የሚወድ እና ሌላ ልጅ ለመውለድ የሚጓጓ ነበር፡፡ ‹‹ስፖርት ይወዳል፡፡ ሌላ አመል የለበትም›› ይላሉ እናቱ፡፡
ሜዳ ላይ አብሬዩ ተፋላሚ እና ሀይል ቀላቅሎ የሚጫወት አማካይ ነው፡፡ ሆኖም ልጅ የሚጥል በሽታ አለበት፡፡ እናቱ ማሪያ ልጃቸው ይህ በሽታ ያገኘው በ13 ዓመቱ ከዛፍ ስለወደቀ መሆኑ ተነግሯቸው አምነዋል፡፡ ጨዋታ ላይ አንዳንድ ጊዜ ሜዳ ላይ ይጥለዋል፡፡ ሆኖም መድሃኒቱን ተከታትሎ እንደሚውጥ እና ችግሩ መለስ እንዳለበት እናቱ ያስረዳሉ፡፡
አብረውት ከሚጫወቱት አንዱ የሆነው ሊዮኒልዶ ሊማ ስለ አብሬዩ ሲናገር ‹‹ሁልጊዜም ሊጣላን ይፈልግ ነበር›› ይላል፡፡ የሊዮኒልዶ ወንድም የሆነው ሊኦናርያ ሊማ ፌሩይራም በበኩሉ አብሬዩ ባህሪይ የማይገመት እና ሜዳ ላይ ከሌሎች ጋር መስማማት የማይችል እንደነበር ይመሰክራል፡፡ ሆኖም ሁሉም ልጆች ተመሳሳይ አለመግባባቶች ሲፈጠሩ ቁጣቸውን ለማብረድ ዘወር ይላሉ፡፡ ‹‹አሁን የተፈጠረውን አልጠበቅንም፡፡ ሁለቱም ጓደኞቻችን ነበሩ›› ይላል ፌሬይራ፡፡
አብሬዩ እና ካንታንሄደ ከግጭታቸው አንድ ሳምንት በፊት እንኳን አብረው ለአንድ ቡድን ተጫውተው ካሸነፉ በኋላ በጋራ ጨፍረዋል፡፡ ቢራ እየተጎነጩም ድላቸውን አክብረዋል፡፡ ባለፈው ፌብሩዋሪ ካንታንሄደ በጩቤ መወጋቱን ሲሰማ አብሬዩ ሆስፒታል ድረስ ሄዶ ጠይቆታል፡፡ ‹‹የልብ ጓደኛሞች አልነበሩም፡፡ ሆኖም በእግርኳስ ምክንያት ይተዋወቁ ነበር›› ትላለች የአብሬዩ ሚስት ጆሴሚር፡፡

ነፍስ የቀማው ጠብ
የጨዋታው ሁለተኛ አጋማሽ ተጀምሮ 15 ወይም 20 ደቂቃ እንደሆነው በጉዳት ምክንያት ወደ ዳኛነት የተለወጠው ካንታንሄዴ በአብሬዩ ላይ ቢጫ ካርድ መዘዘ፡፡ ካንታሄዴ ካርድ ያወጣው ለወንድሙ ጆርጅ አድልቶ እንደሆነ ያመነው አብሬዩ በቁጣ ብዙ ተከራከረ፡፡ ከዚያ በኋላ ተከታታይ ጥፋቶች አጠፋ፡፡ የፊሽካ ድምፅ ከሰማ በኋላ ኳሷን በሀይል መታት፡፡ ሳይቆይ ደግሞ ሆን ብሎ ኳስ በእጁ ነካ፡፡ ቀጥሎም እግሩን ከፍ አድርጎ አደገኛ አጨዋወት ሊጫወት ሞከረ፡፡ አብሬዩ ቀይ ካርድ ማየት የፈለገ ይመስል ነበር፡፡ ካንታንሄዴ ቀይ ካርድ ካሳየው በኋላ ግን ሜዳውን ሊለቅ አልፈቀደም፡፡ ካንታንሄዴም አብሮት ሊወጣ እንደሚገባ ተሟገተ፡፡ ግርግሩ ሲበረታ አንድ በዕድሜ ሄድ ያሉ ሰው ጣልቃ ገቡ፡፡ ነገሩ የበረደ መሰለ፡፡
ካንታንሄዴ እና አብሬዩ ወደቤታቸው እንደሚሄዱ ተገምቶ የነበረ ቢሆንም ቃላት መወራወር ጀመሩ፡፡ ካንታንሄዴ አብሬዩን ‹‹ጅል›› ብሎ ሰደበው፡፡ አብሬዩ በፈንታው በህይወት የሌሉትን የካንታንሄዴ አናት ‹‹ሴተኛ አዳሪ›› ብሎ መሳደቡን ሊማ ሆድሰን ይናገራል፡፡ ከዚህ በኋላ ተያያዙ አብሬዩ በቦክስ እና ‹‹በጠረባ›› ደጋግሞ መታው፡፡ የወደቀው ካንታንሄዴ ከመሬት ሲነሳ በእጁ ጩቤ ይዞ ነበር፡፡ አብሬዩን ጎኑ ላይ እና ደረቱ ላይ ሁለት ጊዜ ወጋው፡፡ አብሬዩን ወደ ሆስፒታል ሲወስድ ካንታንሄዴ እንዳያመልጥ ታሰረ፡፡
ስልኮች ወደ ፖሊስ ጣበያ ቢደወሉም መልስ አልነበረም፡፡ ሉዊስ ሞራይስ ደ ሶዛ ሜዳው ጠርዝ ላይ ቆሞ በዋጋ ርካሽ የሚባለውን መጠጥ እየወሰደ ነው፡፡ ከደቂቃዎች በፊት እየተጫወተ እያለ ሰክረሃል ተብሎ ከሜዳ እንዲወጣ ከተደረገ ጀምሮ እየጠጣ ነው፡፡ ሞራይስ የአብሬዮ አብሮ አደግ ነው፡፡ የመጠጡ ኃይል እና ከአብሬዩ ጋር የነበረው ቅርበት ተደማምሮ ወደ ታሰረው ካንታንሄዴ አመራ፡፡ ሌሎችም ወሬውን የሰሙ የሰፈሩ ልጆች ግማሹ ባዶ እግሩን ሌላውም በሞተር ብስክሌት መጡ፡፡
ካንታንሄዴ እንደታሰረ የፖሊሶችን መድረስ ቢጠባበቅም አልመጡለትም፡፡ ሞራይስ ጠየቀው፡፡ ‹‹ጆሴ ሚርን ለምን ወጋኸው?›› ‹‹የእናቴን ሞት ለመበቀል!›› ሞራይስ በድጋሚ ጠየቀ፡፡ ‹‹የገደላት ማን ነው?›› ካንታንሄዴ ‹‹የከባድ መኪና ሾፌር›› ሲል መለሰ፡፡ ከዚህ በኋላ እንደታሰረ አሰቃቂው ድብደባ እና ግድያ ተፈፀመ፡፡
Ze-Habesha Website may contain advice, opinions, and statements of various information and content providers. The Website neither represents nor endorses the accuracy of information or endorses the contents provided by external sources. All blog posts and comments are the opinion of the authors.

No comments:

Post a Comment